Thursday 28 December 2017

የማይለወጠው ዥንጉርጉሩ ነብርና የኢትዮጲያዊ መልክ

 ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስ፦ “በውኑ ኢትዮጵያዊ መልኩን ወይስ ነብር ዝንጕርጕርነትን ይለውጥ ዘንድ ይችላልን? በዚያን ጊዜ ክፋትን የለመዳችሁ እናንተ ደግሞ በጎ ለማድረግ ትችላላችሁ፡፡” (ኤር.13፥23) በማለት፣ ስለይሁዳ ኃጢአት በከባድ ወቀሳ ይናገራል፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ ይሁዳ ተጠራርጋ በእግዚአብሔር ፍርድ ልትጠፋ እንዳለች በእግዚአብሔር ስለተረዳ፣ ሚስትን ከማግባትና ልጆችንም ከመውለድ ተከልክሏል፤ (ኤር.16፥1-4)፡፡ ትዳር ብቻም ሳይኾን ወዳጆቹም እጅግ ጥቂቶች ነበሩ፤ አኪቃም (26፥24)፣ የአኪቃም ልጅ ጎዶልያስና (39፥14) ኢትዮጲያዊው አቤሜልክ ናቸው (38፥7)፤ የክፋቱ ጠጣርነት ከሰው በብዙ ስላገለለው ረጅም ዘመኑን ያሳለፈው በሐዘን ነው፡፡
     የይሁዳ ኃጢአቶች የተገለጡና ለኹሉ የታዩ ነበሩ፤ “ይሰርቃሉ፥ ይገድላሉ፥ ያመነዝራሉ፥ በሐሰትም ይምላሉ፥ መጻተኛውንና ድሀ አደጉን መበለቲቱንም ይገፋሉ፥ በቅዱሱም ስፍራ ንጹሕ ደምን ያፈስሳሉ፥ ስሙም በተጠራበት በቤተ መቅደሱ በፊቱ ቆመው፦ ይህን አስጸያፊ የሆነ ነገርን ሁሉ አላደረግንም ብለው ይክዳሉ፣ ስሙ የተጠራበት ቤት በዓይናቸው ፊት የሌቦች ዋሻ አደረጉት፣ የቀደሙት አባቶቻቸው እግዚአብሔርን ተዉ፣ አመነዘሩ፣ አማልክት ያልሆኑትን ለራሳቸው አማልክትን አድርገው፣ ሌሎችንም አማልክት ተከተሉ አመለኩአቸውም ሰገዱላቸውም፥ ያስቈጡትም ዘንድ በሰገነታቸው ላይ ለበኣል አጠኑ፥ ለሌሎችም አማልክት የመጠጥን ቍርባን አፈሰሱ፣ ሕጉንም አልጠበቁም፤ እንዲኹም እነርሱም ከአባቶቻቸው ይልቅ ክፉ አድርገዋል፤ እነሆም፥ ሁላቸውም እንደ ክፉ ልባቸው እልከኝነት ሄደዋል እርሱንም አልሰሙትም” (7፥1-11፤ 16፥11፤ 20፤ 22፥9፤ 23፥10፤ 32፥29፤ 44፥2፤ 23)፡፡ በዚህ ኃጢአታቸው እግዚአብሔርን ፈጽመው አስቆጥተውታል፡፡

Tuesday 26 December 2017

በጋሻው “አፍንጫው ሲነካ[ስሙ ሲነሣ]፣ ዓይናችኹ ላላቀሰ” ኹሉ!



Please read in PDF
    በግልጽ አንድ ያልተግባባነው ነገር አለ፤ የሐሰት ትምህርትን መቃወምና የሐሰት መምህራንን አለመቀበል የወንጌል ልብ አለመያዝ ወይም በወንድም ላይ መፍረድ ማለት አይደለም፡፡ ለበጋሻው ሳልራራለት ቀርቼ አልነበረም የሐሰት ትምህርቱን የተቃወምኩት፡፡ “አንዳንዶች ተከራካሪዎችንም ውቀሱ፥ አንዳንዶችንም ከእሳት ነጥቃችሁ አድኑ፥ አንዳንዶችንም በሥጋ የረከሰውን ልብስ እንኳ እየጠላችሁ በፍርሃት ማሩ፤” (ይሁ.22-23) የሚለውን የቅዱስ ይሁዳ ቃልም ፈጽሞ ጠፍቶኝ ወይም ተዘንግቶኝ አይደለም፡፡
  ብናስተውል፣ የሐሰት ትምህርትን እንደቃሉ መቃወም እውነተኛ አማንያን እንዲጠበቁና እንዲጠነቀቁ ማድረግ ብቻ ሳይኾን፣ ሐሰተኛውን መምህር እንዲመለስ ተግሳጻዊ በኾነ መንገድ “የመማጸንም ሥራ” ነው፡፡ ትምህርቱን ስንቃወም ሰውየውን[የሐሰት አስተማሪውን] ከመጥላት ጋር አይደለምና፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በቆሮንቶስ የነበረውን የታወቀውን አመንዝራ ሰው፣ “ … እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው” ሲል፣ ከጥላቻና መዳኑን ካለመፈለግ አንጻር ሳይኾን፣ “  መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ” ነው፤ (1ቆሮ.5፥5)፡፡

Monday 11 December 2017

Thursday 7 December 2017

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፮


Please read in PDF
የእምነት ቃል አገልጋዮች የሰውን ሰው-ነት ለመካድ የሚጠቅሷቸው ጥቅሶች
   መጽሐፍ ቅዱስ ሰው ሥጋም መኾኑን ቢናገርም፣ የቃል እምነት አገልጋዮች ግን ይህን እውነት ከዓውድ ውጪ አጥምመው “ሰው መንፈስ ነው ለማለት” የሚጠቅሷቸው ጥቅሶች አሏቸው፡፡ ዋና ዋናዎቹን ከዚህ በታች እያነሣን፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሽ እንሰጥበታለን፡፡
·        ፍ.1፥26-27 እና 2፥7፦ እኒህን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በባለፉት ጊዜያት በተደጋጋሚ ተመልክተናልና የቀደሙትን ክፍሎች እንድትመለከቱ በመጋበዝ አልፌዋለሁ፡፡ “ሰዎቹ” ሰውን “መንፈስ ነው” ለማለት ከሚጠቅሷቸው ጥቅሶች መካከል መኾናቸውን ግን ማስታወስ እወዳለሁ፡፡
·        ሐ.3፥1-13፦ ሰውን አመናፋሾቹ የሐሰት መምህራን ከዘፍጥረት መጽሐፍ ቀጥለው የሚንደረደሩት ወደዚህ የቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል ክፍል ነው፡፡ እንግዲህ ቅዱሳን መጻሕፍትን በየዓውዳቸው ለማያጠና ተማሪ፣ “እምነትና በጎ ሕሊናውን ያስጥሉታል፥ መርከብ አለ መሪ እንደሚጠፋ፥ በእምነት ነገር እንዲጠፋ ያደርጉታል፤” (1ጢሞ.1፥19)፡፡ ስለዚህ “ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ እንደማይችሉ ሞኞች ሴቶች፣ ከተነዳላቸው ወደየሞት ወጥመዳቸው ሰተት አድርገው ያስገቡታል፤ እኛ ግን ስለምንሰማው ነገር ልንጠነቀቅ፤ ባለማስተዋልም ልንዘለል አይገባንም፤ (2ጢሞ.3፥6-7)፡፡

Monday 4 December 2017

መልዐከ መዊዕ አባ የማነ ብርሐን ካሳሁን አፈርንሎት!

Please read in PDF

      በቀን 24/3/10 8:30 ገደማ በሻሸመኔ ከተማ ማኅበረ ኢየሱስ ባዘጋጀው ጉባኤ ላይ ቀሚሳቸውን ለብሰው መስቀላቸውን ጨብጠው እንደጉባኤው እድምተኛ ከሌሎች ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና ሰንበት ተማሪዎች ጋር በመኾን ልክ ጸሎት በሚጀመርበት ሰዓት ዱላና ድንጋይ አስጨብጠው ወደመድረኩ በመውጣት የያዙትን መስቀል ወደኪስዎ ከትተው ድብደባ ባርከው በማስጀመርዎ አፈርንሎት!

      እርስዎን የማውቅዎ 2004 . እኔ በወንጌል ጉዳይ ተከስሼ በእርስዎ ፊት ቀርቤ በብዙ ጩኸት ይከሱኝ ከነበሩት ከሳሾች በተሻለ ለዘብተኝነት ሲናገሩ ሰምቼዎ ነበር፤ የዚያኔ ጌታ ልብዎን "ለወንጌል አለዝቦ የሥጋ ልብ" እንዲያደርግልዎ በልቤ ማልጄዎት ነበር፤[ዲያቆን ለአባ ቆሞስ መጸለይ ያልተለመደ ቢኾንም¡] ዳሩ ግን ልብዎ ደንድኖ ጆሮዎ ከመስማትና ከማስተዋል ችላ ብሎ፣ በአመጸኝነትና በማን አለብኝነት የእርስዎን የግብር ልጆች አስከትለው በመምጣት፣ ወንጌል ሊማማሩ የተሰበሰቡትን የገዛ ልጆችዎን፣ "ተሳስተዋል ቢሉ መክረው አስተምረው መመለስ ወይም ባይቻልዎ ከእርስዎ ለሚሻል አባት ማስመከር ሲገባዎ" እጅና እግር ሰንዝረው ተማትተው ደም በማፍሰስዎ አፈርንልዎት!

Saturday 2 December 2017

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፭

ü  ዘፍጥ.2፥7 
     ህ ክፍል የምዕ.1 ሌላ እይታ ወይም ማብራሪያ እንጂ ከስድስቱ ቀናት ውጪ ቀጣይ ታሪክን በራሱ የያዘ አይደለም፡፡ የፍጥረትን ታሪክ በተመለከተ ከሁለት አቅጣጫ በመመልከት ወይም የምዕ.1ን የአፈጣጠር ሁኔታ ለማብራራት የተቀመጡ እንጂ፣ ሁለት የተለያዩ ዘመናት ታሪኮችና ክስተቶች አይደሉም፡፡ ይህ ደግሞ የቅዱሳት መጻሕፍት ባሕርይ ነው፡፡ ለምሳሌ፦ አንድ ሰው “ከመሬት ተነሥቶ” አራቱ ወንጌላት ይበዛሉና ይቀነሱ ቢል፣ ጤናማ ሃሳብ ነው ብለን አንቀበለውም፤ ምክንያቱም የአንዱን የጌታችን ኢየሱስን ትምህርትና ሕይወት ከአራት ወንጌላውያን እይታ አንጻር አይተው አስፍረውታልና በደስታ ተቀብለነዋል፡፡ በዘፍ.1 እና 2 ላይም አንድን የፍጥረት ታሪክ በሁለት እይታ መስፈሩን ማስተባበል አንችልም፡፡ 
    አልያ ግን አሁንም ሌላ ጥያቄ ልናነሳ እንችላለን፤ “እግዚአብሔር ፍጥረትን በስድስት ቀን ፈጥሮ አልጨረሰም” ወደሚል አንድ እንግዳ ጫፍ ይወስደናል፡፡ ስለዚህ ምዕ.2 የምዕ.1 ማብራሪያ ወይም ሌላ እይታ ነው፡፡[1] ይህንንም እንዲህ በአጭሩ ማሳየት እንችላለን፤
ü  ለሰማይና ምድር፦
v ምዕ.1፥1-2 በአጭሩ፣ “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ፡፡ ምድርም ባዶ ነበረች፥ አንዳችም አልነበረባትም፤ ጨለማም በጥልቁ ላይ ነበረ፤ የእግዚአብሔርም መንፈስ በውኃ ላይ ሰፍፎ ነበር” ይላል፤
·        ምዕ.2፥4-6 ላይ ይኸንኑ ሲያብራራ፣ “እግዚአብሔር አምላክ ሰማይንና ምድርን ባደረገ ቀን፥ በተፈጠሩ ጊዜ የሰማይና የምድር ልደት ይህ ነው፡፡ የሜዳ ቁጥቋጦ ሁሉ በምድር ላይ ገና አልነበረም፤ የሜዳውም ቡቃያ ሁሉ ገና አልበቀለም ነበር፣ እግዚአብሔር አምላክ ምድር ላይ አላዘነበም ነበርና፥ ምድርንም የሚሠራባት ሰው አልነበረም፤ ነገር ግን ጉም ከምድር ትወጣ ነበር፥ የምድርንም ፊት ሁሉ ታጠጣ ነበር” ይላል፡፡

Wednesday 29 November 2017

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፬


ሰው መንፈስ ነውን?

   ሰው ሥጋና ነፍስ ወይም ሥጋና መንፈስ ነው፤ የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት የብልጥግና ወንጌል[1] መምህራን፣ “ሰው መንፈስ ነው፤ ነፍስ አለው፤ በሥጋ ውስጥ ያድራል፡፡”[2] በሚለው ፍጹም ክህደት ደምድመውታል፡፡ “ሰው መንፈስ ነው” የሚለው ትምህርታቸውን የሚያስተምሩበት ዓላማቸው ኋላ ላይ አግተልትለው ከሚያመጡት “ፈጣጣ ክህደት” አንጻር እንጂ ወዲያው አይገባንም፡፡ በአጭሩ “ሰው መንፈስ ነው” የሚሉበት ዋና ዓላማቸው ሥጋ ለባሹን ሰው፣ “እግዚአብሔር ለማድረግ” ከሚባዝን ከንቱ ምናባዊ ቅዠት የተነሣ ነው፡፡ ይህንን በድፍረት ኢትዮጲያዊው የቃል እምነት መምህሩ ኃይሉ ዮሐንስ እንዲህ ይላል፦
   “ … አዎ ልክ እንደእግዚአብሔር ነን[ኝ] በሚለው እስማማለሁ፤ ምን ማለት ነው ይህ? መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃዎች አሉኝ፤ በመጀመርያም የምሄደው ዘፍ.1፥26-28 ያለውን በመጥቀስ ነው፤ … ያ መልክና አምሳል ሙሉ ለሙሉ እግዚአብሔርን እንድንመስል ያደርገናል የሚል አመለካከት አለኝ፡፡ ግን “detail” መሄድ ቢያስፈልግ ጌታችን ኢየሱስ ስለራሱ የተናገራቸው ነገሮች ትዝ ይሉኛል፤ በዮሐ.14፥8 ላይ … “እኔና አብ አንድ ነን” ያለበት ሃሳብ በእኔ አመለካከት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው፤ የእግዚአብሔር ልጅ ማለት ደግሞ ሰው ነው፤ በእኔ አመለካከት የሌላውን ሰው አመለካከት ልጋፋው አልችልም፡፡ ጌታ ኢየሱስ “እኔና አብ አንድ ነን” ካለ፣ ታላቅ ወንድማችን እንደዛ ካለ፣ እኛ ደግሞ ከአባታችን ጋር አንድነታችንን መናገር እንችላለን፤ ምክንያቱም ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ ነው እኛም ደግሞ የእግዚአብሔር ልጆች ነን፡፡

Saturday 25 November 2017

ሁሉ አንሶ ይታየኝ!


እልፍ ጥሪት ኖሮኝ ሕይወት እንዳላጣ
በሚስቴ ተክቼህ ካንተ እንዳልፋታ
እናት አባት ወንድም እህትና ዘመድ ...

Monday 20 November 2017

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፫

2. ታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰውነቱ የተናገረውንና የተነገረለትን ልክ ለመለኮቱ እንደተነገረ ተቆጥሮ ሲካድ እንመለከታለን፡፡ ለዚህም እንደዋቢ አድርገው የሚጠቅሱት፣ “የክርስቶስን ከዘላለም የእግዚአብሔር ልጅ አለመኾኑን” ሁለት ሃሳቦችን በአንድነት በመስፋት ነው፡፡ እንዲህ በማለት፦ “አብና ወልድ …እኩል አይደሉም፤ አብ ወልድን ይበልጣል፤ … ገብርኤል እንዳለው ስሙ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል፤ ከዛ በፊት አባታችን ነው፤ ሌላ ማስረጃ በዕብ.2 ላይ “ልጆቹ በሥጋና በደም እንደሚካፈሉ እርሱም እንዲሁ በሥጋና በደም ተካፈለ፤ ማን ተካፈለ? አባታቸው፡፡ ስሙ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል በሚል የእግዚአብሔር ልጅ ብሎታል፤ ከዛ በፊት ልጅ አልነበረም ወይ? ልጅ አልነበረም፤ አባታችን ነው፡፡ አባትና ልጅ መሆንም አይችልም፡፡ … ኢየሱስ ክርስቶስ ለዘለዓለም ልጅ ከነበረ ለዘለዓለም ከአብ ያንስ ነበር ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ሥጋ የለበሰው መች እንደኾነ እናውቃለንና፤ ሥጋ የለበሰው የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ከድንግል ማርያም በተወለደበት ጊዜ ነው ልጅ የኾነው፡፡ ያን ጊዜ “officially”[በግልጥ ወይም በይፋ ለማለት ይመስላል] እግዚአብሔር የነበረው ሥጋ ሲኾን፣ አብ ከእኔ ይበልጣል፤ ብታምኑስ አብ ከእኔ ይበልጣል ብሏል፤ አብ ስለሚበልጠው እንደውም በሁሉ ነገር ይጸልይ ነበር እንደማንኛውም ሰው፤ እርሱ ፍጹም አምላክ ፍጹም ሰው ነው ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ከኾነ “somehow”[እንደምንም] የኾነ ቦታ ተወልዷል ማለት ነው፤ …የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር አይደለም፡፡”[1] በማለት፡፡
    “ኢየሱስ ከአብ ጋር አይተካከልም” ለማለት መናፍቃኑ የሚጠቅሱት ጥቅስ፣ በእውኑ ክፍሉ እነርሱ እንደሚሉት ሃሳባቸውን ይጋራልን? እውን ቃሉ እነርሱ እንደሚሉት የኢየሱስን የመለኮታዊ “ታናሽነት” ይናገራልን? የጌታችን ኢየሱስ ልጅነት ወይም አባቴ ብሎ መጥራቱ የእርሱን አምላክ አለመኾንን ያመለክታልን? ዓውዱስ ያንን የሚል ነውን? ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መለኮታዊ ክብር እንደሌለው የሚያመለክት ነውን? … እና ሌሎችንም ተያያዥ ጥያቄዎችን በማንሳት መመርመር ይኖርብናል፡፡
ብ ከእኔ ይበልጣል” የማለቱ ምክንያት
   ንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እጅግ በተደጋጋሚ የክርስቶስ ኢየሱስ ጌታችንን ከአብ ጋር ተካካይነት ሲገልጥልን አይተነዋል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደአባቱ እንደሚሄድ በተናገራቸው ጊዜ ልባቸው ታውኳል፣ (ዮሐ.14፥1)፣ ደግሞም ፈርተዋል፤ (ቁ.27)፡፡ ስለዚህ መፍራትና መሸበር እንደሌለባቸው በሚያጽናና ቃል ተናገራቸው፡፡ እንደውም የእርሱ ወደአብ መሔድ የተሻለ መኾኑን ስለሁለት ምክንያት ተናገራቸው፤ (1) “ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ ይሰጣችኋል፤”(ቁ.15-16)፣ (2) ጌታችን ኢየሱስ ወደአባቱ በመሄዱ አብ እርሱን ያከብረዋል፤ (ዮሐ.17፥5)፡፡ ደቀ መዛሙርቱ እኒህን ታላላቅ ምክንያቶች ያስተዋሉ አይመስሉም፡፡ ስለዚህም ለራሳቸው እጅግ ከማሰብ የተነሣ በራሳቸው ሃሳብና ኀዘን ውስጥ ተዋጡ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ እነርሱ በዚህ ዓይነት ድብልቅልቅ ስሜት ውስጥ እያሉ፣ “የምትወዱኝስ ብትሆኑ ከእኔ አብ ይበልጣልና ወደ አብ በመሄዴ ደስ ባላችሁ ነበር” በማለት ተናገራቸው፡፡ ይህንንም ስለሁለት ነገር ተናግሯቸዋል፡፡ እኒህም፦

Thursday 16 November 2017

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፪

ክፍል አንድ
    ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መለኰታዊ ማንነት መካድ፣ በእምነት እንቅስቃሴ መምህራን ዘንድ እጅግ የታወቀና እንግዳ ያልኾነ ነገር ነው፡፡ ምንም እንኳ በትምህርቶቻቸው መካከል በኢየሱስ ክርስቶስ “እንደሚያምኑ” ቢናገሩም፣ ነገር ግን እናምናለን የሚሉትን ሲያብራሩትና ሊያስተምሩት ሲነሡ ግን በትክክል ሲክዱት ይስተዋላል፡፡ በእርግጥም፣ የኑፋቄ መምህራንን ከምንለይበት መንገድ አንዱ፣ በደፈናው እናምናለን የሚሉትን የትኛውም ትምህርታቸውን፣ “እስኪ አብራሩት” ሲባሉ፣ ኑፋቄያቸው ወለል ብሎ ይታያል ወይም ከመጽሐፍ ቅዱስ በተቃርኖ ይቆማል፡፡
    ስለጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያላቸውም ትምህርት እንዲህ የሚል ነው፦
   “ኢየሱስ መለኮታዊ መኾኑን ያወቀውና ያገኘው በውስጡ መኖሩን ፈልጐ ካገኘ በኋላ ሲኾን፣ ይህንንም በማወቁና ፈልጎ በማግኘቱ እጅግ ታላቅ አስተዋይ ሰው ነው፤ … ራሱም በአንደበቱ፣ “የምትወዱኝስ ብትሆኑ ከእኔ አብ ይበልጣልና ወደ አብ በመሄዴ ደስ ባላችሁ ነበር” (ዮሐ.14፥28) ብሏልና፣ ከአብ ያንሳል፡፡ ሰው ብቻ ኾኖ እንጂ አምላክ በመኾን ፈጽሞ አልመጣም፡፡ ደግሞም በማናቸውም ሥፍራ ራሱን “እኔ አምላክ ነኝ” ብሎ አልገለጠም፡፡”
በማለት ይናገራሉ፡፡ ይህ ትምህርታቸው የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት በግልጥ የሚክድ ነው፡፡
     በዚህ ትምህርታቸው ውስጥ ክርስቶስን በተመለከተ መጽሐፍ ቅዱስን በመቃረን ብዙ ኑፋቄያት ተሰግስገው እናያለን፡፡ በዋናነትም ብንጠቅስም፦

Friday 10 November 2017

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፩


Please readin PDF
መግቢያ
     የሐሰት መምህራን ክርስትና ከመጀመሩ በፊትም የነበሩና ያሉ፣ በእኛም ዘመን እንግዳ ኾነው የተከሰቱ ያይደለ ሲኾን፤ ትምህርታቸውም ከታየበትም ጊዜ ጀምሮ እውነተኛ የእግዚአብሔር አገልጋዮች የሐሰት ትምህርታቸውን ሳይታገሱ ፊት ለፊት የተቃወሙ መኾናቸውን መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ ይነግረናል፡፡ ሐዋርያት በዘመናቸው ይሠራጭ የነበረውን የሐሰት ትምህርትና አስተማሪ መምህራንን ትምህርታቸውንና ስማቸውን ጠቅሰው ተቃውመዋል፤ የሰማርያው ጠንቋዩ ሲሞን (ሐዋ.8፥9)፣ ሄሜኔዎስና እስክንድሮስ[እስክንድሮስ የተባለው ምናልባት የናስ አንጥረኛው እስክንድሮስ ሊኾን ይችላል (2ጢሞ.4፥14)] (1ጢሞ.1፥20)፣ ሄሜኔዎስና ፊሊጦስ (2ጢሞ.2፥17)፣ ዴማስ(2ጢሞ.4፥10)፣ ዋናቸው ሊሆን የሚወድ ዲዮጥራጢስ (3ዮሐ.9) እና ሌሎችንም “ሐዋርያት ነን የሚሉቱን መርምረው ሐሰተኞች ሆነው ባገኟቸው” ጊዜ እንደለዩዋቸው ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክርልናል፤ (ራእ.2፥2)፡፡

   በኋለኛውም በቤተ ክርስቲያን አባቶች ዘመን፣ ቤተ ክርስቲያን የተነሡባትን የኑፋቄ ትምህርቶች እንደጉባኤ ኒቂያ፣ ቁስጥንጥንያ፣ ኤፌሶንና ሌሎችንም ጉባኤያትን በመሥራት ከኢቦናውያን እስከ ግኖስቲካውያን፣ ከሲሞን መሠርይ እስከ አርዮስ፣ መቅዶንዮስ፣ አቡሊናርዮስ፣ አውጣኪ፣ ንስጥሮስ፣ ቫሲለደስ፣ መርቅያን … ድረስ ያሉትን መናፍቃንን በየዘመኑ በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መዝና ትቃወም፤ አልመለስ ያሉትንም አውግዛ ከመካከሏ ትለይ[ለሰይጣን አሳልፋ ትሰጥ (1ቆሮ.5፥5)] እንደነበር ታሪክ ምስክራችን ነው፡፡

Monday 6 November 2017

አመናፋሹ!



እንዳልተበጃጀ፣ በእግዜር ምስያ
እንዳልተፈጠረ፣ በመልኩ በአርዓያ
ራሱን ጫፍ ላይ ሰቅሎ፣ ሥጋውን አግንኖ
አስገኚ ነኝ አለ፣ አስገኚን ኮንኖ፡፡

ሚስቱን በቀኝ ክንዱ፣ ታቅፎ እየሳመ
እየበላ እየጠጣ፣ የላመ የጣመ
ቃሉን አመንፍሶ፣ እኔው መንፈስ አለ ...

Wednesday 1 November 2017

ልዩውን ወንጌል በወንድማማችነት ስም አለመቃወም መጽሐፍ ቅዱሳዊ አይደለም!

   ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱ ስለማመንና ወንጌልን ስለማገልገል በሚገጥመን ነገር፣ “ከእኔ ይልቅ አባቱን ወይም እናቱን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይገባውም፤ ከእኔ ይልቅም ወንድ ልጁን ወይም ሴት ልጁን የሚወድ ለእኔ ሊሆን አይገባውም” (ማቴ.10፥37) በማለት በግልጥ አስተምሯል፡፡ በመንፈሳዊው ዓለም ጌታችን ክርስቶስና የክርስቶስ ትምህርት ዋናና ዘወትር የቀዳሚነት ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ነገር ነው፡፡ በዓለም ላይ ከትዳር፣ ከቤተሰብ፣ ከልጅ፣ ከአባት፣ ከእናት፣ ከባልንጀራ፣ ከወዳጅ፣ ከሃይማኖት አባት፣ ከሰባኪ፣ ከዘማሪ፣ ከመጋቢና ከቄሱም … ከማናቸውንም ሰውና ነገር ይልቅ ጌታችን ክርስቶስ ዋናና ተከታይ የሌለው ነው፡፡
   የክርስቶስ ዋናነት በትምህርታችን፣ በሕይወታችን፣ በመንገዳችን፣ በመውጣት በመግባታችን፣ በኹለንተናችን ጭምር ነው፡፡ በዓውደ ምሕረትም፤ ከዓውደ ምሕረት ስንወርድም፣ ከሌሎች ጋር ባለን ግንኙነትም ኾነ ለብቻችን በመንገዳችን ኹሉ ክርስቶስ ዋናና አይነኬ የክርስትናችን መሠረትና ማንንም የማናስነካው ዓይነ ብሌናችን ነው፡፡ ቅዱሱ መድኃኒታችን ክርስቶስ በቅድስና የምንኖርለት ብቻ አይደለም፣ የምንሞትለትም ጌታችን ነው፡፡ በማናቸውም መንገዳችን ክርስቶስንና ትምህርቱን ለድርድርና ለአማራጭ አናቀርበውም፤ አናስነካውምም፡፡

Monday 23 October 2017

የበጋሻው ደሳለኝ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” አማኝነትና ኑፋቄያቱ (የመጨረሻው ክፍል)


4.   “የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት መካድ፣ በመጽሐፉ ቃል ላይ “የራስን ሃሳብ” መጨመር፤ የቃል ትእዛዝና፣ የገዢነት ሥልጣን”
     “ … ፊተኛው አዳም “lose” ያደረውን ነገር ሁሉ ኋለኛው አዳም መልሷል፤ ፊተኛው አዳም ምንድርነው lose ያደረገው? የተፈጠረበት “purpose” ምን የሚል ነበረ? ምድርን ግዛ፣ ባሕርን ግዛ፣ የሰማይ አእዋፍን ግዛ የሚል ነው፤ ያን ገዢነት ለእኛ መልሷል፤ ሁለተኛው አዳም በዚህ ማንነት ነው የተገለጠው … እያንዳንዱን ነገር አስተካክሏል፤ ለምሳሌ ባሕርን ግዟት አለ፤ በባሕር ውስጥ ያሉት ዓሦች አሉ፤ ኢየሱስ በአንድ ወቅት ግብር ክፈሉ ሲባል፣ ከዛ ጴጥሮስን ምን አለው? ወደባሕር ሂድ፣ ከዛ ዓሳ ታገኛለህ፣ ዓሣ ውስጥ ምን አለ ዲናር አለ፤ እርሱን አንዱን ለእኔ፣ አንዱን ላንተ ትከፍላለህ አለው፤ … ኢየሱስ ለማስደነቅ ምናምን ተአምር ያደረገ ይመስላችኋል? ዓሣ ውስጥ ያ ዲናር ከየት መጣ? …
    ኢየሱስ ሲናገር ዓሳ ውስጥ ዲናር ሲሠራ ነበር፤ በዚህ ቃል ነው ዓለምን የፈጠረው፤ … ምድርን ሲፈጥር እኮ ከነዳይመንዷ ነው የፈጠረው፤ አሁን አይግረምህ … ዓሳው የሆነ ቦታ ዲናር ውጦ አይደለም፤ ይኼ አንተ ያለህ ቃል የሚሠራ ነው፤ የሌለውን እንዳለው አድርጎ የሚጠራ፤ የሚያመጣ ነው፤ አዲሱ ፍጥረት ማንነቱ ይህ ነው፤ ምንም ነገር በቃሉ … [የበለሲቱን ምሳሌ አንስቶ]… የማትፈልገውን ትናገራለህ ይደርቃል፤ የምትፈልገውን ትናገራለህ ይለመልማል፤ የአዲሱ ፍጥረት ማንነቱ ነው ይኼ፡፡
     አዲሱ ፍጥረት ዓሣን ብቻ ማዘዝ እንዳይመስልህ ወዳጄ፤ ባሕሩ ላይ መራመድ ካስፈለገህ ትራመዳለህ፤ ይኼ [ኢየሱስ]አምላክ ስለኾነ አይደለም ያደረገው፤ ገና born again ያላደረገው ጴጥሮስን ተናገር ብሎታል፤ “born again” ያልተወለደው ከተራመደ አንተ እንዴት?[አትችልም?] ያኔ ጀልባ ስላለ ላያስፈልግ ይችላል፤ ጭንቅ ቢኾን ትሞታለህ እንዴ? [ሰሚዎቹ በጣም በሚጮኽ ድምጽ አልሞትም ሲሉ በተደጋጋሚ ይሰማል፤] ትራመድበታለህ፤ በባህር ላይ እንድትራመድ የሚያደርግህ “Divine thecnology” ባንተ ላይ ይገጠማል፤ እምነት ይባላል፤ … ”
     በጋሻው በዚህ ትምህርቱ ውስጥ ብዙ ነገሮችን ይስታል፤
1.     በጋሻው፣ “ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በባሕር የተራመደው አምላክ ስለኾነ አይደለም” ይለናል፡፡ እንዲህ በማለት፦ “... ባሕሩ ላይ መራመድ ካስፈለገህ ትራመዳለህ፤ ይኼ [ኢየሱስ]አምላክ ስለኾነ አይደለም ያደረገው፤ ገና “born again” ያላደረገው ጴጥሮስን ተናገር ብሎታል፤ “born again” ያልተወለደው ከተራመደ አንተ እንዴት?[አትችልም?] ያኔ ጀልባ ስላለ ላያስፈልግ ይችላል፤ ጭንቅ ቢኾን ትሞታለህ እንዴ? [ሰሚዎቹ በጣም በሚጮኽ ድምጽ አልሞትም ሲሉ በተደጋጋሚ ይሰማል፤] ትራመድበታለህ፤ በባህር ላይ እንድትራመድ የሚያደርግህ “Divine thecnology” ባንተ ላይ ይገጠማል፤ እምነት ይባላል፤ … ”

Monday 16 October 2017

የበጋሻው ደሳለኝ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” አማኝነትና ኑፋቄያቱ (ክፍል 4)

Please read in PDF

3.  በጋሻው “ሰው መንፈስ  ነው” ይለናል፤ ከየት ይኾን የቀዳው?
    በጋሻው የሰውን ሰውነት አያምንም፡፡ ሰው ሥጋና ነፍስ ወይም ሥጋና መንፈስ ነው፤ የሚለውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት በጋሻው፣ “ሰው መንፈስ ነው፤ ነፍስ አለው፤ በሥጋ ውስጥ ያድራል፡፡” በሚለው ፍጹም ክህደት ደምድሞታል፡፡ የዚህ ኑፋቄ ትምህርቱንም ሲያብራራ እንዲህ ይላል፦
   “ ... በእግዚአብሔር የተፈጠረው መንፈስ የሆነው ሰው ከምድር አፈር አዘጋጀው፡፡ ... ያበጀውን፣ የፈጠረውን ያበጀው ውስጥ ጨመረው፤ መንፈስ ሥጋ ውስጥ ገባ ማለት ነው፡፡ ... ነፍስ ማለት ሦስተኛ አካል ምናምን አይደለችም … ነፍስ የተባለው ነገር ዕውቀት ስሜት ፈቃድ ናት፡፡ ለምሳሌ፦ አንድ ዕውቀት ወይም ትምህርት ... ለምሳሌ፦ ባዮሎጂ አካል አለው እንዴ? ... እርሷ[ነፍስ] በመንፈስና በሥጋ መካከል ሆና ላሸነፈው ላሳመነው ... እርሷን ራሱ በዕውቀት ነው የምታሳምነው፡፡ ... በተጨባጭ ነገር ካመነች ስሜት ይፈጠራል ማለት ነው፡፡ ...
     ... ስለዚህ ሰው የራሱ ፈቃድ፣ የራሱ እውቀት፣ የራሱ ስሜት ያለው ማንም ጣልቃ የማይገባበት ለወደደው ነገር ራሱን የሚያስገዛ ማንነት ባለቤት ሆኖ ተፈጠረ፡፡ ስለዚህ ሰው ማን ነው? ከተባለ መንፈስ ነው ነፍስ አለው በሥጋ ውስጥ ያድራል ነው መልሱ፡፡ ሰው ሥጋ ነው፤ ነፍስ ነው አትልም፤ ሰው ማን ነው? ከተባለ ሰው መንፈስ ነው፤ …” 

Tuesday 10 October 2017

የበጋሻው ደሳለኝ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” አማኝነትና ኑፋቄያቱ (ክፍል 3)

2.   በጋሻው ደሳለኝ ተቀባሁበት ያለው “የኢየሱስ ቅባት”?!
    መጽሐፍ ቅዱስ ስለቅባት ወይም መቀባት ግልጥና ምንም የማያሻማ ትምህርት አለው፡፡ በብሉይ ኪዳን ዘመን ነቢያት፣ ካህናትና ነገሥታት እንዲሁም ዕቃዎች ለአገልግሎት ስለመለየታቸውና ስለመሾማቸው በዘይት ይቀቡ ነበር፡፡ ለእግዚአብሔር ሥራ የተለዩት የብሉይ ኪዳን የመገናኛው ድንኳንና ዕቃው ተቀብተው ነበር፤ (ዘጸ.30፥22-29)፡፡
    “ … ይህንን በብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ በግልጥ ሰፍሮ እንመለከተዋለን፡፡ እኒህም ካህናት፣ ነገሥታትና ነቢያት አገልግሎታቸውን የሚፈጽሙት በቅዱስ ቅባት ከተቀቡ በኋላ ነበር፡፡  ለምሳሌም፦ ሙሴና ወንድሙ አሮን (ዘጸ.40፥13 ፤ ዘሌ.4፥3 ፤ 8፥1 -9፥1-8 ፤ መዝ.98(99)፥6)፣ አብያታር(1ሳሙ.30፥7 ፤ 1ዜና.15፥11፤ 27፥34)፣ … ካህናት፤ ሙሴ (ዘዳግ.18፥15 ፤ ሐዋ.7፥37)፣ ናታን(2ሳሙ.7፥2)፣ ሳሙኤል (1ሳሙ.7፥15-17) … ነቢያት፤ ዳዊት(1ሳሙ.16፥13 ፤ 26፥11 ፤ 2ሳሙ.5፥3፤ ሐዋ.13፥22)፣ ሰሎሞን( 1ነገ.1) እኒህና ሌሎችን ብናነሣ ካህናት፣ ነቢያትና ነገሥታት የሆኑትና ሕዝቡን በግልጥ ያገለግሉ የነበሩት በአደባባይ በቅዱሱ ቅባት ተቀብተው ነበር፡፡ ይኸውም ለተለዩለትና ለተሾሙበት ሥራ በቅዱሱ እግዚአብሔር መለየታቸውንና ለሥራቸው ብቁዐን አድራጊው በዘይቱ የተመሰለው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መኾኑን በምሳሌነት ያሳያል፤ …” [1]
    በዚህ ዘመን የሚነሡ የሐሰት መምህራን “ተቀባሁ ወይም ተቀብቻለሁ” የሚለውን ሃሳብ ይዘው የሚነሱት፣ ስለመቀባት የተነገሩትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን “በሥልጣናዊ ቃልነት” የራሳቸውን ሃሳብ በማስገባት ሊጠቀሙባቸው በማሰብ ነው፡፡ በአንድ በኩል ከእግዚአብሔር ተምረናል ብለው የሚናገሩትን ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንቀበላቸው፤ በሌላ በኩል ደግሞ በእንከንና በሕጸጽ የተከበበውን ትምህርታቸውን “ትክክል አይደለም” ብለን ብንሞግት፣ “የቀባኋቸውን አትዳስሱ፥ በነቢያቴም ክፉ አታድርጉ ብሎ፥ ሰው ግፍ ያደርግባቸው ዘንድ አልፈቀደም፥ ስለ እነርሱም ነገሥታትን ገሠጸ፤” (መዝ.107፥14-15) የሚለውን በመጥቀስ እንዳፈለጋቸው ቢያጠፉና ቢያስቱ ምንም እንዳንናገራቸው፤ “በመቅሰፍታቸው ሊገስጹን” ስለሚፈልጉ ነው፡፡

Wednesday 4 October 2017

የበጋሻው ደሳለኝ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” አማኝነትና ኑፋቄያቱ (ክፍል 2)

በክፍል አንድ ላይ ለተሰጡ አስተያየቶች “ሚጥጥዬ መደምደሚያ”
    የተሰጡት አስተያየቶች ሁለት መልክ ያላቸው ናቸው[ሦስተኛውን የስድብ ክፍል መጥቀስ ባልሻም]፤ አንደኛው ቀድሞ በግል መምከርና ማናገር ይገባ ነበር እና አንተ ራሱ ማን ኾነህ ነው እርሱን “የምትኰንነው?” የሚሉ ይመስላሉ፡፡ ለአስተያየቶቹ መልስ መስጠትን ባላምንበትም፣ በአብዛኛው በዙርያዬ ያሉ ሰዎች ያዘነቡትን ስድብና[በተለይ በኢሜይል] አስተያየት ከክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር እጅግ ስለወረደብኝ፣ የትምህርቱን ኢ ክርስቶሳዊነት ለሚረዱት የማጥራት ሥራ ለመሥራት፣ ትምህርቱን አምነው ለተከተሉት ደግሞ በክርስቶስ ትምህርት ላይ ለሚመጣው የትኛውም ሰውም ኾነ ማኅበር ጭካኔዬን ለማሳየት ነው፡፡ አንድ ነገር ማስታወስ እወዳለሁ፤ አሁን እየተቃወሙ ካሉ ሰዎች መካከል አንዳንዶቹ በአንድ ወቅት ግብረ ሰዶማውያን አገልጋዮች በግልጥ ተደርሶባቸው እንዲመለሱ ብዙ ተመክረው አልመለስ ሲሉ፣ ከአደባባይ ነውራቸው አልመለስ ብለው ልባቸውን ሲያደነድኑና እውነታውን ለማድበስበስ ሲጥሩ በአደባባይ ሰዎች እንዲጠነቀቋቸው ስጽፍ የተቃወሙኝ መኾናቸውን አሁንም ማንሳት እፈልጋለሁ፡፡
    በጋሻውን በተመለከተ በተደጋጋሚ ማውራቴንና በዚህ ትምህርት ማመን አለማመኑን ስለመጠየቄ፣ እርሱም ስለመናገሩ ያልጻፍኩት፣ ብዙም አስፈላጊ መስሎ ስላልታየኝ ነው፤ አስፈላጊና ሁሉ ማወቁ የግድ ተገቢ ነው ከተባለ ግን እንዴትና ምን ብዬ እንዳወራሁት፤ እርሱም በዚህ ትምህርት ዙርያ ያለውን አቋሙን ምን ብሎ እንደነገረኝና ይህን የሐሰት ትምህርትም ሊለውጠውም እንደማይፈቅድ የመለሰልኝን በዚህ ጽሁፍ ማብቂያ ላይ ለመግለጥ ቃል እገባለሁ፡፡

Monday 2 October 2017

በጋሻው ደሳለኝ ና አዲሱ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” ትምህርቱ (ክፍል 1)

ግቢያ
     በዚህ ዘመን በእግዚአብሔር ዘንድ ያልታወቁትን(ማቴ.7፥23) በሕዝብ ዘንድ የገነኑትንና የታወቁትን አገልጋዮች “ተሳስታችኋል ተመለሱ” ማለት፣ ራስን በስለት ላይ የማቆም ያህል ሕመሙ ጽኑና እጅግ አደገኛ ነው፡፡ አደገኛነቱም ከሁለት ነገር አንጻር ነው፤
1.     ደጋፊዎቻቸው ብዙ ከመሆናቸው የተነሣ ተቃውሟቸው ተራ ተቃውሞ ሳይሆን፣ ልክ እንደቅዱሳን ሰማዕታት ስለመምህሮቻቸው በነፍስ ተወራርደው እስከመግደልና ስም ለማጥፋት የሐሠት ታሪክን ፈብርከው ከማኅበረሰቡ እስከማግለል ሊያደርስ በሚችል ጽኑ ቁጣ ውስጥ ስለሚገቡና፤
2.    ሕዝብ[አማንያንም ጭምር] ደግሞ እንዲህ ያለውን ነገር በቅንነትና በልበ ሰፊነት ከእግዚአብሔር ቃልና ከስህተት መምህራን ጠባይ አንጻር ከመመዘን ይልቅ፣ እንዲህ ያሉ መምህራንን የሚቃወሙትን አካላት ቀንተው ወይም ከጥላቻ አንጻር ... አንዳንዴም ሲከፋ የራስን ቅቡልነት በሕዝቡ ለማስረጽ የሚደረግ ደባ ነው በማለት፣ ተግሳጽና ተቃውሞውን በትክክል ለሕዝቡና ለእግዚአብሔር ከመቅናት አንጻር እንደተደረገ አድርጎ መውሰድ ፈጽሞ አልተለመደም፡፡

Saturday 30 September 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (የመጨረሻ ክፍል)

Please read in PDF 
4.   ስሐ እንግባ
    አማንያን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ብቻ በትክክል እንዲሰሙ፣ ክርስቶስን ሳይኾን ራሳቸውን የሚያገለግሉ አገልጋዮችን ከመስማት ተከልክለው ለቃሉና ለፈቃዱ እንዲታዘዙ ለማድረግ፣ ቤተ ክርስቲያን የራሷን ጠባይ እንደቃሉ ማረቅና ዘወትር በቅዱስ ቃሉ መስታወትነት ራሷን መመልከት ይገባታል፡፡ ንስሐ ራስን ለእግዚአብሔር በትክክል ማቅረብና አራቁቶ ማቅረብ ብቸ ያይደለ፣ ድርጊታዊ ምላሽን ይሻል የምንለውም ከዚህ ተነሥተን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሌሎችን ከክፋታቸው እንዲመለሱ ለመምከር ከመዘጋጀቷ በፊት፣ ከምትወቅስበት ወቀሳ ለራሷ ንጹህና በዚያም ነውርና ክፋት ያልተያዘች፤ ፈጽማም የጠራች ልትኾን ይገባታል፡፡
     የራሳችንን ክፉ ጠባይ ሳናስተካክል፣ ሌሎች ትክክለኛውን ነገር እንዲያደርጉና ወደትክክለኛው እውነት እንዲመጡ ጫና ከማድረግ መከልከል አለብን፡፡ ከዚህ ነገራችን ንስሐ ሳንገባ ይህንን የምናደርግ ከኾነ ግን ቅዱስ ቃሉ፦አንተ የምትፈርድ ሰው ሁሉ ሆይ፥ የምታመካኘው የለህም፤ በሌላው በምትፈርድበት ነገር ራስህን ትኰንናለህና፤ አንተው ፈራጁ እነዚያን ታደርጋለህና” (ሮሜ.2፥1) እንዲል፣ “በወንድምህም ዓይን ያለውን ጉድፍ ስለምን ታያለህ፥ በዓይንህ ግን ያለውን ምሰሶ ስለ ምን አትመለከትም?” (ማቴ.7፥3) በማለት በጽኑ ወቀሳ ሁላችንን ይወቅሰናል፡፡

Monday 25 September 2017

መስቀል ማለት ለኔ …

          Please read in PDF

መስቀል ማለት ለኔ …
ጌታዬ ኢየሱስ እኔን ስለመውደድ
ሊያድነኝ ሊቤዠኝ የሄደበት መንገድ
ከጲላጦስ ሄሮድስ ከሄሮድስ ጲላጦስ

Thursday 21 September 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል ሃያ)


Please read in PDF
3. ጌታችን ጋር ጸንታችሁ ቁሙ፦ መጽናት፣ አለመናወጥን፣ መረጋጋትን፣ መቆምን፣ አለማወላወልን፣ ወደግራም ወደቀኝም አለማለትን፣ አንድን ነገር አጥብቆ መያዝንና ለዚያም ነገር ዋጋ መክፈልን ... የሚያሳይ ነው፡፡ መጽናት የብዙ መታገስ ውጤት[እጅግ ብዙ ትእግስት] ነው፡፡ ብዙ የማይታገስ የማይናወጠውን በመመልከት ሊጸናና ሊቆም አይችልም፡፡ በመከራ የሚታገሱ ሁሉ(ሮሜ.12፥12) በክርስቶስ መንግሥት የሚካፈሉት ሕይወትና ደስታ አላቸው፡፡ የማይጸኑና በክርስቶስ ትምህርት ታግሰው የማይኖሩ ግን እጅግ አስጨናቂ ነገር ይገጥማቸዋል፡፡
     መጽሐፍ ቅዱስ አስቀድመን በክርስቶስ ኢየሱስ ባመንነው እምነታችን መጽናትና በዚያም ማወላወል እንደሌለብን በተደጋጋሚ ይነግረናል፤ ምክንያቱም ራሱ ክርስቶስ ኢየሱስ መከራን ሁሉ በቅድስናና ባለማጉረምረም በመጽናት የእውነተኛ ጽናት ዋና ተምሳሌት ነውና፣ (1ጴጥ.2፥21)፤ “ጽና፥ እጅግ በርታ፤ ባሪያዬ ሙሴ ያዘዘህን ሕግ ሁሉ ጠብቅ፥ አድርገውም፤ በምትሄድበትም ሁሉ እንዲከናወንልህ ወደ ቀኝም ወደ ግራም አትበል፤” (ኢያ.1፥7)፤ “ንቁ፥ በሃይማኖት ቁሙ፥ ጎልምሱ ጠንክሩ” (1ቆሮ.16፥13)፤ “… ተመሥርታችሁና ተደላድላችሁ ከሰማችሁትም ከወንጌል ተስፋ ሳትናወጡ፥ በሃይማኖት ጸንታችሁ ብትኖሩ ይሆናል” (ቈላ.1፥23) “እናንተ በጌታ ጸንታችሁ ብትቆሙ፥ አሁን በሕይወት እንኖራለንና” (1ተሰ.3፥8)፤ “እንግዲያስ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ጸንታችሁ ቁሙ፥” (2ተሰ.2፥15)፤ “በነፍሳችሁ ዝላችሁ እንዳትደክሙ፥ ከኃጢአተኞች በደረሰበት እንዲህ ባለ መቃወም የጸናውን አስቡ” (ዕብ.12፥3) እንዲል፡፡

Friday 15 September 2017

የኢትዮጲያ ከፍታችን፤ ያለመብሰል ምኞት ወይስ ከልብ የምንሻው እውነት?!



     Please read in PDF

    መጽሐፍ ቅዱስ ስለኢየሱስ ክርስቶስ ሲናገር እንዲህ ይላል፥ “ … በዚህ ምክንያት ደግሞ እግዚአብሔር ያለ ልክ ከፍ ከፍ አደረገው፥ ከስምም ሁሉ በላይ ያለውን ስም ሰጠው፤” (ፊልጵ.2፥9) በማለት ሲናገር ምክንያቱንም፣ “እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋር መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቈጠረውም፥ ነገር ግን የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ፥ በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፥ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ የመኾኑ” ነገር ነው በማለት ይነግረናል፤ (ቁ.6-8)፡፡
   ጌታችን ኢየሱስ አንድ ባሪያን ይዞ ሳይሆን የባሪያን መልክ፣ የሰውን ትስብእት ይዞ፤ የማይሞተው እርሱ መዋረዱንና ሰው በመኾኑም ሞትን ሊቀምስ እንዳለው ያስተምረናል፡፡ ሰው ለመሆን ሲፈቅድ አገልጋይነትንና እስከሞት መታዘዝን መከራንና ስድብን ሁሉ መቀበልን(ማር.15፥29) ፍጹም ዝቅ ዝቅ ማለትን ያሳየናል፡፡ ሰማያዊ መብቱንም በፈቃዱ በመተው ፍጹም ዝቅታን መርጧል፡፡ በዚህ ክፍል ያለው ሃሳብ እጅግ ሰፊና ታላቅ ትምህርት ቢኾንም፣ ጌታችን ኢየሱስ በአብ ፊት አለልክ ከፍ ከፍ ለማለት ምክንያቱ ስለሰው ልጅ ማዳን አለልክ ዝቅ ዝቅ ማለቱን ከርእሳችን ጋር ተወራራሽ ነውና ልናነሣው ወደድን፡፡

Sunday 10 September 2017

ሠርክ አዲስ ዘመኔ!

Please read in PDF


ለምንድር ነው እንባ ስለምንስ ልቅሶ?
ከዘመናት በፊት ደምህ ለ‘ኔ ፈሶ፤
ሰቀቀን ለምኔ ማፈርና ፍርሃት?

Thursday 7 September 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ዘጠኝ)


Please read in PDF
1.     ንጸልይ፦ ጸሎት ሰባተኛው መሣርያ አይደለም፡፡ ከስድስቱም ጋር በአንድነት ዘወትር የምንታጠቀው ነው እንጂ፡፡ ስለዚህም እንደሰባተኛ ራሱን የቻለ መሣርያ አድርገን የምንቆጥረው አይደለም፡፡ ጸሎትን ዘወትር በትጋት መታጠቅ ይገባናል፡፡ ለክርስቲያን ጸሎት ዋና መንፈሳዊ መሣርያው ነው፡፡ ማናቸውንም መልካም ነገሮችን በጸሎት ልንጀምር፤ በጸሎትም ልንጨርሳቸው ይገባናል፡፡ “በጸሎትና በልመናም ሁሉ ዘወትር” የሚለው ቃል ስናጠቃም ኾነ ስንከላከል ጸሎት መሠረታዊና በማናቸውም ሰዓትና ሁኔታ ውስጥ ዘወትር መከናወን ያለበት ነገር እንደኾነ ያስገነዝበናል፡፡

Saturday 2 September 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ስምንት)




6.    መንፈስንም ሰይፍ ያዙ፦ ሰይፍ፣ “ከብረት የሚሠራ የጦር መሣርያ፤ (1ሳሙ.13፥19 ፤ 22)፡፡ አንዳንዱ ሰይፍ ባለሁለት አፍ ነው፤ (መዝ.149፥6)፡፡”[1] ሰይፍ ከማይታዩ ከክፉ ኃይላት ጋር አማኙ ለሚያደርገው ጦርነት በዋናነት የሚጠቀምበትና ከማጥቂያ መሣርያዎች የሚካተት ነው፡፡ ወታደር ዘወትር ከሚይዛቸው መሣርያዎችና ጥብቅ ስልጠና ከሚወስድበት አንዱ ስለሰይፍና አጠቃቀሙ ነው፡፡ በዚህ ክፍል በሰይፍ ምሳሌነት የቀረበው “እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ነው” ተብሎ የተነገረው ነው፡፡
    ሰይጣን ከምንም በላይ በእግዚአብሔር ቃል ላይ ያለንን መታመን ዋጋ ለማሳጣት ወይም ለማጥፋት በኹለንተናው የተቻለውን ሁሉ ያደርጋል፤ “እኔም ዛሬ አንተን የማዝዘውን ይህን ቃል በልብህ ያዝ፡፡ ለልጆችህም አስተምረው፥ በቤትህም ስትቀመጥ፥ በመንገድም ስትሄድ፥ ስትተኛም፥ ስትነሣም ተጫወተው፡፡ በእጅህም ምልክት አድርገህ እሰረው፤ በዓይኖችህም መካከል እንደክታብ ይሁንልህ፡፡ በቤትህም መቃኖች በደጃፍህም በሮች ላይ ጻፈው፤” (ዘዳግ.6፥6-9)፣ “በልብህ ጽላት ጻፋቸው” (ምሳ.3፥3 ፤ ኤር.31፥33)፣ “እንድንሰውራቸውም” (መዝ.119፥11) የታዘዝነውን የእግዚአብሔር ቃል ሰይጣን እንድንጥለው ብርቱ ጥረት ያደርጋል፡፡ ቃሉን በመጣል ውስጥ ያለውን ቀላልና አስቀያሚ ሽንፈት ዲያብሎስ በሚገባ ያውቀዋል፡፡

Thursday 24 August 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ሰባት)


   “ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል፡፡ እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ፤” (ሮሜ.13፥12) ሌሊቱ ተብሎ የተጠቀሰው አሁን ያለው ክፉ ዘመን ነው፡፡ ጊዜውም ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣበት ጊዜ ጀምሮ ያለውን የሚያካትት ነው፡፡ ቀጥሎም ሐዋርያው የክርስቶስን መምጣት አጽንቶ ይናገራል፡፡ “ቀኑም ቀርቦአል” ሲልም፣ በሌሎች የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፣ “ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ” (ማቴ.24፥33)፣ “ዘመኑ አጭር ሆኖአል፤”(1ቆሮ.7፥29)፣ “ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቦአል”(1ጴጥ.4፥7)፣ “የእግዚአብሔርን ቀን መምጣት እየጠበቃችሁና እያስቸኰላችሁ” (2ጴጥ.3፥11)፣ “ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ … ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን” (1ዮሐ.2፥18) “ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ” (ያዕ.5፥7)፣ “ዘመኑ ቀርቦአል” (ራእ.1፥3) ተብለው ከተገለጡት ምንባባት ጋር በመስማማት የዘመኑን  ከፊት ይልቅ ወደእኛ መቅረብና ክርስቶስ ሊመጣ በደጅ መኾኑን ይገልጥልናል፡፡

Monday 21 August 2017

ኾኜ ያንተ ሎሌ!

በዚህ በኛ ዘመን፣ ሁሉ ነቢይ ኾኖ፤
ሐዋርያነትም፣ ስሙ ብቻ ገኖ፤
ቅስናም ድቁናም፣ ሁሉ እየተካነው፤

Wednesday 9 August 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ስድስት)

                            Please read in PDF
3.    ሠላም ወንጌልም በመዘጋጀት እግሮቻችሁ ተጫምተው ቁሙ፦ የጫማ ዋና ሥራ ከማናቸውም እንቅፋት፣ እሾኽና እግርን ከሚጎዳ አደጋ መከላከልና መደገፍ ነው፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት “ከትእዛዝህ የተነሣ አስተዋልሁ፤ ስለዚህ የሐሰትን መንገድ ጠላሁ፡፡ ሕግህ ለእግሬ መብራት ለመንገዴ ብርሃን ነው” (መዝ.119፥104-105) አለ፤  በጥንት አይሁድ አንድ ሰው የሩቅ መንገድ ሲጓዝ ድንገት ቢጨልምበት፣ በሚሄድበት መንገዱ እንዳይሰናከል በእግሮቹ ላይ መብራትን ያሥራል፡፡ ይህም የሚረግጥበትን በትክክል እንዲያስተውልና ወድቆም ከመሰበር እንዲድን ይረዳዋል፡፡
   ዳዊት በማናቸውም የሕይወት መንገዱ የእግዚአብሔር ሕግ መብራትና ብርሃኑ ነው፤ ስለዚህም በማናቸውም መንገዱ ቢሆን ከሐሰት ጋር አያመቻምችም፣ አይስማማምም፡፡ የሐሰትን መንገድ ከነፍሱ እጅግ ይጠየፋል፡፡ መብራትና ብርሃኑ የሕጉ ቃል ነውና፣ ይህንንም ሕግ በማናቸውም መከራ ውስጥ እንኳ ቢያልፍ ከመጠበቅና በሕጉም ከመጽናናት ቸል አይልም፡፡ በዳዊት ንግግሮች ውስጥ ሁል ጊዜ ዝግጁነትና ፍጹም ታማኝነት አለ፡፡

Tuesday 1 August 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ አምስት)

Please read in PDf
የምንዋጋባቸው መሣርያዎቻችን
    መጽሐፍ ቅዱስ ከማን ጋር መዋጋት እንዳለብን አበክሮ የተናገረውን ያህል ከጠላታችን ጋር በመዋጋት በትክክል ስለምናሸንፍበት መሣርያም በግልጥ ይናገራል፡፡ ከዚህ በፊት እንዳየነው የምንዋጋው የእምነት ጦርነት ነው፡፡ የውጊያውም የጊዜ ቆይታ እስከክርስቶስ ዳግመኛ መምጣት ድረስ የሚቀጥል ነው፡፡ “በጌታና በኃይሉ ችሎት የበረታን ሆነን … የዲያብሎስን ሽንገላ መቃወም እንዲቻለን፣ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር ሁሉ መልበስ ያስፈልገናል”፡፡ ልብሱንና የጦር ዕቃውን መልበስና መለማመድ ግድ ነው፤ ያልተለማመድንበትና አብረን “ያልሰለጠንበት” ልብስ ለውጊያ ሊሆነን ፈጽሞ አይችልም፡፡
     የመሣርያው ዓይነት፣ የትጥቆቹ ይዘት በመከላከልና በማጥቃት ላይ የተመሰረቱ ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሁለቱንም ሥራዎች[መከላከልና ማጥቃትን] ክርስቲያኖች መፈጸም እንዳለባቸው ያስተምራል፡፡ ለጌታ መታዘዝን በባርያ ማንነት ውስጥ ሆነን የምናሳየውን ትጋት ያህል፣ ለጠላትና ለሚያስጨንቀው ገዢ አለመታዘዛችንና ግልጥ ተቃውሞዓችንን የምናሳይበት መንፈሳዊ ጠባይ የጌታ መንፈሳዊ ወታደር በመሆን ነው፡፡

Tuesday 18 July 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ አራት)

                                                                                   Please read in PDF
2. ዋጉ፦ በክርስቶስ ኢየሱስ ካመንንበት ቀን ጀምሮ ከክፋት ሁሉ አሠራርና ከዲያብሎስ ጋር ውጊያ ለመግጠም ፊት ለፊት ተፋጥጠናል፡፡ ደጋግመን እንዳነሣነው ውጊያችንም ከሥጋ ለባሽ ፍጡር ጋር ሳይሆን፣ ከጀርባው ለራሱ ክብርና አምልኮን ለመቀበል ከሚሠራው[ወንጌል የጨበጡ አገልጋዮችንም ጭምር በመጠቀም] ከክፉ መንፈሳውያን ሠራዊት አለቃ ከሆነው ከዲያብሎስ ጋር ነው፤ (ኤፌ.6፥12)፡፡ ውጊያውን በተመሳሳይ መንገድ በመቆም እንጂ በግል ማንነታችን ብቻ ማሸነፍ እንደማንችል መጽሐፍ ቅዱስ ደጋግሞ ነግሮናል፡፡
     “በሰው ልማድ ምንም እንኳ የምንመላለስ ብንሆን፥ እንደ ሰው ልማድ አንዋጋም፤ የጦር ዕቃችን ሥጋዊ አይደለምና፥ ምሽግን ለመስበር ግን በእግዚአብሔር ፊት ብርቱ ነው፤ የሰውንም አሳብ በእግዚአብሔርም እውቀት ላይ የሚነሣውን ከፍ ያለውን ነገር ሁሉ እናፈርሳለን፤ ለክርስቶስም ለመታዘዝ አእምሮን ሁሉ እንማርካለን፤” (2ቆሮ.10፥3-5) እንዲል፣ ሰይጣን የሚሰወርበትንና የሚሰውርበትን የክፋትን ምሽግ፣ የስህተትን ትምህርት፣ ርኩሰትና ኃጢአትን ሁሉ ለማፍረስና ለመደምሰስ ፍጹም የሆነ ብቃት ያለውና ጠንካራው መሣርያ ከእግዚአብሔር የምናገኘው ጦር ዕቃ ብቻ ነው፡፡

Friday 14 July 2017

ላ'ንተ ብቻ

የበገናው የመሰንቆው ኅብረ ዜማ
የዋሽንቱም የክራሩም የከበሮው ጥዑም ቃና
የግዕዛን ፉጨት የሕያዋን ቅኝት
የአምልኮ እልልታ የእንሰሳት የአራዊት
ላንተ ብቻ ይሁን ለክብር መንግሥትህ
ክብር ተጠቅልሎ አንተን ብቻ ያክብርህ!!!

Monday 10 July 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ሦስት)

Please read in PDf
3.    ይጣን፦ ብዙ ስሞች ያሉት ያሉት ሲሆን፣ ሰይጣን በዕብራይስጡ አሰናካይ፣ ስም አጥፊ፤ (ኢዮ.1፥6 ፤ ዘካ.3፥1 ፤ ማቴ.4፥10 ፤ ራእ.12፥9)፤ ዲያብሎስ ደግሞ ስም አጥፊ፣ ከሳሽ፤ ቤልሆር ማለት ደግሞ የማይረባ ከንቱ (2ቆሮ.6፥15)፤ አብዶንና አጶልዮንም አጥፊ (ራእ.9፥11) ተብሏል፤ በሌላ ሥፍራ ደግሞ የዚህ ዓለም ገዥ(ዮሐ.12፥311)፣ ወይም የዚህ ዓለም አምላክ (2ቆሮ.4፥11) ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በተለይም ደግሞ ስለተንኮለኛነቱና አታላይነቱ የቀደመው እባብ ወይም ታላቁ ዘንዶ(ራእ.12፥9)፣ ዛቻ ወዳጅና የሚያስፈራራ ስለመሆኑ ደግሞ “የሚያገሳ አንበሳ” ተብሏል፤ (1ጴጥ.5፥8)፡፡
     ሰይጣን ዋና ዓላማው ሰዎች ለጌታችን ኢየሱስ ያላቸውን ትኩረት ማስነፈግ ነው፡፡ ትኩረታቸውንና ፊታቸውን ከኢየሱስ ዘወር ባደረጉ ጊዜ ለማን እንደሚያደሉና ወደማን እንደሚያቀኑ በትክክል ያውቀዋል፡፡ ይህንንም ለማድረግ ስውር መረቡን ይዘረጋል፡፡ የክፋት መረቡንም ለመዘርጋት የሚራዱ ብዙ ኃይላትና ሠራዊት፣ ተባባሪዎችም አሉት፤ (ኤፌ.6፥10)፡፡ ከዚህም ባሻገር ልናጣጥልና ልንንቀው የማንችለው የክፋት ጥበብንም የተመላ ነው፡፡