Saturday 31 December 2022

“የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መጻሕፍት ሁሉ - ኒዎኔወስቶስ” (2ጢሞ. 3፥16)

Please read in PDF

ቅዱስ ጳውሎስ ኹለተኛ ጢሞቴዎስን ሲጽፍ፣ የኑዛዜ ያህል በሞቱ ዋዜማ ነው (4፥6)፤ የሚጽፍለት ደግሞ “በመንፈስ ለወለደው ልጁ” (1፥2) ቅዱስ ጢሞቴዎስ ነው፤ ለዚህ ተወዳጅ ባላደራ አገልጋይ፣ የቅዱሳት መጻሕፍትን እስትንፋሰ እግዚአብሔርነት በግልጥ ይጽፍለታል። ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ክፍል፣ መጽሐፍ ቅዱስን፣ “ቅዱሳት መጻሕፍት” እና የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መጻሕፍት” በማለት ይጠራቸዋል። “ኒዎኔወስቶስ” የሚለውም የግሪክ ቃል፣ የቅዱሳት መጻሕፍትን የእግዚአብሔር እስትንፋስነት የሚገልጥ ቃል ነው።

Sunday 25 December 2022

ሄኖክ ኃይሌ(ዲያቆን) ስለ አዋልድ መጻሕፍት ያሳየው ደካማና ጠንካራ ሙግቱ!

 Please read in PDF

ሄኖክ ኃይሌ፣ ስለ ተአምረ ማርያም በጻፈው ኹለተኛ ክፍል ላይ እስካኹን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ አዋልድ መጻሕፍትን (ማለትም ትርጓሜያትን፣ ገድላትን፣ ድርሳናትን፣ መልክዐ መልክዕን፣ ተአምራትን፣ ነገራትን፣ ፍካሬያትን) ለማስተካከልና ለማደስ የተቸገረችበትን ምክንያት ሲጠቅስ እንዲህ ይላል፤

“ … ላለፉት ሠላሳ ዓመታት ያሳተሟቸውና በነጻ ያደሏቸው መጻሕፍት … ክርስቶስን ‘ጨርሶ አታውቂም’ የሚሏትን ከሳሾችዋን በማስታገሥ ሥራ ላይ ተጠምዳ እንድትቆይ ግድ ኾኖባት ቆይቶአል።”

Friday 16 December 2022

ዮናታዊ ቀበሮነት!

 Please read in PDF

በግልጽ ቃል የዮናታን ዓላማ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አይደለም፤ ዓላማው ቅዱስ ወንጌልን መስበክ ቢኾን ኖሮ፣ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” ከሚባል ነሁላላ ትምህርት አስቀድሞ ራሱን ባረቀና በጠበቀ ነበር። ነገር ግን ይህ የኑፋቄ ትምህርቱ እንዳይታወቅበት፣ የኦርቶዶክስን ድርሳንና ገድላት በመንቀፍና በመተቸት “ራሱን ወንጌላዊ አድርጎ ለማቅረብ” ብዙዎችን ያሞኛል፤ ያጃጅላል።



Monday 12 December 2022

ተሐድሶ እንዴት ይታያል? የመጨረሻ ክፍል

 Please read in PDF

ካለፈው የቀጠለ …

የቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓታት የዶግማ ማስፈጸሚያ ሥልቶች ናቸው። ለምሳሌ መጠመቅ የግድ ነው፦ ዶግማ ነው፤ የአጠማመቅ ኹኔታ ግን ሥርዓት ነው። ቁርባን ዶግማ ነው፤ ‹እንዴት መቁረብ ይኖርብናል?› በሥርዓት መልስ ያገኛል። በዚህ ዓይነት ከሐዋሪያት ጀምሮ ያሉ አባቶች ከኅብረተ ሰቡ የአኗኗር ሁኔታ ጋር የሚስማሙና ለጽድቅ ሥራ የሚያበቁ የእምነት መተግበሪያ ስልቶችን ነድፈዋል፤ እንደ ኹኔታውና እንደ ኅብረተ ሰቡ እያዩም ሊያስተካክሉት ይችላሉ።

Sunday 11 December 2022

ተሐድሶ እንዴት ይታያል? ክፍል ፩

 Please read in PDF

ከረጅም ጊዜያት ጀምሮ የተሐድሶ ጉዳይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አነታራኪ ኾኖአል። ንትርኩም “ባፍ በመጣፍ” እንደሚባለው ኾኖአል ማለት ይቻላል። ንትርኩና ፍትጊያው አኹንም ድረስ ያለና እንዲያውም፣ በአኹን ወቅት ደግሞ በኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ “ጸረ ተሐድሶ የተባሉ ኮሚቴዎች” የተቋቋሙበትና ከፊት ይልቅ በጽኑ ለመቃወም ቅስቀሳ እንዳለ ጸሐፊው ያስተውላል። ንትርኩና ጭቅጭቁ ደግሞ፣ ቀለል ከሚለውና ለመመለስ ግን ከሚቸግረው፣ “ተሐድሶ የሚባለው እንቅስቃሴ አለ ወይስ የለም?” ከማለት ይጀምራል። እኔም ከዚሁ፣ “እውን የተባለው የተሐድሶ እንቅስቃሴ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ እየተካሔደ ነው ወይስ የለም?” ብዬ በመጠየቅ ልነሳ ፈለግኹ።



Saturday 3 December 2022

የዕብራውያን መልእክት ዓላማና የእኛ ዘመን መመሳሰል!

 Please read in PDF

ኢየሱስ ከይሁዲነት ይልቃል!

ኢየሱስ ከኦሮሞነትና ከአማራነት ከሌሎችም ይልቃል!

ኹሉም የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት የተጻፉበት የየራሳቸው ዓላማ አላቸው፤ የመጻሕፍቱ ዋነኛ ዓላማ ማጠንጠኛው ደግሞ፣ የእግዚአብሔር መንግሥትን ማዕከል ያደረጉ ናቸው፤ ከዚህም የተነሣ ዓላማቸው የሚበልጠውንና የሚልቀውን የእግዚአብሔርን ዐሳብና ፈቃድ ማሳየት ነው። ከዚህ አንጻር የዕብራውያን መልእክትን ስንመለከት፣ ኹለት ዋና ዋና ዓላማዎችን ማውጣትና መናገር እንችላለን።

የመንፈስ ቅዱስ ጸጋዎች ቀርተዋል ለማለት አንሻፍፈው የሚተረጕሟቸው ጥቅሶች

Please read in PDF

   “በአሁኑ ዘመንም የመንፈስ ቅዱስ እንቅስቃሴ በሚታይበት ቦታ ኹሉ አንዳንዶች ያፌዛሉ፤ ሌሎች ደግሞ እውነተኛ ምልክት እያዩ “ዐይኔን ግንባር ያድርገው” በማለት ለአኹኑ ዘመን አይደለም የመንፈስ ቅዱስ ስጦታዎች በሐዋርያት ዘመን አክትሟል ሲሉ ሌሎች ደግሞ “ተጠንቀቁ” በማለት በድፍኑ መሸሽን ይመርጣሉ።”[1]

ኹሉም የስሕተት አስተማሪዎች የመጽሐፍ ቅዱስን ክፍሎች ለትምህርታቸው ዋቢነት ከዐውዱ ውጭ ቦጭቀው በማውጣትና በመጥቀስ ዘወትር ይታወቃሉ። የቅዱሳት መጻሕፍትን ሐሳብ ለገዛ ትምህርታቸው በማጣመም ይታወቃሉ፤ ግልጡን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በማጣመም ወይም አወሳስቦ በመተርጐም የሚያኽላቸው የለም፤ ቅዱስ ጴጥሮስ “በእነዚያ ዘንድ ለማስተዋል የሚያስቸግር ነገር አለ፥ ያልተማሩትና የማይጸኑትም ሰዎች ሌሎችን መጻሕፍት እንደሚያጣምሙ እነዚህን ደግሞ ለገዛ ጥፋታቸው ያጣምማሉ” እንዲል (2ጴጥ. 3፥16)።

Monday 21 November 2022

ተሐድሶን ለማጥፋት መወሰድ ያለባቸው ርምጃዎች! (የመጨረሻ ክፍል)

Please read in PDF

2.  የተሐድሶን ጥያቄዎች መቀበል

የተሐድሶን ጥያቄዎች በደፈናው ከመቃወምና አገልጋዮችን ከማውገዝ ይልቅ፣ በቅንነትና በእግዚአብሔር ቃል መሰረት መዝኖ ጥያቄዎችን መቀበል ተሐድሶን ለማጥፋት የመጀመሪያ ርምጃ ነው። ይህም ርምጃ ምናልባት በአገልጋዮች እውቀትና ልምድ ማነስ ምክንያት ሊከሰት የሚችለውን ከተሐድሶ ዓላማ ጋር የማይሄድ ችግር ለማስቀረትና ሙሉ ለሙሉ በተሻለ አቅም ተሐድሶን ለመምራት ያስችላል።

ተሐድሶን አልፈልገውም ተብሎ አይካድም፤ ምክንያቱም ተሐድሶ በራሱ መንገድ የእግዚአብሔር ቃል በተነገረበት፣ የእግዚአብሔር ስም በተጠራበት እንዲሁም የእግዚአብሔር መንፈስ በሚሠራበት ቦታ ኹሉ የሚከሠት እንቅስቃሴ እንጂ ልናስቀረው የምንችለው ጉዳይ አይደለምና።

Sunday 20 November 2022

ተሐድሶን ለማጥፋት መወሰድ ያለባቸው ርምጃዎች! (ክፍል 1)

በእግዚአብሔር ቃልና በእግዚአብሔር መንፈስ ተፈጥሮ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደ ሰደድ እሳት እየተቀጣጠለ ያለውን ተሐድሶን ለማጥፋት እንዴት ይቻላል? የሚለው ጥያቄ፣ የብዙ ዓመታት ጥያቄ ነው፤ ከታሪክም ኾነ በዚህ ዘመን እየኾነ ካለው እውነታ እንደምንረዳው አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናትና ግለሰቦች ተሐድሶ እንዲጠፋ ይፈልጋሉ፤ ነገር ግን እንዴት ሊያጠፉት እንደሚችሉ አያውቁም። ለምሳሌ፦ በአገራችን ታሪክ በአባ እስጢፋኖስና በተከታዮቹ ደቂቀ እስጢፋኖስ ላይ በኢትዮጵያውያን ነገሥታትና ጳጳሳት በተለይም በዐጼ ዘርዓ ያዕቆብ የተፈጸመውን ግፍ፣ ከአውሮፓ ታሪክም በአሥራ ስድስተኛው ክፍለ ዘመን በተነሣው የተሐድሶ እንቅስቃሴ ላይ ከካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የተደረገውን ተቃውሞ ማንሳት ይቻላል።

Saturday 5 November 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፳፪)

 Please read in PDF

ምጽዋት የናቡከደነጾርን በደል ደመሰሰን?

1.1.3. “… ልዑሉም በሰዎች መንግሥት ላይ እንዲሠለጥን፥ ለሚወድደውም እንዲሰጠው እስክታውቅ ድረስ ከሰዎች ተለይተህ ትሰደዳለህ፥ መኖሪያህም ከምድር አራዊት ጋር ይሆናል፥ እንደ በሬም ሣር ትበላ ዘንድ ትገደዳለህ፥ በሰማይም ጠል ትረሰርሳለህ፥ ሰባት ዘመናትም ያልፉብሃል። የዛፉንም ጉቶ ይተዉት ዘንድ ማዘዙ፥ ሥልጣን ከሰማያት እንደ ሆነ ካወቅህ በኋላ መንግሥትህ ይቆይልሃል። ንጉሥ ሆይ፥ ስለዚህ ምናልባት የደኅንነትህ ዘመን ይረዝም እንደ ሆነ ምክሬ ደስ ያሰኝህ፤ ኃጢአትህንም በጽድቅ፥ በደልህንም ለድሆች በመመጽወት አስቀር። ይህ ሁሉ በንጉሡ በናቡከደነፆር ላይ ደረሰ።” (ዳን. 4፥25-28)።

Saturday 29 October 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፳፩)

 Please read in PDF

የመድሎተ “ጽድቅ” ጸሐፊ፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ሥልጣን በግልጥ በመቃወም፣ ሌሎችን መጻሕፍት ከቅዱሳት መጻሕፍት ጋር ለማስተካከል የሄደበትን ሩቅ መንገድና እንዲሁም ቅዱሳት መጻሕፍትን አጥምሞ ወይም የመጽሐፍ ቅዱስ ቃላትን እንደ ገና በመተርጐም በመጽሐፉ ውስጥ እንዴት እንዳስገባ በጥቂቱ በማሳየት፣ ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣን ያለንን ዐሳብ እንቋጫለን፤ የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣንን ከተቃወመባቸው ወይም ከሻረባቸው መንገዶች ጥቂቶቹን እናንሳ፦

1.   ያላለውን እንዳለ አድርጎ በማቅረብ፦ የመጽሐፍ ቅዱስን ሥልጣን የሚቃወሙ አካላት ከሚፈጽሟቸው ግልጽ ስህተቶች አንዱ፣ የመጽሐፉን ዐውድ በመጣስ ያልተናገረውን እንደ ተናገረ አድርጐ ማቅረብ ነው። የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊ በዚህ ረገድ ለምሳሌ፦

Thursday 20 October 2022

ተሐድሶ፣ በማኅበረ ቅዱሳን አደባባይ!

 

ስለ “አጥማቂ” ግርማ ወንድሙ፣ በተደጋጋሚ ጠንቋ ይነቱን፣ በመቍጠሪያ ላይ ባስደገመው ድግምት እንደሚሠራና ሰዎችን ማሳበድ እስከሚያደርስ በሽታ ላይ እንደሚጥል በተደጋጋሚ ጽፈናል፤ አስጠንቅቀናል። ነገር ግን የዚያኔ አሰምተን ጮኸን ስንናገር እኛን እንደ መና ፍቅና ሐሰተኛ እንጂ ማንም “አሜን” ብሎ ሊቀበለን የወደደ አልነበረም።

Tuesday 11 October 2022

“ባዕዱ ወንጌል 2”ና ግለ ምልከታዬ!

Please read in PDF

ባዕድ 2 - ሌላ ኢየሱስ (የሐሰተኛ አስተማሪዎች ኢየሱስ - በቅዱስ ቃሉ ሲፈተሽ) ወይም “Baed Documentary Film” የሚለውን ዘጋቢ ፊልም ተመልክቼዋለሁ። የብልጽግና ወንጌል ለእውነተኛዪይቱ ቤተ ክርስቲያን ፈተናና ከባድ ተግዳሮት ሊኾን እንደሚችል ጥያቄ የሚያስነሳ ጉዳይ አይደለም። በዚህ ረገድ እኔም የድርሻዬን ለመወጣት በ2010 ዓ.ም “የእምነት እንቅስቃሴ - የዛሬዪቱ ቤተ ክርስቲያን ፈተና” በሚል ርዕስ፣ የእንቅስቃሴውን አደገኛነትና በተለይም በተሐድሶአውያን መካከል በነበጋሻው ደሳለኝ አማካይነት ማቆጥቆጡን ተመልክቼ ተቃውሜ ጽፌአለሁ።

Friday 7 October 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፳)

Please read in PDF

ከያዝነው ርዕስ ጋር በሚስማማ መልኩ፣ የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊ፣ ሮሜ 8፥34ን ለመተርጐም በተጠቀመበት መግቢያ ላይ እንዲህ ይላል፤

“በአዲስ ኪዳን የተጻፉ መጸሕፍት ኹለት ነገሮችን ታሳቢ ማድረግ አለባቸው። መጽሐፍ ቅዱስን የምትተረጕመው ቤተ ክርስቲያን ናት። መጽሐፉ ይህ ነው ብላም ለይታ፤ ሰፍራ፤ ቈጥራ የሰጠችውም ቤተ ክርስቲያን ናት። ቤተ ክርስቲያን ናት መጽሐፍ ቅዱስን የሠራችው እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን አልሠራም።”[1]

እንግዲህ አስቀድመን እንደ ተናገርን፣ ይህ የ“መድሎተ ጽድቅ” አቋም ወይም አስተምኅሮ የካቶሊክ እንጂ የኦርቶዶክሳውያን አቋም አይደለም። ጸሐፊው ግን የካቶሊክን አስተምኅሮና እምነት በግልጥ እንደ ኦርቶዶክስ አስተምኅሮ ሲያቀርብ እንመለከተዋለን። ይህን ግልጥ መስመር መለየት ባልቻለበት ኹኔታ፣ ማለትም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሥልጣንን ከቤተ ክርስቲያን አሳንሶ ማቅረብ፣ መድሎተ ስሑትነቱን  በግልጥ ያሳያል።

Sunday 2 October 2022

አእመረ አሸብርና ብልጠታዊ ቋንቋው!

 Please read in PDF

አእመረ አሸብር፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቲቪ ላይ ያደረገውን የክፍል አንዱን ቃለ መጠይቁን አድምጬዋለሁ። እጅግ ሊደንቀኝ በሚችል መልኩ፣ ቃለ መጠይቁን ያደረገው ሰው ደጋግሞ ላነሳቸው ግልጽ ጥያቄ አእመረ አለመመለሱ ሳይኾን፣ ጠያቂው ጨርሶ ለማመን አለመቻሉ፣ ከአእመረ ይልቅ ጠያቂውን እንዳምነው ግድ ብሎኛል።

Friday 30 September 2022

Dubbi Ateetee warra Waaqefannaa Gabaabinaan!

 

“ Waaqtaanummaa – Waaqefannaa fi Kiristaanummaan maal waliif ta’u? mata duree jedhuun kitaaba dhiyootti maxxansiisu irraa kan fudhatame.

“… Ateeteen mallattoo ykn mallattoo aadaa qofaati yaada jedhu irraa ni darba. Hawaasa Oromoo keessatti dhugummaa hawaasichaatiin alatti mallattoo  waaqefachuus ni qaba.[1] Ateeteen mallattoo firii, hortee, kabaja haadhummaa ti. Ateetee dubartiin takka kabaja olaantummaa hafuuraa keessatti kenna fudhatamummaa hortee kan kennituu dha.  Humna nageenya waaqummaa dubarti,[2] ykn ayyaana dubartootaa fi[3] waggootti yeroo tokko kan kabajamtu yoo ta’u; sababni kabajaas gadaamessaa fi eebba firii gadaameessaa (goddess of fertility) waaq eebbistu jedhamee ti.[4] Dubartootnis ateeteedhan waa’e fayyaa fi hortee ni kadhatu.

የዋቄፈና ነገረ አቴቴ በአጭሩ!

 Please read in PDF

“ዋቄስትና - ዋቄፈናና ክርስትና ምንና ምን ናቸው?” ከሚለውና በቅርብ ከሚታተመው መጽሐፌ የተወሰደ!

“… አቴቴ ለምልክትነት ወይም የባህሉ ምልክት ብቻ ከመኾን ያልፋል፤ በኦሮሞ ማኅበረ ሰብ ዘንድ ከማኅበራዊ እውነታነቱ ባሻገር አምልኮአዊ ምልከታዎች አሉት።[1] አቴቴ የፍሬያማነት፣ የወላድነት፣ የእናትነት ክብር መገለጫ ናት። አቴቴ ሴት ልጅ በመንፈሳዊ ልዕልናና ክብር ውስጥ የመውለድን ሞገስ እንድታገኝ ጸጋ የምትሰጥ ናት። ሰላማዊ የሴት መለኮት ኃይል[2] ወይም የሴቶች መንፈስና[3] በዓመት አንድ ጊዜ የምትከበር ሲኾን፣ የመከበርዋም ምክንያት የማኅፀንና የፅንስ ባርኮትን (goddess of fertility) ባራኪ አማልክት ናት ተብሎ ነው።[4] ሴቶችም አቴቴን ስለ ጤናና ስለ መውለድ ይለማመናሉ።

Monday 26 September 2022

ከዕጸ መስቀሉ ወደ ተሰቀለው ፊታችሁን አቅኑ!

Please read in PDF

በዚህ ሳምንት ከሚከበሩት በአላት አንዱ፣ ጌታችን ኢየሱስ ተሰቅሎበታል የተባለው፣ የዕጸ መስቀሉ በአል ነው። የሚከበርበት ምክንያት በአጭሩ ሲገለጽም፣ አይሁድ በጥላቻ ኢየሱስ የተሰቀለበትን መስቀል ከቆሻሻ መጣያ ቦታ ወስደውት ስለ ቀበሩት፤ ይህን የተቀበለውን መስቀል ከዓመታት በኋላ በአንድ ሰው መሪነት የቆስጠንጢኖስ እናት የኾነችው ከዓመታት ፍለጋ በኋላ፣ የተቀበረውን የእንጨት መስቀል እንዳወጣችና በአሉም ከዚህ ጊዜ ጀምሮ መከበር እንደ ጀመረ ይተረካል።

Saturday 24 September 2022

ጳጳሳት ባሉበት ጉባኤ የሴት አገልግሎት!

 በአንድ ወቅት አቡነ መርሐ ክርስቶስ ባሉበት ጉባኤ፣ አንዲት “ዘማሪ” ስለ ተክለ ሃይማኖት፣ “ባለ ስድስት ክንፉ” ብላ ስትዘምር፣ “ሰውየውን ወፍ አደረገችው” ብለው አሳፍረው አስቀምጠዋታል ይባላል። በርግጥ የአደባባይ ስህተት አደባባይ ላይ መታረም አለበት፤ አግባብም ነው! በዚህ ረገድ አቡነ መርሐ ክርስቶስ ብዙ መልካም ምሳሌነት አላቸው።

Sunday 18 September 2022

“ጳጳስ፣ የማይነቀፍና የአንዲት ሚስት ባል ሊኾን ይገባዋል!”

 Please read in PDF

አባቶቻችን ሐዋርያት በነበሩበት ዘመን ሳይፈቱት የቀረ ችግር፣ ረስተው የተዉት ነገር የለም። በመልእክታቸው ተጽፎ የምናገኘው እምነታቸውን ደግሞም የእምነታችውን ሥርዓት ነው። በእያንዳንዱ ጉዳይ ላይ ውሳኔ ሰጥተዋል። ከእነዚህ ውሳኔዎች አንዱ የጵጵስና ጉዳይ ነው። ጳጳስ መኾን ያለበት ምን ዓይነት ሰው ነው? እኛ የሐዋርያትን ውሳኔ ላለመቀበል ቃላትን በመሰንጠቅ ትርጉምን ማጣመም ውስጥ ካልገባን በስተቀር፣ እውነቱን በቀጥታ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እናገኘዋለን።

ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ መልካምን ሥራ ይመኛል የሚለው ቃል የታመነ ነው። እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊኾን ይገባዋል፤ የማይነቀፍ፥ የአንዲት ሚስት ባል፥ ልከኛ፥ ራሱን የሚገዛ፥ እንደሚገባው የሚሠራ፥ እንግዳ ተቀባይ፥ ለማስተማር የሚበቃ፥ የማይሰክር፥ የማይጨቃጨቅ ነገር ግን ገር የኾነ፥ የማይከራከር፥ ገንዘብን የማይወድ፥ ልጆቹን በጭምትነት ሁሉ እየገዛ የራሱን ቤት በመልካም የሚያስተዳድር፤ ሰው ግን የራሱን ቤት እንዲያስተዳድር ባያውቅ፥ የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን እንዴት ይጠብቃታል?” (1ጢሞ. 3፥1-5)።



Saturday 10 September 2022

በዘመናት የሸመገለው “የሰው ልጅ”!

 Please read in PDF

ከሰማይ በታች ያለው መላለም(መላው ዓለም) አንድ ቀን ወይም በጌታ ቀን፣ በታላቅ ድምጽ፣ በትኵሳትና በመቅለጥ ሊያልፍ ቀን ተቀጥሮለታል፤ መጽሐፍ፣ “በዚያም ቀን ሰማያት በታላቅ ድምፅ ያልፋሉ፥ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኵሳት ይቀልጣል፥ ምድርም በእርስዋም ላይ የተደረገው ሁሉ ይቃጠላል።” እንዲል (2ጴጥ. 3፥10)። ሰማይና ምድር የሚያልፍበት ኹኔታ፣ የሰው ልጆች ኹሉ ሥራ በእግዚአብሔር ፊት የሚመረመርበት ወይም የሚታይበት መንገድ እጅግ አዳጋችና ኹኔታውን ለመግለጥ የሚያስቸግር እንደ ኾነ ይታመናል፤ ለጌታ ግን ኹሉ ይቻላል!

Thursday 1 September 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፲፱)

 Please read in PDF

የመጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣን የእግዚአብሔር የራሱ ሥልጣን ነው ስንል፦

1.   ቃሉ የእግዚአብሔር ነው፦ መጽሐፍ ቅዱስ የእግዚአብሔር ቃል ስለ ኾነ፣ ለቤተ ክርስቲያና መሠረትና ዓምድዋ ነው። ቃሎቹ የእግዚአብሔር ባሕርይ ገንዘብ አድርገዋልና፣ መጽሐፍ ቅዱስ አይለወጥም (ማቴ. 5፥17)፤ ልብን ኹሉ ይመረምራል (ዕብ. 4፥12)፣ ይቀድሳል (ዮሐ. 17፥17)፤ ይፈውሳል (መዝ. 107፥20)።

Sunday 21 August 2022

ስለ ኹለቱ መጻሕፍቴና አዲሱ መጽሐፌ ጥቂት ነገር!


ከአኹን ቀደም ኹለት መጻሕፍት በዕቅበተ እምነት ዙሪያ አሳትሜአለሁ፤ በአጭሩ፣ የመጀመሪያውን መጽሐፍ በአብዛኛው ያሰራጨኹት በማኅበራዊ ሚድያ ለምተዋወቃቸው ወንድምና እህቶች ነበር፤ ነገር ግን ከ2000 ኮፒ ውስጥ መጽሐፉን ለማሳተም ተበድሬ ለመክፈል፣ በዕዳ ካስያዝኩት 800 መጻሕፍት ውጭ፣ ካከፋፈልኩት ከ406 በላይ የሚጠጉት መጻሕፍት ቢሸጡም፣ የተሸጡበት ብር ግን ለእኔ አልደረሰኝም። ኹለተኛው መጽሐፌ ደግሞ ገና በስርጭት ላይ ነው። በጽሑፍ ዓለም አሳትሞ፣ መልሶ ማሰራጨት እጅግ ከባድና ፈታኝ ሥራ ነው።



Wednesday 13 July 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፲፰)

Please read in PDF

ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣን የወንጌላውያን ትምህርት

ከምዕራባውያን መካከል ከካቶሊካውያን በ16ኛው ምዕተ ዓመት የተለዩት ወንጌላውያን፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ሥልጣንና ትውፊት በተመለከተ “Sola Scriptua - መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ” የሚል ጽኑ አቋምን ይዘዋል። መጽሐፍ ቅዱስ ብቻ፣ “እንከን አልባ ለሰው ልጅ ብቸኛው መዳኛና የሕይወታችን መመሪያና የኹሉ ነገር ዳኛ” የሚል አቋምን በውስጡ የያዘና፣ ይህንም ብርቱ ሥልጣን ከመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስነት ያገኘ መኾኑን ሲናገሩ፣

Saturday 9 July 2022

“ራስህን ለካህን አሳይ”፣ ብሉያዊ ወይስ አዲሳዊ?

Please read in PDF

“ኀጢአትን ለካህን ለመናዘዝ ይገባል” ለማለት የሚከራከሩ ሰዎች፣ ከሚጠቅሷቸው ጥቅሶች መካከል ይህ ቀዳሚው ነው። ክፍሉ በቀጥታ እንዲህ ተብሎ በጌታችን ኢየሱስ ተነግሮአል፤ “… ሄደህ ራስህን ለካህን አሳይ፥ ለእነርሱም ምስክር እንዲሆን ሙሴ ያዘዘውን መባ አቅርብ” ጌታችን ኢየሱስ ይህን የተናገረው፣ ከለምጽ ለነጻው ለምጻም ሰው ነው፤ (ማቴ. 8፥4፤ ማር. 1፥44፤ ሉቃ. 5፥14)። ጌታችን ይህን ለምጻም እንዲህ ብሎ ለምን እንዳዘዘው ከመናገር፣ አስቀድሞ አንድ ሰው ለምጽ ሲወጣበት ስለሚደረገው ብሉያዊ ሥርዓት በአግባቡ መረዳት ነገሩን ለማስተዋል እጅግ ይቀላል።

Friday 8 July 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፲፯)

 Please read in PDF

ስለ መጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣን የምሥራቃውያን ትምህርት

የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት የመጽሐፍ ቅዱስን ሥልጣን፣ ከትውፊት ነጥለው ብቻውን በማቆም ሥልጣኑን ይቀበላሉ። ከትውፊት የመነጠላቸውም ምክንያት፣ መጽሐፍ ቅዱስ የትውፊት የበላይና የቤተ ክርስቲያን መመሪያ፣ የኹሉ ነገር መመዘኛ፣ ልዩና የማይገረሰስ ሥልጣንም እንዳለው አምነው ይቀበላሉ።



ከካቶሊክና ከላቲን አብያተ ክርስቲያናት በተለየ መንገድ፣  የምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት መጽሐፍ ቅዱስን ከቤተ ክርስቲያን ትውፊት መነጠላቸውና “ብቻውን በቂና አስተማማኝ” ማለታቸው የሚደንቅ ነው።

Saturday 2 July 2022

በአሜሪካ ለ50 ዓመታት የቆየው የውርጃ ሕግ መሻሩ!

 Please read in PDF

እግዚአብሔር በማናቸውም መንገድ የሰው ልጅ እንዲገደል አይፈልግም። ከታላላቆቹ ሕጎች መካከል አንዱ፣ “አትግደል” የሚለው ሕግ ነው። የሰው ልጆች ደግሞ በተቃራኒው፣ የሰውን ልጅ ለተለያዩ የገቢ ምንጭነትና የዓመጽ ሥራ በብርቱ ጭካኔ ከሚገድሉበት መንገድ አንዱና ዋነኛው፣ ውርጃ ከፊቶቹ ተርታ ይመደባል። ውርጃ በግልጽ በመጽሐፍ ቅዱስ ቢከለከልም፣ ተፈጥሮን የሚቃረን ቢኾንም እጅግ በሚዘገንን መልኩ አያሌ የውርጃ ተግባራት እንዲተገበሩ ብዙ ብሮች ይፈሱበታል፤ ሰዎች ተግባሩን እንዲፈጽሙ በሕግ ጭምር ከለላ ይደረግላቸዋል። ይህን በማድረግ ከሚታወቁት መካከል ግንባር ቀደሟ አሜሪካ አንዷ ናት። እናም ለ50 ዓመታት በሕግ ከለላ ሰጥታ ትፈጽም የነበረውን የውርጃ ሕግ፣ የአሜሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዳኞች ሽረውታል።

Friday 24 June 2022

“ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” (መዝ. 68፥31)

 Please read in PDF

ኢትዮጵያ ቅድስት አገር እንደ ኾነች ለማሳመን፣ ከሚጠቀሱት ጥቅሶች መካከል አንዱ ይህ ጥቅስ ነው። ብዙዎችም በዚህ ጥቅስ በጣም ደስ ይላቸዋል፤ እንዲያውም አንዳንዶች ይህን ጥቅስ በመጥቀስ፣ “ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋ ነበር” ብለው ሲሞግቱ እንሰማቸዋለን። ነገር ግን ጥቅሱ እውን ሰዎች የሚሉትን ይናገራል ወይ? ክፍሉን ብንመረምር ተቃራኒውን ኾኖ እናገኘዋለን።

መግቢያ

Saturday 18 June 2022

“... ከዋነኞቹ አለቆች አንዱ ሚካኤል ሊረዳኝ መጣ፤ ” (ዳን. 10፥13)

Please read in PDF

ይህን ቃል የተናገረው ነቢዩ ዳንኤል አይደለም፤ ከመላእክት መካከል ዕርዳታ ይፈልግ ከነበረ መልአክ መካከል አንዱ ወይም መልአኩ ገብርኤል ነው። የተናገረው ደግሞ ለነቢዩ ዳንኤል ነው። እንዴት?

ነቢዩ ዳንኤል በምዕ. 10፥1 በተመለከተው ታላቅ የጦርነት ራእይ እጅግ አዝኖ አለቀሰ። እናም እንደ አንድ ታላቅ መንፈሳዊ አገልጋይ፣ ያየውን ነገር በእግዚአብሔር ፊት ለማቅረብ፣ ባየው ራእይ ላይ የእግዚአብሔር ፈቃድ ምን እንደ ኾነ ለማወቅ፣ ራሱን ከምግብና ከመጠጥ በመከልከል ሦስት ሳምንታት እስኪፈጸሙ ጾምን ጾመ።

Wednesday 15 June 2022

መዳንም በሌላ በማንም የለም!

 Please read in PDF

·        ዛሬ በኢየሱስ ስም መስበክ ወይም ኢየሱስ ያድናል ማለት መናፍቅ አሰኝቶ ያስወግዛል!

·        ገድለ ተክለ ሃይማኖት ደግሞ፣ የተክለ ሃይማኖትን ስም የጠራ ይድናል ይላል!

 “መዳንም በሌላ በማንም የለም እንድንበት ዘንድ የተሰጠን ከሰማይ በታች ሌላ የለም” (የሐ.ሥ 12፥4)

ይህን ቃል የተናገረው ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ነው። የተናገረውም በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ በቅዱስ ድፍረት ውስጥ ኾኖ ነው። ይህን ቃል ለመናገር ያበቃው ደግሞ፣ ሲወለድ ጀምሮ ሽባ የነበረውን ሰው ከፈወሰ በኋላ ለተነሣው ሙግት ምላሽ ነው። ሰውዬው ለመሥራት ለመሮጥ፣ ለመቅደም፣ ለመታገል የማይችል ምስኪን ሰው ሆኖ፣ በወላጆቹ ላይ ወድቆ የሚኖር ሰው ነበር። ጥዋትና ማታ በቤተ መቅደስ በር ላይ እያመጡ ይጥሉታል፣ ከሕዝብ ምጽዋት እየለመነ የዕለት እንጀራውን ያገኛል። ከዚህ ሕይወት የሚያወጣው ሌላ እድል አያገኝም፣ ተስፋው በሙሉ በሰው ስጦታ ላይ የተመሠረተ ነው። አንድ ቀን በትክክል ቆሜ እራመዳለሁ ብሎ አስቦ አያውቅም፣ የሚያስበው በቀን ምን ያህል ምጽዋት እንደሚያገኝና ኑሮውን እንደሚገፋ ብቻ ነው። በዚህ ሁኔታ ከ40 ዓመት በላይ አሳልፎአል።

Sunday 12 June 2022

መንፈስ ቅዱስና አማኙ

 Please read in PDF

  ከግሪኩ “ፓራክሊቶስ” ወይም ከዕብራይስጡ “ፕራቅሊጥ” ከሚለው ግስ የተገኘው፣ “ጰራቅሊጦስ” የሚለው ቃል ትርጉሙ፦ “አማላጅ፣ አስታራቂ፣ አፍ፣ ጠበቃ፣ ትርጁማን፣ አምጃር፣ እያጣፈጠ የሚናገር፣ ስብቅል ካፉ ማር ጠብ የሚል።…፤ ናዛዚ፣ መጽንዒ፣ መስተፈስሒ፤ መንፈስ ቅዱስ” በማለት አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ተርጉመውታል።[1]

Wednesday 8 June 2022

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፲፮)

 Please read in PDF

የመጽሐፍ ቅዱስ ሥልጣን፣ የራሱ የእግዚአብሔር ሥልጣን ነው!

“የመጽሐፉ ባለቤት ጌታ ራሱ ካልረዳ በስተቀር የቅዱሳት መጻሕፍትን ትርጓሜና ምስክርነት ለመረዳት አይቻልም። መጻሕፍቱ ምንም በሰው እጅ የተጻፉ ቢኾኑ በጌታ ትእዛዝ እንደ ተጻፉ እናምናለን።”[1] 

መግቢያ

ክርስትናም ኾነ የብሉይ ኪዳን እምነት የተመሠረተው፣ በመጽሐፍ ቅዱስ እውነትና ሥልጣን ላይ ነው። እግዚአብሔር ለወደቀው ዓለም፣ ተስፋ መስጠቱን ያረጋገጠበት እውነተኛ ሰነድ መጽሐፍ ቅዱስ ነው። የኦሪት መጻሕፍት የመሰጠታቸው ዓላማ፣ በምድረ በዳ ለነበረችው እስራኤል የተሰጠ አስደናቂ የተስፋና የእምነት መጽሐፍ ነው። የእግዚአብሔር ኹሉን ቻይነትና ታዳጊነት እንዲደገፉበት የተጻፈ መጽሐፍ ነው። ቅዱሱ ፍጥረት፣ ውድቀቱ፣ ተስፋውና ደገፌታው ጭምር በውስጡ መጠቀሱም በዋናነት ይኸንኑ ሊያመለከት አለ።

Thursday 2 June 2022

ዕርገት - ወደ ሄደው ጌታ እንሄዳለን!

 Please read in PDF

የክርስቶስ ኢየሱስ ስቅለትና ሞቱ፣ የኀጢአታችን ዕዳ ፍጹም መከፈሉንና ቤዛችን እኛን ወክሎ መከራ መቀበሉን ያበሥራል፤ ትንሣኤው ደግሞ የዕዳችን ክፍያ ፍጹም መጠናቀቁንና መረጋገጡን የሚያመለክት ታላቅ ደስታችን ነው። ሞቱ ያለ ትንሣኤው ከንቱ ነበረ፤ ትንሣኤው ግን ሞቱን ጽድቃችን አደረገው፤ ከትንሣኤው ኃይልና ሕይወት የተነሣም የጸደቅንና የተቀደስን መኾናችንን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሰክሩልናል፤ “እርሱ[ክርስቶስ] ስለ ኀጢአታችን እንዲሞት ዐልፎ ተሰጠ፤ እኛን ጻድቅ አድርጎ ለማቅረብም ከሞት ተነሣ” እንዲል፤ (ሮሜ 4፥25)።

Monday 16 May 2022

ይድረስ ለየዋሁ ኦርቶዶክሳዊ ወገኔ በሙሉ!

 Please read in PDF

ያ ትሁት ልብ የነበረውና ጽድቅ ፍለጋ ወደ ኢየሩሳሌም የተጓዘው ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ፣ 'የምታነበው ይገባሃልን?' ተብሎ በወንጌላዊው ፊልጶስ ለቀረበለት ጥያቄ የሰጠው መልስ እጅግ ልቤን ይነካኛል። 'የሚያስረዳኝ ሳይኖር እንዴት ይገባኛል?' እኛ ከዚህ እውነተኛና ትሁት ሰው ደም ምንድነው የወረስነው? ከራሳችን ሰዎች እንዳንማር ተረግመን ይኾንን? ''በታሪካችን ውስጥ አንዳንድ ፋና ወጊ ወገኖቻችን ሃገርን የሚጠቅም እውነት ይዘው ብቅ ሲሉ ማጥፋቱን ተክነንበታል። (ምሳሌ፦ እነ ደቂቀ እስጢፋኖስን)። ለዚህ ነው በሥልጣኔ በር ላይ ቀድመን ደርሰን በመገተራችን፣ ሌሎች ከኋላ እየመጡ ቀድመውን የገቡት'' በማለት ፕሮፌሰር መስፍን በሕግ አምላክ ደቂቀ እስጢፋኖስ በሚለው የፕ/ር ጌታቸው መጽሐፍ ላይ የተናገሩት። 

Thursday 5 May 2022

መንትዮቹ፤ መስቀሉና ትንሣኤው!

 Please read in PDF

በሰሙነ ሕማማቱና በትንሣኤው ወቅት የነበረውን እውነት ካሰላሰለ በኋላ፣ ጴጥሮስ ክርስቶሎጎስ የተባለ አንድ አባት እንዲህ ብሎአል፤ “ሴቶቹ የክርስቶስን ትንሣኤ ለማክበር ቀዳሚዎች ናቸው፤ ደቀመዛሙርቱ ደግሞ ስለ ክርስቶስ መከራን ለመቀበል የመጀመሪያዎች ኾኑ። ሴቶቹ ሥጋውን ሽቱ ለመቀባት አዘጋጁ፤ ደቀ መዛሙርቱ ደግሞ ለቅጣት መሣሪያዎች ሰውነታቸው አዘጋጁ። ሴቶቹ ወደ መቃብር ገቡ፤ ደቀ መዛሙርቱም ከጥቂት ጊዜ በኋላ ወደ እስር ቤት ሊገቡ ነው። ሴቶቹ ምስክርነታቸውን ለመግለጽ የተፋጠኑ ኾነዋል፤ ደቀ መዛሙርቱም ስለ እርሱ የሰንሰለት እስራትን ለመቀበል የማይፈሩ ኾነዋል።” ብሎአል።



Friday 22 April 2022

የኢየሱስን እንጂ የቆስጠንጢኖስን መስቀል አልወደውም!

 Please read in PDF

መስቀል የክርስትና ማዕከልና ዋና ትምህርት ነው። ያለ መስቀሉ ክርስትና ክብር አልባ ትምህርት፣ ሕይወት አልባ ጉዞ ነው። መስቀሉን ማዕከል ያላደረገ ክርስትና፣ ከውኃ የወጣ ዓሳ ያህል አንዳች ትርጕም የለውም። ከውድቀት ዘመን ጀምሮ፣ የሰው ልጆች “የእግዚአብሔር ጠላትና ለእግዚአብሔር ሕግ የማይታዘዙ፣ ለመገዛትም የማይፈቅዱ” የነበሩትን ያህል (ሮሜ 8፥7)፣ እንዲታዘዙና እንዲመለሱ፣ በሕይወትም እንዲኖሩ ጥሪ የቀረበላቸው፣ በታረደውና በመስቀሉ ላይ በተሰቀለው ጌታ “አባት ሆይ፥ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” (ሉቃ. 23፥34) በሚለው፣ የመስቀል ላይ የጣዕር ድምጽ ነው።

Wednesday 20 April 2022

ስለ ወገኔ እንዲህ ብጸልይስ?

 Please read in PDF

ጌታና ቸር የኾንክ አባት ሆይ፤ በአገራችን ላይ ጦርነት እንዳለ፣ ዛሬም ድረስ ሰቆቃው ገና እንዳላበቃ፣ ምጡ እንዳልባጀ፣ ጭንቀቱ እንዳልሰከነ...  ታውቃለህ፤ ደግሞም ይህ ጦርነት የአንድ አገር ሰዎች ኾነን፣ ነገር ግን መዋደድ ተስኖን፣ መፈቃቀር አቅቶን፣ መቀባበል ባንችልበት ነውና እባክህን ትግራዮችንም፤ አማራዎችንም፤ ኦሮሞዎችንም፣ ቤኒሻንጉልንም፣ አፋርንም፣ ሶማሌንም … በጥይት እሩምታ ፍጃቸው፤ በአዳፍኔና በባዙቃ አደባያቸው፤ በጦርና በገጀራ አስወግዳቸው። ነገር ግን ስለ ቅዱሱ ስምህ፣ ስለ ተወደደው አባታዊ ርኅራኄህ ሕፃናቱ አይነኩ፤ ሴቶቹ አይበደሉ፤ አረጋውያኑ አይባዝኑ፣ ባልቴቶቹ አይቅበዝበዙ፤ አካል ጉዳተኞቹ አይሰቀቁ፤ አሮጊቶቹ በበጎ ይታሰቡ፤ ወጣቶቹ በቁመታቸው ልክ አይጋደሙ።

Sunday 17 April 2022

የኛ ዘመን አማኝ!

 Please read in PDF

ገበታ ዘርግተው ርግብ ሚሸቅጡ

የመሥዋዕቱን ዋጋ በብር ሚለውጡ

ጨካኝ ነጋዴዎች የነፍስ ደላሎች

አቅናን እባክህን!

 Please read in PDF

ይገባሃል ክብር መባል ሆሳዕና

ከመስቀሉ ስትሸሽ አልታየኽምና

Monday 11 April 2022

እግዚአብሔር፣ ማርያምን ፈርቶ?!

 Please read in PDF

እግዚአብሔር አምላክ እጅግ የተፈራ አምላክ ነው፤ ቅዱሳት መጻሕፍት ስለ መፈራቱ እንዲህ ይመሰክራሉ፤

   በምስጋና የተፈራህ፥ ድንቅንም የምታደርግ፥ በቅድስና የከበረ እንዳንተ ያለ ማን ነው?” (ዘጸ. 15፥11)

      ስሙ የተቀደሰና የተፈራ ነው።” (መዝ. 111፥9)

እግዚአብሔርን መፍራት የጥበብ ኹሉ መጀመሪያ ነው፤ ደግሞም እግዚአብሔርን መፍራት ከኹሉ ነገር ያወጣል፤ አማኝ በመታመኑም ከኹሉ ነገር ይጠበቃል፤ በሰላምም ይኖራል፤ (ምሳ. 1፥7፤ መክ. 7፥18)፤ ነገር ግን ሰውን ወይም ፍጡርን መፍራት ወጥመድን ያመጣል (ምሳ. 29፥25)። ሰዎችን ስንፈራቸው ሕይወታችንን እስከ መቆጣጠር ይደርሳሉ፤ እናም በኹለንተናችን በእነርሱ አስተያየትና አረማመድ ውስጥ እንድንዘፈቅ ፍጹም በመጫን ያጠምዱናል። እግዚአብሔርን መፍራት ግን ምንም ወጥመድ የለበትም፤ ሳኦል ከእግዚአብሔር ይልቅ ሰውን በመፍራቱ ምክንያት፣ ከንግሥና ዙፋኑ የሚያዋርደውን ታላቅ ስህተት ሠራ፤ “ሳኦልም ሳሙኤልን፦ ሕዝቡን ስለ ፈራሁ፥ ቃላቸውንም ስለ ሰማሁ የእግዚአብሔርን ትእዛዝና የአንተን ቃል በመተላለፍ በድያለሁ።” (1ሳሙ. 15፥24) እንዲል።

Tuesday 29 March 2022

ማራን አታ!

 Please read in PDF

“ማራናታ” የሚለውን ቃል፣ ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማኹት፣ በ20/7/1995 ዓ.ም በከሰዓት መርሐ ግብር፣ በሻሸመኔ ከተማ በቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በተደረገ ጉባኤ ላይ [ያኔ ይህን ጉባኤ ለመታደም ከአርሲ ነጌሌ፣ ሻሸመኔ ድረስ በእግራችን ነበር የምንሄደው] ከመምህር ይልማ ቸርነት አንደበት ነው። በዕለቱ መምህሩ፣ በዘፍጥ. 3፥10 ላይ ያለውን ኃይለ ቃል አንስቶ አስተምሮ፣ ትምህርቱን ሲያሳርግ፣ “ማራናታ” የሚለውን ቃል ሲናገር፣ ትርጉሙ ባይገባኝም፣ ቃሉ በልቤ መካከል ተሰንቅሮ ከብዙ ጥያቄዎች ጋር በውስጤ ቀረ። በጊዜው መምህሩን አጊኝቼ ትርጕሙን ለመጠየቅ ዕድል ባላገኝም፣ በተደጋጋሚ ብዙ ሰዎችን ጠይቄ የመለሰልኝ ሰው ግን አልነበረም።

Saturday 26 March 2022

የካውንስሉ የማይቀር መንገዳገድ!

 Please read in PDF

ቅዱስ ቃሉ፣ “በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ።” (ኤፌ. 4፥3) እንዲል፣ ቤተ ክርስቲያን ከምንም ነገር ይልቅ መጠንቀቅ ያለባት ለመንፈስ አንድነትዋ ነው። መሲሑ በሊቀ ካህናትነት በጸለየውም ጸሎትም፣ “ቅዱስ አባት ሆይ፥ እነዚህን የሰጠኸኝን እንደ እኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው።” (ዮሐ. 17፥11) የሚል ነው። ሰይጣን፣ ቤተ ክርስቲያንን ከሚፈትንበትና ድል ከሚያደርግበት አንዱና ዋናው መንገዱ፣ መለያየት፣ መከፋፈል፣ ክፉ የልዩነትን ዘር በመዝራት ነው። “አንድ ቤተሰብ እርስ በእርሱ ከተለያየ ጸንቶ መኖር አይችልም” እንዲል (ማር. 3፥25)።

Wednesday 23 March 2022

ይድረስ ለፓስተር ቸሬ!

 Please read in PDF

“ኢየሱስን መንፈስ ቅዱስ ብቻ እንጂ ሥጋና ደም አይገልጠውም!”

“ኦርቶዶክሶች ማርያም ካለቻቸው እንዴት ኢየሱስ የላቸውም ብለህ አሰብህ? … ።” (ከፓስተር ቸሬ ንግግር የተወሰደ)

ፓስተር ቸሬ፣ “ኤጳፍራ ቤተ ክርስቲያን” በሚባል ከወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት በአንዱ፣ የሚያገለግል አገልጋይ ነው። አገልጋዩ በትዳር እንዲሁም ተያያዥ ጉዳዮችና በስህተት መምህራን ላይ በሚናገራቸው ንግግሮቹ በአብዛኛው ይታወቃል። እኔም በበኩሌ የተወሰኑ ትምህርቶቹን ለመከታተል ጥረት አድርጌ፣ በተወሰነ መንገድ ተጠቅሜበታለሁ። አገልጋዩ በትዳር ጉዳዮች ላይ ባለው ትምህርቱ ቢቀጥል፣ እጅግ ትርፋማ ይኾናል ብዬም ገምታለሁ። ከሰሞኑ ግን “ለኦርቶዶክሳውያን ወንጌል መሰበክ የለበትም፤ ያውቁታል” የሚል መልእክት ያለው ንግግር ማሰማቱን ሰምቼ ይህን ለመጻፍ ተገደድሁ።

Sunday 20 March 2022

የጌታ ያልኾኑ የጌታ ነበርን ባዮች!

 Please read in PDF

የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ፣ “ተሐድሶ ወይም ሐድሶ” የአንድ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እንቅስቃሴ፣ በመኾኑ እንጂ፣ የአንድ ወይም የተለዩ አካላት መጠሪያ በመኾኑ አያምንም። አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፦ “ሐድሶ ማለት ማደስ፤ መለወጥ፤ ሐዲስ ማድረግ፤ ማጥናት ማበርታት፤ መሥራት መጠገን፤ ያሮጌ የሰባራ።” በማለት ተርጉመው፣ “ሐዳሲ ወይም ሐዳስያን ማለት ደግሞ፣ የሚያድስ የሚጠግን፤ ወጌሻ፤ ገንቢ፤ ዐናጢ” ብለው፣ ውጤቱን ደግሞ፣ “ተሐደሰ፤ ታደሰ፣ ተለወጠ፤ ዐዲስ ኾነ” በማለት በግልጥ የተረጐሙትን ትርጒም ታሳቢ በማድረግ፣ “ሐዳሲ ወይም ሐዳስያን” የሚለውን ቃል ይጠቀማል።

ሐዳሲነት፣ ጤናማ ትምህርትና ሕይወት ይፈልጋል!

Friday 18 March 2022

ምኩራቡ!

Please read in PDF 

ቅዱሳት መጻሕፍት የሚነበቡበት

የሚፈከሩበት የሚሰበኩበት

ምኩራቡ ነበረ ውብ ዓውደ ምሕረት

Wednesday 16 March 2022

“የሎጥን ሚስት አስታውሱ” (ሉቃ. 17፥32)

 Please read in PDF

ስለ ኢየሱስ ብዙ ተናግሬአለሁ፤ ከእንግዲህ ስለ ማርያም በመናገር ዘመኔን አሳልፋለሁ” (ወደ ኦርቶዶክስ ከተመለሱት አንዱ የተናገረው)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ወደ ኋላ ስለ መመለስ ጠቅሶ ከተናገራቸው ምሳሌዎች አንዱ፣ ወደ ኋላ በመመለስዋ ምክንያት፣ የጨው ሃውልት የኾነችውን የሎጥን ሚስት በመጥቀስ ነው። የሎጥን ሚስት በምሳሌነት ከማንሳቱ ጋር አያይዞ፣ እንዲህ የሚል ምሳሌም አብሮ ተናግሮአል፤ “በቤቱ ጣራ ላይ ያለ ማንም ሰው በቤቱ ውስጥ ያለውን ንብረት ለመውሰድ አይውረድ፤ እንዲሁም በእርሻ ቦታ ያለ ሰው ወደ ኋላው አይመለስ።” ይላል። ጌታችን ይህን ምሳሌ ጠቅሶ ባስተማረበት ቦታ የነበሩ ሰዎች፣ በከፍተኛ ሙቀት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች በመኾናቸው፣ የቤቶቻቸው ጣራ ክፍትና ለመዝናናት ምቹ እንዲኾን ተደርጎ የተሠራ ነበር።

Thursday 10 March 2022

ጾም ለአዲሱ ሰው

 Please read in PDF

በድጋሚ፣ በቅድስና እየጾማችሁ ላላችሁ፣ እንኳን ለዐቢይ ጾም በሰላም አደረሳችሁ!!! ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምድር ላይ እየተመላለሰ በሚያስተምርበት ወቅት፣ የመጥምቁ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ቀርበው፦ “እኛና ፈሪሳውያን ብዙ ጊዜ የምንጦመው ደቀ መዛሙርት ግን የማይጦሙት ስለ ምንድር ነው? አሉት” (ማቴ. 9፥14)፡፡ እነዚህ የዮሐንስ ደቀመዛሙርት፣ መጾማቸው መልካም ነበር። በጾማቸው ውስጥ ግን የሚያዩት እግዚአብሔርን ሳይኾን፣ የሌሎችን አለመጾም ነበር። ስለዚህ ጾማቸው፣ “በክስ የተሞላ ሥነ ሥርዓትን” ብቻ ያሟላ እንጂ የልብ መሠበር፣ የንስሐ መንፈስ፣ ፍቅር የነበረው አልነበረም። ጾማቸውን ለሃይማኖታዊ ውድድር ወይም ውርርድ አውለውታል። ስለዚህ መልስና እርካታ ያለው አልነበረም። ጾም ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝበት መንፈሳዊ መስመር፤ ቅዱስም ተግባር ነው።