Monday 29 December 2014

እኛ ኢትዮጲያውያን በአጼ ቴዎድሮስ እይታ …

      
                                  
                             Please read in PDF                       

       “እኛ ኢትዮጲያውያን” የሚለው ሃሳብ “ደምና አጥንታችንን ገብረንላታል” ለሚሉ አርበኞች ልብ የሚመላ ነገር አለው፤ በጥንት በሕገ ልቡና፣ ቀጥሎም በሕገ ኦሪት ከዚያም በክርስትና መኖሯን ለሚያምኑ ደፍረው የሚሉት ነገር አላቸው ፤ በአክሱምና በዛጉዌ የታነጹትን ሐውልትና ህንጻ አብያተ ክርስቲያናትን ለሚያደንቁ አርክቴክቸሮችና ሌሎች፥ እጃቸውን በአፋቸው ጭነው ብዙ የሚተነትኑት ነገር አላቸው፤ ሁሉም በየሙያውና በያለበት ደረጃ ስለኢትዮጲያችን ቢጠየቅ የሚለው ብዙ ብዙ አለው፡፡
     ሃሳቤ ግን ወዲህ ነው፤ አጼ ቴዎድሮስ በጥር 22 በ1858 ዓ.ም ለእንግሊዛዊቷ ንግሥት ለቪክቶሪያ በኢትዮጲያ ምድር ከታሠሩት የእንግሊዝ እስረኞች ጋር በተያያዘ፤ እንዲሁም ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ሲያስቀምጡ፦  “የኢትዮጲያን ሰዎች ድንቁርነታችነን ዕውርነታችነን ሣይሰሙት አይቀሩም ያማረ መስሎኝ ደፍሬ የላክሁብዎን ከፍቶብኝ (አጥፍቼ እንደሆነ) ቢገኝ ይምከሩኝ እንጂ አይክፉብኝ፡፡ እግዚአብሔር የመረጠዎ ንግሥት ዓይንዎ የበራ ነውና፡፡”(ጳውሎስ ኞኞ ፤ ዐጤ ቴዎድሮስ ፤ ግንቦት 1985 ፤ ቦሌ ማተሚያ ድርጅት ፤ አዲስ አበባ ፤ ገጽ.214)
    አሁንም በድጋሚ በሚያዝያ 10 ቀን 1858 ዓ.ም ለዚህችው ንግሥት ድጋሚ በጻፉት ድብዳቤ እኛን ኢትዮጲያውያንን እንዲህ ገልጠዋል፦ “ የኢትዮጲያ ሰዎች እውር ነንና ዓይናችነን ያብሩልነ፡፡ እግዚአብሔር በሰማይ ያብራልዎ፡፡” በማለትም በግልጥ አስቀምጠዋል፡፡ (ጳውሎስ ኞኞ ፤ ዐጤ ቴዎድሮስ ፤ ግንቦት 1985 ፤ ቦሌ ማተሚያ ድርጅት ፤ አዲስ አበባ፤ ገጽ 233)

Tuesday 23 December 2014

የትኩረት ጩኸት ትኩረትን ሲያደበዝዝ


                                  Please read in PDF              

     በአገራችን ትኩረትን የሚስበው ድርጊት እንጂ ዝግጅት አይደለም፤ አንድ ከባድና ዘግናኝ ድርጊት ሲፈጸም ብዙ ጊዜ ስሜቶቻችን ተጋግሎ መንጫጫት፤ ድርጊቱ እንዳይፈጸም ቀድመን ከመሥራት ይልቅ ከድርጊቱ በኋላ በጣም መጯጯህ ፣ ሰላማዊ ሰልፎች ፣ ብዙ ስብሰባዎች ፣ የአቋም መግለጫዎችና የስሜት ዕርምጃዎችም ይወሰዳሉ፡፡  ማሳያዎችን በምሳሌ ብናነሳ፦ በባለፈው ወር የአዋሽ ፓርክን በሚያቋርጠው ትልቁ የምሥራቅ ኢትዮጲያ መንገድ በጉዞ ላይ ሳለ በአንድ ቅጥቅጥ አይሱዙ ላይ በደረሰው አደጋ ከሐያ ሰባት ሰዎች በላይ የሞት አደጋ መድረሱን ሰምተን ሳናባራ፤ ወዲያውኑ በተወሰደው እርምጃ መንገዶች ላይ በተደረገው (በዋናው አስፓልት ላይ መኪናዎች በጉዟቸው እንዲያቀዘቅዙ ለማድረግ በተደረገው ሌላ የአስፓልት ጉማጅ ሥራ) በተወሰደው የስሜት ዕርምጃ ሌሎች የመኪና አደጋዎች መከሰታቸውን ከቦታው ሄዶ ማስተዋል ይቻላል፡፡
    አሁንም ሌላ ማሳያ ብናነሳ ፦ በባለፈው ወር ከተከሰተው ጆሮን ጭው ከሚያደርጉ ነገሮች አንዱ የእህት ሐና ላላንጎ ጉዳይ  ነው፡፡ ድርጊቱ ከዳር እስከዳር ብዙ በጣም ብዙ አነጋግሯል፡፡ ከወረዳ እስከ ሚኒስቴር ቢሮ ፤ ከሆስፒታል እስከ የፖሊስ መምሪያና ጣቢያዎች ፤ ከመንገድ ዳር “ታዛቢ” እስከመኪና አሽከርካሪዎች በዚህ ሂደት ውስጥ ያሉበትን ልልነትና ግድ የለሽነት በሚገባ አጢነናል፡፡ ጥቂት ስህተት ምን ያህል ዋጋ እንደሚያስከፍል አይተናል፡፡ የፖሊስ ዳተኝት ፣ የሆስፒታሎቻችን ከልክ ያለፈ ቸለተኝነት ድርጊቱን ከፈጸሙት የማይተናነስ መሆኑን ሌላ ምስክር ሳያሻ የአደባባይ ገመና ሆኗል፡፡

Thursday 18 December 2014

በመሠወሬ ነው!


                     Please read in PDF

ሺህ ሰልፍ ከፊቴ ፥ ትዕልፊት ከኋላ፤
እንደጉንዳን ፈልቶ ፥ እንዳʻንበሳ ቢያጓራ፤

Monday 15 December 2014

የብርሃን መልአክ የሚመስሉ አገልጋዮች(የመጨረሻ ክፍል)



4. አገልግሎቱን ለእግዚአብሔር ለቃሉ አደራ መስጠትን ያውቃል (ቁ.32)

                  “ብዙ ሰዎች የመሰከሩለትን ከእኔም የሰማኸውን ሌሎችን ደግሞ
                  ሊያስተምሩ ለሚችሉ ለታመኑ ሰዎች አደራ ስጥ።” (2ጢሞ.2፥1)

   አገልጋዮች የእግዚአብሔርን መንጋ የምንጠብቅ ሲመስለን እንስታለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ የኤፌሶንን ሽማግሌዎች (ጳጳሳት) “እናንተን ራሳችሁን … ለጸጋው ቃል አደራ ሰጥቻችኋችሁ” ሲላቸው እናያለን፡፡ የእግዚአብሔር መንጋ የሚጠፋው ወይም የሚጎዳው ከእግዚአብሔር በኃጢአቱ ሲለይ ወይም እግዚአብሔር ንስሐ ባለመግባቱ በኃጢአቱ ምክንያት ሲለየው  ነው፡፡ ያ እንዳይሆን መሪዎቹ ሕዝቡን ትክክለኛው የጸጋውን ቃል ወንጌል በማስተማር ሊመሩት ይገባል፡፡ በትክክል ሳይነግሩትና ሳያስተምሩት ሲቀር ግን ይጎዱታል ማለትም የመንግሥተ ሰማያት በር ይዘጉበታል፡፡
      ቅዱስ ጳውሎስ እርሱ ቀድሞ ወንጌልን ለመስበክ አደራ ከክርስቶስ ኢየሱስ እንደተቀበለ እንዲሁ፤ (ሐዋ.9፥1-16 ፤ 26፥16 ፤ 1ቆሮ.9፥17) አሁን ደግሞ እርሱ ለታመኑት ሲሰጥና የታመኑትም ለሌሎች ለታመኑ አደራ እንዲሠጡ ሲተጋ እናየዋለን፡፡ ወንጌል መስበክ አደራ ከሆነ አደራው ኃላፊነት ያለበት አደራ ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን መሪዎች ወንጌልን ኃላፊነት ተሰምቷቸው ከፍቅር በተነሳ ውዴታ እንጂ በምርጫ እንዲያገለግሉ አልተጠሩም፡፡

Tuesday 9 December 2014

የብርሃን መልአክ የሚመስሉ አገልጋዮች(ክፍል - አራት)




2. ለመንጋው ሁሉና ለራሱ ሊጠነቀቅ ይገባል፡፡(ቁ.28)

    ቅዱስ ጳውሎስ ቅዱስ ጢሞቴዎስን “ለራስህና ለትምህርትህ ተጠንቀቅ፥ በእነዚህም ጽና፤ ይህን ብታደርግ፥ ራስህንም የሚሰሙህንም ታድናለህና።” በማለት ይመክረዋል፡፡ በእርግጥ የሚያድን እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ አማኞች ወደጌታ በመምጣት ሕይወታቸው  ዕለት ዕለት በማደግ እግዚአብሔርን ወደመምሰል እንዲደርሱ አገልጋዮች ትልቁን ድርሻ አላቸውና፥ ለራሳቸውም፤ ለትምህርታቸውም ሊጠነቀቁ ይገባቸዋል፡፡ ጤናማውን ጉዞ እስከፍጻሜው ልንጓዝ የምንችለው ለትምህርታችንና ለምናስተምረው የእግዚአብሔር መንጋ መጠንቀቅ ስንችል ነው፡፡
    ጥቂት እርሾ ብዙውን ሊጥ እንደሚያቦካ (1ቆሮ.5፥16)፤ ጥቂት የተባለም ኃጢአት ወይም ክፉ ትምህርት ብዙውን መንጋ ከመበከል አይመለስም፡፡ እንደዋዛ የሚደረጉና የሚነገሩ ነገሮች በመንጋው ላይ ሊያሳርፉ የሚችሉት ተጽዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ ትላንት እንደዋዛ ሲነገሩ የነበሩ ተረታ ተረቶች፥ ዛሬ ወደቤተ ክርስቲያን ሾልከው ገብተው ለብዙ ምዕመናን የሕይወት መመሪያ እስከመሆን ደርሰዋል፡፡ በዚህ ሳያበቃ አሁንም ለመንጋው ባለመራራት የሚጻፉትና የሚሰበኩት ስብከቶች በቃሉ ሚዛንነት ልንፈትሻቸው፤ ቀለው ከተገኙ ልናስወግዳቸው ይገባናል፡፡

Tuesday 2 December 2014

የብርሃን መልአክ የሚመስሉ አገልጋዮች(ክፍል - ሦስት)



5. የሚነሱት ከመካከላችን ነው፡፡
     እውነተኛውና ለእግዚአብሔር የጨከነ አገልጋይ ሲጠፋ ክፉው አገልጋይ ከውጪ ወደውስጥ ወይም በብዛት ከመንጋው መካከል ይነሳል፡፡ ከመካከል የሚነሱ የሐሰት መምህራን በዋናነት የመሳታቸውና የማሳታቸው ምክንያት ከመሠረተ እምነት ትምህርት ጉድለት ነው፡፡ ገበሬ እርሻውን አለስልሶ ከዘራ በኋላ በየጊዜው መከታተል ይገባዋል፡፡ የሚከታተለው አለስልሶ የዘራው እርሻ የማይበቃ ሆኖ ሳይሆን አረምና እንክርዳድ ዋናውን ዘር እንዳይውጠው ነው፡፡ አረምና እንክርዳድ ገበሬው የዘራው አይደልም፤ እርሱ ያልዘራው ከመካከል የበቀለው አረም ግን የዘራውና ዋና ዘር ሊያጠፋው ይችላል፡፡ ስለዚህ በየጊዜው  ሊያርም ፤ ሊኰተኩተው ይገባዋል፡፡ በመንፈሳዊ አለም ደግሞ መልካሙ ገበሬ እግዚአብሔር ዘርን ከዘራ በኋላ መጥቶ ክፉን ዘር የሚዘራው ጠላት ዲያብሎስ ነው፡፡ (ማቴ.13፥28) ስለዚህ ልንተጋ ቃሉን በማጥናት ልንበረታ ይገባናል፡፡

Saturday 22 November 2014

ግብረ ሰዶማዊነትና የእኛ ዘመን አገልጋዮች


                          Please read in PDF                  

        ይህ ጽሁፍ በዚህ ብሎግ በመጀመርያ ሲወጣ ተቃዋሚዎች ገጥመውታል፤ በተቃውሞው ምክንያትም ለጊዜው ከዚህ ብሎግ ላይ ለማንሳትና ያለውን ነገር ለማጤን ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ ነገር ግን ቁጣውና ተቃውሞው ለእግዚአብሔር ስላላደላና ኃጢአትን ስላልተቃወመ ምንም ሳልቀንሰው ሙሉ ጽሁፉን እንዳለ መልሼ አውጥቼዋለሁ፡፡ ለእግዚአብሔር እንጂ ለሰው ፊት አናደላም፤ የሚያስጨንቀን የቤተ ክርስቲያን ቅድስናና ሸክም እንጂ በእግዚአብሔር ምህረት ላይ ለሚዘብቱና ለክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን መነቀፍ ግድ ለማይላቸው አይደለም!!!
     ስለግብረ ሰዶም ብቻ ሳይሆን በእግዚአብሔር ጉልበት ቤተ ክርስቲያንን ስለሚያሳድፍ ስለየትኛውም ነውር ለክርስቶስ አድልተን ከመገሰጽ ዝም አንልም፡፡ ግብረ ሰዶም አገር እያካለለ ለመሆኑ የቅርብ ሌላ ማሳያ ብናመጣ፤ ሬድዮ ፋና “የአመቱ የፍቅር አሸናፊ ግጥም” ብሎ በግዮን ሆቴል በሸለመው ሽልማትና በራሱ ሬድዮ በትላንትናው ዕለት የለፈፈው ከሴት ለሴት የተጻፈ “የፍቅር ግጥምን” ነው፡፡ መቼም በአገራችን የፍቅር ግጥም ብሎ ከሴት ለሴት የሚጻፍ ይኖራል ብሎ ማሰብ ወይ የአገርን ባህል መናቅ፤ ወይ ግብረ ሰዶምን መደገፍ እንጂ ሌላ ትርጉም አይሰጠውም፡፡  ይህንና ሌላም እየሰማን ዝም ለማለት የተቀበልነው አደራ አይፈቅድልንም፡፡ መልካም ንባብ፡፡ 
 ስለግብረ ሰዶማዊነት በሁለት የተለያዩ ክፍሎች መጻፌና በሁለቱ ክፍሎችም ለጊዜው የነበረኝን ሃሳብ ማጠቃለሌን አልዘነጋውም፡፡ ነገር ግን አሁንም ግብረ ሰዶማዊነት የቤተ ክርስቲያንን ቅድስና ከማርከስ፤ ምድራችንን ለከፋ ጉስቁልናና ርኩሰት አሳልፎ ከመስጠት ያላቆመ ፍጹም ወደመስፋፋት የሄደ ክፉ ርኩሰት ነውና ዳግም ይህንን ርዕስ ማንሳት አስፈልጎኛል፡፡ ለዚህ እውነታ ብዙ የቅርብ ጊዜ ማሳያ ብቻ ማንሳቱ በቂ ይመስለኛል፡፡
    ድርጊቱ የተፈጸመው በምስራቁ የሃገራችን ክፍል ነው፡፡ የሠላሳ ሁለት አመት አጐት የአራት አመት የወንድም ልጁን በእረኝነት ሥፍራ በመሄድ ጫት እንዲቅም ያግባባዋል፡፡ ህጻኑ እንቢ ቢልም ያስገድደዋል፡፡ ጫት እንዲቅም ካስገደደው በኋላ ልጁ ራሱን መቆጣጠር ሲያቅተው ልጁን የግብረ ሰዶም ጥቃት ይፈጽምበታል፡፡ የልጁ የሰገራ ማውጫ ሙሉ ለሙሉ ይቀዳዳል፡፡ ከሆዱ የወጣው የውስጠኛው የሰገራው ክፍል ሙሉ ለሙሉ የልጁን ጠረን ይለውጠዋል፡፡ ልጁ ፍጹም ራሱን ስቶ ሲወድቅ ከወደቀበት ቦታ ተሸክሞት ከወላጆቹ ጓሮ አምጥቶ ጥሎት ይሰወራል፡፡ ከዚያ በኋላ ብዙም ሳይቆይ የልጁ ህይወት ያልፋል፡፡

Friday 14 November 2014

በድል ነሺው ስምህ …


                             Please read in PDF

በጐነት ለዛ አጣ፤
ወዳጅ ከወዳጅም ፥ ፍቅሩ ሆነ ለበጣ፤
መልክ ብቻ ሆኖ፤
እምነት ከኃይል ጦሞ …
ኪሳራ ገነነ፤

Tuesday 11 November 2014

የብርሃን መልአክ የሚመስሉ አገልጋዮች (ክፍል - ሁለት)



3. ደቀ መዛሙርትን ወደኋላ ይስባሉ(ቁ.30)

   ጌታ ኢየሱስ በወንጌል “መስቀሉንም የማይዝ በኋላዬም የማይከተለኝ ለእኔ ሊሆን አይገባውም።” ብሏል፡፡  (ማቴ.10፥38) እኛ ሁል ጊዜ ከክርስቶስ በኋላ ነን፡፡ ተፎካካሪ ስላልሆንን ከጐኑ ፤ ወይም የተሻልን ሆነን ከኋላችን የምናስከትለው አይደለንም፡፡ እርሱ ሰባሪ ነውና ሁል ጊዜ ከፊት የሚወጣ ነው፡፡ (ሚክ.2፥13) ተመርቆ የተከፈተው አዲስ፤ ህያው መንገድና (ዕብ.10፥19) ቀድሞም በመንገዱ የሄደበት እርሱ ስለሆነ እኛ የእርሱን ፋናና ፍለጋውን የምንከተል ነን፡፡ (1ጴጥ.2፥21) ይህ ጉዞ የዕለት ተዕለትና ያለምንም ማቋረጥ ልናደርገው የሚገባን ነው፡፡(ሉቃ.9፥23)

Friday 7 November 2014

የብርሃን መልአክ የሚመስሉ አገልጋዮች(ክፍል - አንድ)


                                          Please read in PDF
    
     የመከራው አይነቱና መጠኑ ይለያይ እንጂ ክርስትና ያለመከራ የኖረበት ዘመን የለም፡፡ የትላንት ቄሳሮች ክርስቲያኖችን በማረድ ፤ የኋላ መናፍቃን የእውነትን ወንጌል በማጣመም፤ ፖለቲከኞችም ድርሳኖቻቸውን አግዝፈው መጽሐፍ ቅዱስን “ሊያንኳስሱ” ፤ ህሊናቸውን የሳቱ ፈላስፎች በወንጌሉ ቃል ሊሳለቁ ፤ ሳይንሳዊ ምርምር (ሁሉም አይደለም) ሐለወተ እግዚአብሔርን ሊቃረን … መልከ ብዙ ስህተቶችንና መከራዎችን በክርስትና ውስጥና ላይ ተስተናግዷል፡፡ ይህ ግን ክርስቶስንና ቤተ ክርስቲያንን የተቃወሙትን አደከመ እንጂ፤ ቤተ ክርስቲያንን እንደትክል ድንጋይ በሙሽራዋ ጽናት ዛሬም ህያው ምስክር ሆና አለች፡፡
    ከዚህ የሚከፋው ነገር ግን፥ ከውጪ ሆኖ በግልጥ የሚዋጋው የጠላት አሠራር ሳይሆን በስውር “ሌላ ወንጌል ሳይይዙ”(ገላ.1፥7) እንደብርሃን መልአክ (2ቆሮ.11፥14) ተገልጠው ሊያናውጡ የሚወዱቱ ናቸው፡፡ በዘመናት የሰይጣን ውጊያ ልዩ ልዩ ነው፡፡ ትላንት ጣዖት አቁሞ ያሰግድ የነበረው፤ ዛሬ ያንን ስልት ትቶ ጣዖትን የብርሃን መልአክ አልብሶ በእያንዳንዱ ልብ አቁሟል፡፡ ሰው ዛሬ ከእግዚአብሔር ጋር ላለመገናኘት የራሱ “የብርሃን ምክንያት” አለው፡፡ ያንን “ብርሃናዊ ምክንያት” በጸሎትና በመንፈስ ቅዱስ ሃሳብ ብንመረምረው ግን ጣዖት እንጂ ሌላ ትርጉም የለውም፡፡ ምንም ነገር ቢሆን ለእግዚአብሔር የሆነውን ነገር እንዲሰርቅብን አልተፈቀደለትምና፡፡(ማቴ.10፥37)

Friday 31 October 2014

ተጠርተናል ጥሪ


                               Please read in PDF
                                     
እግዚአብሔር አዳምን በመልኩ ሲፈጥረው፤
አዳም በራሱ መልክ ቃየልን ወለደው፤

Sunday 26 October 2014

ዘመን የሚያረጀው …


                                          Please read in PDF

ዘመንማ ጠብቷል፣ ፈክቷል በማለዳ፤
ቀንበር አለዝቦ፣ አንከባ’ሎ ፍዳ፤
ንጋቱ ፈንጥቋል፣ ጨለማውን ገፏል፤

Thursday 16 October 2014

የአብያተ ክርስቲያናት ሐሳብ ያስጨንቀናል?



     የመጽሐፍ ቅዱስ ሐሳብ ለተነገረለት ሳይሆን ላልተነገረለት ነገር በግድ በማስጨነቅ ከሚተረጐሙት ክፍሎች አንዱ ነው፡፡ የመጻህፍትና የእግዚአብሔርን ኃይል ስለማናስተውል ብዙ ጊዜ በስህተት ወጥመድ እንያዛለን፡፡(ማቴ.22፥29) ቤተ ክርስቲያን በመመስረት ከሌሎች ሐዋርያት ግንባር ቀደሙ ሐዋርያ፥ ቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡ ለዚህም አገልግሎቱ ሦስት በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱ አንድ ደግሞ በታሪክ የተረዳ በድምሩ አራት ታላላቅ ሐዋርያዊ ጉዞዎችን አድርጓል፡፡ በእነዚህ ጉዞዎቹ እጅግ ብዙ አብያተ ክርስቲያናት መሥርቷል፡፡  (አንደኛው ሐዋርያዊ ጉዞ ሐዋ.13፥4-18፥28 ፤ ሁለተኛው ሐዋርያዊ ጉዞ 15፥39-18፥22 ፤ ሦስተኛው ሐዋርያዊ ጉዞ 18፥23-21፥17 ያለው ነው፡፡)

Monday 13 October 2014

ደመወዛችሁ ይብቃችሁ! (ሉቃ.3፥14)

       
                                                  Please read in PDF

 ለዚህች አጭር ጽሁፍ መነሻ የሆነኝ የምወደው፤ በአክብሮትም የሚያስተምረኝ ወንድሜ ከነገረኝ ነገር በመነሳት ነው፡፡ “አየር መንገድ ላይ ነው፡፡ ወንድሜ ሰው ለመጠበቅ እዚያ ከተቀመጠበት ከጐኑ ‘የተፈራና የተከበረ’ አገልጋይ ተቀምጦ በኪሱ ስልክ ያወራል፡፡ የሚደውልለት ለአገልግሎት ከኢትዮጲያ ውጪ እየጋበዘው ነው፡፡ ግና ሲጀምር ለአገልግሎት ከአንድ አገር ተጠርቶ በእርሱ በኩል ሌላ አገልጋይ የጠየቀው ጥያቄ ‘በአሪፍ ይሸኛሉ ወይ?’ ብሎ ነው፡፡ … ቀጠለ በአሪፍ የማይሸኙ ከሆነ ላይመጣ እንደሚችል በሚያቅማማ ድምጸት መለሰ፡፡ ወይ በአሪፍ መሸኘት!

Thursday 9 October 2014

“ታይታኒክን ራሱ እግዚአብሔር እንኳ አያሰጥማትም!!!”

   

                                               



 በሰው እጅ ተንቀሳቃሽ ሆነው ከተሠሩ ነገሮች ተወዳዳሪ ያልተገኘላትን ኤም. ኤስ ታይታኒክ መርከብን በባለቤትነት የያዛት ጆን ፒርፖንት በ1912 ዓ.ም ስለታይታኒክ መርከብ የተናገረውን ቃል ነው በርዕስነት የወሰድኩት፡፡ ስለመርከቢቱ ብዙ የተባለ ስለሆነ እኔ ስለዚያ የምለው ነገር የለኝም፤ ይሁንና የመርከቢቱ ባለቤት የተናገረው ቃል እጅግ ድፍረትና “መዓት አውርድ” መሆኑን መርከቢቱ ያሰጠመቻቸውን 1522 ሰዎችን በሞት፤ በንብረትም ላይ ካደረሰችው ጥፋት መረዳት ይቻላል፡፡

Saturday 4 October 2014

አሻጋሪህን ጥራ!


                                      Please read in PDF                                

ትዕዛዝን ከሰጠ ተሻገሩ ብሎ፣
መሻገር ነው እንጂ በታንኳ ቸኩሎ፣

Tuesday 30 September 2014

ሞት ደጅ ደጄን እያየ …


                          Please read in PDF              
                                     
ደምህ ነው ህይወቴ ፣ መከራህ ጉልበቴ፤
ህማምህ ድጋፌ ፣ መድከምህ ብቃቴ፤

Thursday 25 September 2014

የመስቀሉ ቃል


                                   

                                 
      የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉ አህዝብ ሞኝነት፤ ለአይሁድም ማሰናከያ ነው፡፡ ምክንያቱም አይሁድ የመስቀሉን ቃል  በእንጨት ላይ መዋልና መሰቀልን እንደተረገመ ስለሚቆጥሩት ነው፡፡(ዘዳግ.21፥23 ፤ ገላ.3፥13) ነገር ግን ክርስቶስ ኢየሱስ በመስቀል ላይ በመሰቀሉ “እኛ በእርሱ ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኃጢአት ያላወቀውን እርሱን ስለ እኛ … ” እንደኃጢአተኛ የተቆጠረ ሆነ፡፡(2ቆሮ.5፥21) ለግሪክ ሰዎች ደግሞ በእንጨት ላይ መሰቀል የአማልክትን ክብርና ልዕልና ዝቅ የሚያደርግና እንደድኩም የሚያስቆጥር ስለሆነ ፈጽሞ አይቀበሉትም፡፡
      ቀድሞ የጥንት ፋርሶች በኋላም ሮማውያን አንድን ወንጀለኛ በመስቀል ላይ በመስቀል የሚቀጡት “ኦርዝሙድ” የተባለ የመሬት አምላካቸው እንዳይረክስባቸው በመጠንቀቅና ለአማልክታቸው ክብርን ለመስጠት በማሰብ ነበር፡፡(አባ ጐርጐርዮስ(ሊቀ ጳጳስ)፤ የኢትዮጲያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ 3ኛ ዕትም፤ 1991፤ አዲስ አበባ፤ ትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ድርጅት፤ ገጽ.104)

Monday 22 September 2014

ሦስቱ ባህታውያን(የመጨረሻ ክፍል)


                                            Please read in PDF
      
     ነገር ግን ሁለተኛው ባህታዊ ቃላቶቹን አቀላቅለው አሳስተው ተናገሩ፡፡ ራቁታቸውን ያሉት ረዥሙ ባህታዊም አጣርተው አልደገሙትም፡፡ ጢማቸው አፋቸውን ሸፍኖት ስለነበር የተጣራ ድምፅ ሊያወጡ አልቻሉም፡፡ ጥንታዊው ደግሞ ጥርሶቻቸው ስለረገፉ በግልጽ የማይሰማ ነገር ነው ያጉተመተሙት፡፡
   አቡኑ እንደገና ደገሙላቸው፡፡ ባህታውያኑም እንደገና ደገሙት፡፡ አቡኑ በትንሽ ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ባህታውያኑም በአጠገባቸው ቆመው አፍ አፋቸውን አፍጠው እየተመለከቱ የሚሏቸውን ይደግሙላቸው ነበር፡፡ ቀኑን ሙሉ እስከአመሻሽ ድረስ ሊያስተምሯቸው ደከሙ፡፡ አንዲቷን ቃል አስር፣ ሃያ፣ መቶ ጊዜ እየመላለሱ አስጠኗቸው፡፡ ቃላት እየተቀለቀሉባቸው ሲቸገሩ ያርሟቸውና እንደገና ከመነሻው ያስጀምሯቸዋል፡፡
     የጌታን ጸሎት ሙሉ ለሙሉ እስከሚያስተምሯቸው ድረስ አቡኑ ከባህታውያኑ ዘንድ ቆዩ፡፡ በመጨረሻም ያለ አቡኑ ድጋፍ እያንዳንዳቸው በራሳቸው ሙሉ ጸሎቱን ወረዱት፡፡
    አቡኑ ወደ መርከቡ ሊመለሱ ሲነሱ ጨለማው እየከበደ ከባህሩም ጨረቃ እየወጣች ነበር፡፡ ባህታውያኑን ሲሰናበቱ ሁሉም እስከመሬት አጐንብሰው ሸኟቸው፡፡ እሳቸውም እያንዳንዳቸውን ካጐነበሱበት ቀና እያደረጉና እያቀፏቸው ባስተማሯቸው መሠረት እንዲጸልዩ ካዘዟቸው በኋላ ወደ ጀልባዋ ገቡ፡፡

Friday 19 September 2014

ሦስቱ ባህታውያን (ክፍል - ሁለት)

    
        Please read in PDF

       አቡኑ ከመርከቢቷ የፊት ጫፍ ላይ ወንበር ቀርቦላቸው ሲቀመጡ ሌሎቹም ሁሉ መጥተው ወደ ትንሿ ደሴት መመልከታቸውን ቀጠሉ፡፡ ጥሩ የማየት ችሎታ ያላቸው ሰዎች በደሴቷ ላይ የሚገኙትን አለቶችና የጭቃ ጎጆዋንም ማየት ችለው ነበር፡፡ ከመሃላቸው አንዱ ሦስቱን ባህታውያን ጭምር መለየት ችሎ ነበር፡፡ ካፒቴኑ አጉሊ መነጽር አምጥቶ ከተመለከተ በኋላ ለአቡኑ እየሰጣቸው፦
   “ትክክል ነው፡፡ ከባህሩ ጠረፍ ላይ ከትልቁ አለት እንዲህ ወደ ቀኝ ሲሉ ሦስቱ ባህታውያን ቆመው ይታያሉ፡፡” አለ፡፡
    አቡኑ በመነጽር ተመለከቱ፡፡ ወደትክክለኛው አቅጣጫም አዞሩት፡፡ የተባለው እውነት ነው፡፡ ሦስቱም እዚያው ቆመዋል፡፡ አንደኛው ረዥም ሌላኛው ትንሽ አጠር የሚሉና ሦስተኛው ደቃቃ ትንሽ፡፡ ሦስቱም ከባህሩ ጠረፍ ላይ እጅ ለእጅ ተያይዘው ቆመው ነበር፡፡

Monday 15 September 2014

ሦስቱ ባህታውያን (ክፍል አንድ)



አጭር ልብወለድ
(ምንጭ ብሪቱ መጽሔት ጥር - የካቲት 1991)
(ደራሲ፦ ሊዎ ቶልስቶይ)
(ተርጓሚ፦ ሁነኛው ጥላሁን)

“አሕዛብም በመናገራቸው ብዛት እንዲሰሙ ይመስላቸዋልና ስትጸልዩ እንደ እነርሱ በከንቱ አትድገሙ።ስለዚህ አትምሰሉአቸው፤ ሳትለምኑት አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና።” (ማቴ.6፥7-8)

     አቡኑ ከአርካንጌልስክ ከተማ ወደ ሶሎቬትስኪ ደሴት በመርከብ እየተጓዙ ነበር፡፡ ቅዱሱን ሥፍራ ለመሳለም የሚሄዱ ምዕመናንም አብረዋቸው ነበሩ፡፡ የነፋሱ አቅጣጫ አመቺ፣ አየሩም ማለፊያ ነበረ፡፡ ባህሩም ጸጥ ብሏል፡፡ ምእመናኑ ገሚሱ ጋደም ብለው ከፊሉም ከያዙት ስንቅ እየቀማመሱ የተቀሩትም በቡድን በቡድን ተቀምጠው እርስ በእርስ ያወራሉ፡፡ አቡኑ ከነበሩበት ተነስተው ወደ መርከቡ መተላለፊያ መራመድ  ጀመሩና ወደጫፉ ሲቃረቡ ሰብሰብ ያሉትን ሰዎች አዩዋቸው፡፡ አንድ ባላገር ወደባህሩ እያመለከተ አንድ ነገር እያሳያቸው ሲናገር ሰዎቹ ያዳምጡት ነበር፡፡ አቡኑ ቆም ብለው ባላገሩ ወደሚያመለክትበት በኩል ተመለከቱ፡፡ በፀሐይ ከሚያብረቀርቀው ባህር በስተቀር ምንም የሚታይ ነገር አልነበረም፡፡ ወደሰዎቹም ጠጋ ብለው ባላገሩ የሚለውን ማዳመጥ ጀመሩ፡፡ ባላገሩ አቡኑን እንዳየ ባርኔጣውን በማውለቅ ንግግሩን አቋርጦ ፀጥ አለ፡፡ የሚያዳምጡትም ሰዎች ባርኔጣዎቻቸውን በማንሳት በአክብሮት ተቀበሏቸው፡፡
    “በመምጣቴ አትጨነቁ ወዳጆቼ” አሉ አቡኑ፡፡ ወደባላገሩም ፊታቸውን አዙረው “የመጣሁት አንተ የምትነግራቸውን ለመስማት ብዬ ነው” አሉት፡፡

Tuesday 9 September 2014

የተወደደችው የጌታ አመት (ሉቃ.4፥19)



እንኳን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላም በፍቅር አሸጋገራችሁ!!!

    ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ያለማቋረጥ ከብዙ ህዝብ ጋር ለአምልኰ በመገኘት ለተከታዮቹ ደቀ መዛሙርት የሚደነቅ ምሳሌ የሚሆን ልምድ አለው፡፡(ማቴ.13፥54፤ ማር.1፥21፤ ሉቃ.4፥16፤ ዮሐ.7፥14) ጌታ ለጸሎትና ቃሉን ለማስተማር ዘወትር “መሰብሰብን ባለመተው” ለደቀ መዛሙርቱ አብነት ሆኗል፡፡(ዕብ.10፥24) ዘወትር በእግዚአብሔር ፊት ለጸሎት፤ ቃሉን ለመመርመርና ለማስተማር መሆንን ጌታ በእውነት እኛንም አስተምሮናል፡፡ ናዝሬት ጌታን ለመቀበል ፈቃደኛ ባትሆንም እርሱ ግን ወዳደገባትና ወደሚያውቃት ከተማ ምኩራብ መጥቶ አስተማረ፡፡ ዕድገታችንን፣ ማንነታችንን፣ ገመናችንን፣ ልጅነታችንንና፣ ውድቀታችንን … ምናልባትም “ልካችንን” በሚያውቁን ሰዎች ፊት ማገልገል ከባድ ህመም ይኖርበት ይሆናል፤ ጌታ ግን አድርጎታልና ልጆቹ በህይወቱ ልንታዘዝ፤ ህይወቱም ሊያስተምረን ይገባል፡፡
    ጌታ  ወደምኩራብ በገባ ጊዜ የኢሳይያስን ትንቢት ጥቅልል አንስተው ሰጡት፡፡ እርሱም ተነስቶ መጽሐፉን በመተርተር ማንበብ ጀመረ፡፡ አይሁድ ምንም እንኳ ወደ ተስፋው ፍጻሜ ባይደርሱም፤ የእግዚአብሔርን ቃል የማንበብ ብቻ ሳይሆን መጻህፍትን በመቅደሱና በየምኩራቦቻቸው በአግባቡ የማስቀመጥ ልማድ ነበራቸው፡፡ በምኩራባቸው የእግዚአብሔር ቃል ጥቅልል ትልቁንና የመጨረሻውን ሥፍራ በክብር ይይዛል፡፡ ትልቅና የመጨረሻው አምልኰ ለእግዚአብሔር ቃልና ላስተማረን ትምህርቱ ልዩ ክብርን በመስጠት መታዘዝ ነው፡፡ የብዙዎቻችን ቤት “መጻህፍት መደርደርያ” የተመሉት በልቦለድና በፍልስፍና “ጥቅልል ጽሁፎች” ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ቃል ቸል በማለት ለሌሎች “ፍጡራን ጥቅልሎች” ትልቅ ክብርና ሥፍራ የሰጠ ትውልድ ይህ የእኛ ዘመን ትውልድ ነው ብል ያልተጋነነ እውነት ነው፡፡

Tuesday 2 September 2014

ማስተስረያውን ክዶ


                               Please Read in PDF 


ሳይጐድል ደምግባቱ፣ አምሮ እንደደመቀ፤
ትኩስ ሥጋነቱ፣ ግሎ እንደሞቀ፤
ሸጋ ቆንጆነቱ፣ ጉድ አጀብ አስብሎ፤
ከደሙ ቤዛነት፣ ከ‘ርሱ ተነጥሎ፤

Thursday 28 August 2014

የመቶ አለቆቹ (የመጨረሻ ክፍል)





4. የመቶ አለቃው ዩልዮስ (ሐዋ.27፥43)

“የመቶ አለቃው ግን ጳውሎስን ያድነው ዘንድ አስቦ ምክራቸውን ከለከለ … ”
      ቅዱስ ጳውሎስ ለቁጥር በሚታክቱና ምላሳቸው በሳለ ከሳሾች መካከል “እየተብጠለጠለ” ቅንጣት ታህል አለመፍራቱን ሳስብ የጌታ ኢየሱስ “ … አሳልፈውም ሲሰጡአችሁ፥ የምትናገሩት በዚያች ሰዓት ይሰጣችኋልና እንዴት ወይስ ምን እንድትናገሩ አትጨነቁ፤ በእናንተ የሚናገር የአባታችሁ መንፈስ ነው እንጂ፥ የምትናገሩ እናንተ አይደላችሁምና፡፡” የሚለው የትንቢት ቃል መፈጸሙን ትዝ ይለኝና ልቤ ይረካል፡፡(ማቴ.10፥19-21) የእስያ አይሁድ፣ የኢየሩሳሌም አይሁድ፣ ጠርጠሉስ፣ ሊቀ ካህናቱ ሐናንያ … ስለእርሱ በጎነት የላቸውም፡፡ ፊስጦስም እንደቀደሙት ባዕለ ሥልጣናት ክፉ ልማድ አይሁድን ደስ ለማሰኘት ጳውሎስ በኢየሩሳሌም ተመልሶ እንዲዳኝ ይጐተጉተዋል፡፡(ሐዋ.25፥9፤21)
        ቅዱስ ጳውሎስ ነገሩ እንዳላማረ፤ ፊስጦስ ራሱ ወደአይሁድ እንዳደላ ያወቀ ይመስላል፡፡ አሁን በቆመበት የሮማ የፍርድ ችሎት ፊት መዳኘት እንደሚፈልግ በጽናት ተናገረ፡፡ ምክንያቱም በአይሁድ ሸንጎ ፊት ቢዳኝ የልባቸውን ክፋት ያውቀዋል፡፡ ይገድሉታልና፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ለሌለው ሞት ራሱን አሳልፎ አልሰጠም፡፡(ዮሐ.8፥59) ጳውሎስ “ሰማዕትነት አያምልጠኝ” ብሎ ለስንፍና ሞት ሳይሸነፍ ወደቄሳር ይግባኝ በማለት በሮማዊ ዜግነቱ የተሰጠው መብቱን ተጠቀመበት፡፡(ሐዋ.25፥11)

Monday 25 August 2014

የመቶ አለቆቹ (ክፍል አራት)



የሮማ መቶ አለቆች
3.2. በሰፈሩ ውስጥ(ሐዋ.23፥10)

       ቅዱስ ጳውሎስ ከመገረፍና ጭካኔ ከተመላበት ድብደባ በኢየሱስ መንፈስና ብርታት፤ በየመቶ አለቃውም ቅንነት ተርፏል፡፡ በማግስቱ ሻለቃው አይሁድ እርሱን የከሰሱበትን እርግጡን ምክንያት ምን እንደሆነ ለማወቅ አስቦ ከፈታው በኋላ፤ ሸንጎውንና የካህናት አለቆችን እንዲሰበስቡ አዞ፤ ጳውሎስን በፊታቸው አቆመው፡፡ የአይሁድ ሸንጎ እንዲሰበሰቡ የተፈለገበት ምክንያት ሻለቃው የጳውሎስን ጥፋት ማወቅ ስለተሳነው የእርሱ ወገኖች እንዲያጣሩ ነበር፡፡ ግን ዳኝነቱ ቀድሞ በአድሎአዊነት አጋድሏል፡፡
   ቅዱስ ጳውሎስ በሸንጎው ፊት በቆመ ጊዜ ሁለት የማይስማሙ ወገኖች ጳውሎስን ለመክሰስ ግን ተስማምተው ቆሙ፡፡ ሁል ጊዜ ይደንቀኛል፡፡ የጌታ የሆኑ ክርስቲያኖችን ለመግደል፤ ለማሳደድ፤ ለመክሰስ ሁለት ፈጽሞ የማይስማሙ አካላት ይፋቀራሉ፡፡ የዚህ ጽሁፍ ጸሐፊ በሁለት ፍጹም ተቃራኒ የእምነት አካላት የተከሰሱ አማኞችን የአለማዊ ፍርድ ቤት ችሎት እየደነቀው የማየት ዕድል አጋጥሞታል፡፡ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን አብረው ለመኖር አይስማሙም፣ ይበላላሉ፤ ክርስቶስ ኢየሱስንና እንደጳውሎስ ያሉ አማኞችን ግን ለመክሰስ ከባልና ሚስት ይልቅ ይዋሃዳሉ፡፡

Thursday 21 August 2014

በድንግል ማርያም ላይ የአይሁድ አሽሙር (የመጨረሻ ክፍል)



     አረጋዊው ቅዱስ ስምዖን የናዝሬቱን ህጻን ኢየሱስን ለግዝረት ወደቤተ መቅደስ በእናቱ ክንድ ታቅፎ በወጣ ጊዜ፤  ህጻኑን  ከእናቱ ክንድ ተቀብሎ የደስታና የሚያስጨንቅ ትንቢት ለህጻኑና ለእናቲቱ ተናገረ፡፡ እንዲህም አለ፦   “እነሆ፥ የብዙዎች ልብ አሳብ ይገለጥ ዘንድ፥ ይህ በእስራኤል ላሉት ለብዙዎቹ ለመውደቃቸውና ለመነሣታቸው ለሚቃወሙትም ምልክት ተሾሞአል፥ በአንቺም ደግሞ በነፍስሽ ሰይፍ ያልፋል አላት።”(ሉቃ.2፥35) እመቤታችን ጥልቅ የመከራ ሥቃይ እንደምትቀበል የሚያመለክትና፤ ኢየሱስ ገና በስምንተኛ ቀኑ ሊሞት እንዳለው ለመጀመርያ ጊዜ ተነገረለት፡፡
     በራስ የሚደርስን መከራንና ስቃይን ገና በልጅነት መስማት ከማስደንገጥ አልፎ ያሰቅቃል፡፡ ድንግል ማርያም በነፍሷ ሰይፍ ማለፍ የጀመረው ጌታን መጽነሷ ከታወቀባት ከሦስት ወር ቆይታ በኋላ ከኤልሳቤጥ ዘንድ ወደናዝሬት ከመጣች በኋላ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ምክንያቱም አይሁድ የጌታ በመንፈስ ቅዱስ አሠራር ከድንግል ማርያም መወለድ ሲያስተምር በነበረበት ዘመኑ እንኳ አልተቀበሉትምና፡፡
      ጌታ “አባታችን አብርሃም ነው” ብለው በባዶ ትምክህት የሚመኩትን አይሁድ “የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ አብርሃም የሠራውን ትሠሩ ነበር፡፡ … እናንተ የምታደርጉት አባታችሁ ዲያብሎስ የሚያደደርገውን ነው” (ዮሐ.8፥38፤44) ባላቸው ጊዜ የመለሱት መልስ የአሽሙር ስድብ ነበር፡፡

Monday 18 August 2014

“ … እርሱን ስሙት” (ማቴ.17፥5)



እንኳን ለደብረ ታቦር መታሰቢያ በዓል አደረሳችሁ!!!



    ቃሉን የተናገረው አብ ነው፤ የተነገረለት ደግሞ ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ፡፡ … የሰው ልጅ “ምን እንደሚሰማ እዝነ ልቡናውን አለመጠበቁ” (ማር.4፥24) የህይወት ዘመኑን በጭንቅ እንዲጓዝ፤ ፈቃዱም ከፈጣሪው ይልቅ ወደፍጡር እንዲያዘነብል፤ ሊሰማ የሚገባውን የበላዩን ጌታ ትቶ ከጎን ያለችውን “ወዳጅ ሚስቱን” መስማቱም ማንነቱን ድካም፤ እሾህና አሜኬላ ደግሞ ዙርያውን ለመከበቡ ምክንያት ሆኗል፡፡(ዘፍ.3፥10-21)
     አዳም ሁሉን አዋቂውንና ሰምቶ ከመመለስ ቸል የማይለውን ጌታ አለመስማቱ፥ ለማይሰማውና በጭካኔ ለተሞላው ለሰይጣን አገዛዝ ማንነቱንና ነጻነቱን አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ የእስራኤል ልጆች ወደእግዚአብሔር እረፍት ያልገቡት ጌታ እግዚአብሔር በድምፁና በሙሴ አማካይነት እየተናገራቸው ከመስማት ይልቅ “እግዚአብሔር በመካከላችን ነውን ወይስ አይደለም?”(ዘጸ.17፥7)፤ “ … ወደዚህ ክፉ ስፍራ ታመጡን ዘንድ ከግብፅ ለምን አወጣችሁን? ዘርና በለስ ወይንም ሮማንም የሌለበት ስፍራ ነው የሚጠጣም ውኃ የለበትም።”(ዘኅ.20፥5-6) ብለው ፍጹም ድምጹን እየሰሙ እግዚአብሔርን በአመጻ ቃል በማስመረራቸውና አልታዘዝ በሚል ልብ በመከራከራቸው ነው፡፡(ዕብ.3፥7)

Saturday 16 August 2014

የመቶ አለቆቹ (ክፍል ሦስት)




3. የሮም መቶ አለቆች
3.1. በማረፊያው ሥፍራ (ሐዋ.22፥24)
     ቅዱስ ጳውሎስ ወደኢየሩሳሌም ጉዞ ከመጀመሩ በፊት የተነገረበት ትንቢት አስጨናቂ ነው፡፡(ሐዋ.21፥10-14) እንደሚገረፍና ለአህዛብ ተላልፎ እንደሚሠጥ ቢያውቅም፤ ጨክኖ ወደኢየሩሳሌም እየወጣ፦ ለሮሜ ቤተ ክርስቲያን “ለኢየሩሳሌምም ያለኝ አገልግሎቴ ቅዱሳንን ደስ የሚያሰኝ ይሆን ዘንድ ጸልዩ።”(ሮሜ.15፥33) በማለት እንዲጸልዩለት ያሳስባል፡፡ ጸሎቱና ጸሎታቸው ተሰምቶ “ወደ ኢየሩሳሌም በደረስን ጊዜ ወንድሞች በደስታ ተቀበሉን።” ብሎ ጸሐፊው ያስረግጠዋል፡፡(ሐዋ.21፥17)
   ሐዋርያው በኢየሩሳሌም የሚታወቀው “የጌታን ደቀ መዛሙርት እንዲገድላቸው ገና በመዛቱ፤ በቅዱሳንም ላይ ብዙ ክፉ በማድረጉ”ና (ሐዋ.9፥1፤13) ለኦሪት ህግ እጅግ በመቅናቱ ነው፡፡ አሁን ግን ታሪክ ተለውጦ ያሳድድ በነበረው በዚያ ነገር መሰደድ ጀምሯል፡፡ ብዙዎች ወደኢየሩሳሌም እንዳይሄድ አብዝተው የለመኑት ስለዚህ ነገር ነው፡፡ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ግን ለእስራት ብቻ ሳይሆን በኢየሩሳሌምም እንኳ እንዲሞት ልቡን አስጨከነ፡፡ አገልግሎት ሰዎች ባዩልን አልጋ በአልጋ በሚመስለው ይቀናችኋል ቢሉንም ጌታ ባየልን በእሾሁና በጐርባጣው መንገድ በደስታ የሚቀበሉ እጆችን ያሰናዳል፡፡ ምስክርነትና ንስሐ በተካደበትና በተበደለበት መንገድ ሲሆን ብዙ ሥራ ይሠራል፡፡ በግልጥ ያሳደደውን ጌታን ባሳደደባትና ብዙዎችን በበደለባት ከተማ ቅዱስ ጳውሎስ በዚያች ከተማ ተገኝቶ ታላቅ ምስክርነትን መሰከረ፡፡ በአደባባይ ያሳደደው በአደባባይ ተሰደደ፡፡ ዛሬ ግን በዘፈን፣ በከህደት ትምህታቸው፣ በፖለቲካ … መርዝ ብዙውን ህዝብ በአደባባይ የበደሉ ንስሐቸውን በጓሮ መጨረሳቸውን ከየት እንደተማሩት ግራ ይገባል፡፡ እውነተኛ ንስሐና ምስክርነት በተሠራበት በዚያው መንገድ ቢሆን ብዙ ምህረት ከጌታ በሆነችልን ነበር፡፡

Wednesday 13 August 2014

ድንግል ማርያምና የአይሁድ አሽሙር(ክፍል ሁለት)



ፈጣን ጉዞ ወደ ተራራማው የኤፍሬም አገር
   
    ድንግል ማርያም “እንደቃልህ ይሁንልኝ” ባለች ጊዜ እንደመንፈስ ቅዱስ አሠራር ህጻኑ በማህፀኗ ተፀንሷል፡፡ ይህ ነገር ከሆነ በኋላ ሳትቆይ ወደ ተራራማው አገር ወደ ይሁዳ ወደዘካርያስ ቤት ተጓዘች፡፡ ከመልአኩ አንደበት የሠማችው የኤልሳቤጥ መፅነስ ሳያስደምማት አይቀርም፡፡ በእርግጥም ዝጉ ማህፀን ሲከፈት፤ አይቻልም የተባለው ሲቻል፤ አይሆንም ተብሎ የተደመደመው ሆኖ ሲታይ በእርግጥ ያስደምማል፡፡ ደስታ የበዛላቸው በአንድ ተገናኙ፡፡ “አንዱ ለአንዱ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው” እያሉ ሊያወሩ፡፡ አዎ! ሠላምታቸው እንኳ ለእግዚአብሔርን ክብርና አምልኮን በመስጠት የደመቀና የሚማርክም ነው፡፡

Friday 8 August 2014

ድንግል ማርያምና የአይሁድ አሽሙር(ክፍል አንድ)




    
እመቤታችን ድንግል ማርያም በጌታ ያመነች ብጽዕት ናት፡፡(ሉቃ.1፥45) ከዳዊት ቤት ወገን የምትሆን ድንግል ብላቴና(ኢሳ.7፥13) ዕድሜዋ ወጣት፣ የገሊላ ናዝሬት ወደምትሆን … “ብዙ ገሊላ አለና ከዚያ ሲለይ እንተ ስማ ናዝሬት፤ ብዙ ደናግል አሉና እንተ ተፍኀረት ለብእሲ ዘስሙ ዮሴፍ፤ ብዙ ዮሴፍ አለና ከዚያ ሲለይ ዘእምቤተ ዳዊት አለ፡፡”(ወንጌል ቅዱስ ከቀድሞ አባቶች ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው ንባብና ትርጓሜው፤1997፤ ትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት፤ አዲስ አበባ፡፡) ኑሮዋም ባላመኑና በክፉዎች መካከል ቢሆንም(ሉቃ.1፥26) በእግዚአብሔር የምታምን፤ የእስራኤልን አምላክ ብቻ በመፍራት የምታመልክ ነበረች፡፡ ድንግል ማርያም ምንም መልካምነት በሌለባት ናዝሬት(ዮሐ.1፥47) የሚደነቅ መልካም ነገር ተገኝቶባታል፡፡
የመልአኩ ገብርኤል ብሥራት አጭር ቅኝት
    ወደገሊላ ናዝሬት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ ሲወርድ፤ የሄደው ወደአንዲት፤ ማርያም ወደምትባል ድንግል ሴት ነው፡፡(ሉቃ.1፥27) ይህ ቃል እግዚአብሔር በየትኛውም ክፉ ዘመንና ሁኔታ ውስጥ የራሱ የሆኑትን ፍጹም ጠብቆ እንደሚያኖር ያሳየናል፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ጥበብ ከሰው ህሊናና ማስተዋል በላይ የሚደንቅ ነው፡፡ ቅዱስ ኤልያስ በእርሱ ዘመን ጣዖት ተስፋፍቶ ሰው ሁሉ በዓልን ይከተል ነበር፡፡ ከእርሱ በቀር ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ያለ አልመሰለውም፡፡ ነገር ግን ነቢዩ ቅዱስ ኤልያስ በማያስተውለውና በማያውቀው መንገድ እንደኤልያስ “ከእስራኤል ጕልበታቸውን ለበኣል ያላንበረከኩትን ሁሉ፥ በአፋቸውም ያልሳሙትን ሁሉ፥ ሰባት ሺህ ሰዎች ለእኔ አስቀርቼአለሁ።”(1ነገ.19፥9፤18)፤ሮሜ.11፥5) ያለ እግዚአብሔር፤ በናዝሬትም በጸጋው የመረጣትን ቅሬታ፤ ድንግል ማርያምን እናገኛለን፡፡

Saturday 2 August 2014

ብትሮጥም አክሊል የማትደፋው …


Please read in PDF

ፍቅርና ርህራሄ፣ ደስታና ቸርነት፤
የውሃት፣ ቅንነት፣ የበዛ ምህረት፤
ለማድረግ ምክንያቶች የምትደረድረው፤
እኔ በሚል ብቃት ለማድረግ ‘ም‘ጥረው፤
እንዳይመስልህ ፍጹም አንተ የምትችለው፡፡

Tuesday 29 July 2014

የመቶ አለቆቹ (ክፍል ሁለት)


2. የቂሳርያው የመቶ አለቃ ቆርኔሌዎስ(ሐዋ.10፥1-48)
      ቆርኔሌዎስ ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር “እግዚአብሔርን የሚያመልክና የሚፈራ ሰው” ነበር፡፡ እግዚአብሔርን የመፍራቱና የማክበሩ መገለጫ እግዚአብሔርን ያከብራል(ሐዋ.10፥22)፣ ለህዝቡ እርዳታና ቸርነትን ያደርጋል፤ የጸሎት ህይወትም ነበረው፡፡(ሐዋ.10፥2) ነገር ግን ሙሉ ለሙሉ የአይሁድን ሥርዐት በመከተል አልተገረዘም፣ ምስክሮች ባሉበት የውኃ ጥምቀት አልተጠመቀም፤ በመቅደስም መሥዋዕት አላቀረበም፡፡ ይህ ደግሞ አህዛብ ወደይሁዲ እምነት እንዳይመጡ ከልካይ ከነበሩት ሥርዐት ዋና ዋናዎቹ ምክንያቶች ነበሩ፡፡
    ከአህዛብ ወደአይሁድ እምነት ሙሉ ለሙሉ የገባና ሥርዐታቸውን ሳያጓድል የሚፈጽም ባይሆንም፤ ቆርኔሌዎስ በአንድ አምላክ አምኖ የአይሁድን ሃይማኖትና ምግባር የሚከተል ሰው ነበር፡፡ ለምሳሌ፦ እንደአይሁድ ሥርዐት ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ይጸልይ ነበር፡፡(ሐዋ.3፥1) በዛሬ ዘመን ያሉት አብያተ ክርስቲያናት እንዲህ ያሉ አማኞችን ተቀብለው፤ የጸጋውንና የመዳኑን ወንጌል ከመስበክ ይልቅ የራሳቸውን ሥርዓትና መመሪያ በማሸከም አማኞችን ማጉበጣቸው ያሳዝናል፡፡ ሌሎቹ ደግሞ እንደመናፍቅና ቀኖና ጣሽ ቆጥረው ማውገዝ እንጂ ማቅረብ አይሆንላቸውም፡፡

Tuesday 22 July 2014

የመቶ አለቆቹ (ክፍል አንድ)




     እግዚአብሔር ሥልጣንን ለሰው ሁሉ የሚሰጥ አምላክ ነው፡፡ ምክንያቱም “ከእግዚአብሔር ካልተገኘ በቀር ሥልጣን የለምና፤ ያሉትም ባለ ሥልጣኖች በእግዚአብሔር የተሾሙ ናቸው።”(ሮሜ.13፥1) የሥልጣን መገኛው እግዚአብሔር ከሆነ ሥልጣንን የጨበጡ ወገኖች ቀዳሚ ተግባራቸው ደግሞ ህዝብ መምራታቸው ሳይሆን እግዚአብሔርን መፍራት ነው፡፡ “እግዚአብሔርን መፍራታቸው ክፋትን ፤ ትዕቢትንና እብሪትን፤ ክፉንም መንገድ፤ ጠማማውንም አፍ እንዲጠሉ ይረዳቸዋል።(ምሳ.8፥13)
  በመጽሐፍ ቅዱስ ከተጠቀሱት የሥልጣን እርከኖች መካከል መቶ አለቅነት አንዱ ነው፡፡ የመቶ አለቃ በሥሩ መቶ ወታደሮችን የሚያዝዝ የሮማዊ ጦር መኰንን የማዕረግ ሥልጣን ነው፡፡ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የተጠቀሱት ሮማውያን የመቶ አለቆች ደግሞ፤ አህዛባውያን ሆነው ካመኑት የተሻለ ህይወትና እምነት ይዘው ተገኝተዋል፡፡ ጌታ ቢረዳን እነዚህን የመቶ አለቆች አንድ በአንድ እናያለን፡፡

1.    የቅፍርናሆሙ የመቶ አለቃ (ሉቃ.7፥1-11)
   

Friday 18 July 2014

በልባቸው ወደግብጽ ተመለሱ(ሐዋ.7÷39) (የመጨረሻ ክፍል )

የእግዚአብሔር ሀሳብ - የእግዚአብሔር እስራኤል

    
 በአንዱ እስራኤል መካከል ክርስቶስን በማመንና ባለማመን ምክንያት ልዩነት ሆኗል፡፡ በሥጋ የአንድ ዘር ወገን ነኝ ማለት የእግዚአብሔር ወገን ስለመሆን ዋስትና አይደለም፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ምንም እንኳ በመገረዝና እስራኤላዊ በመሆን ብቻ የእግዚአብሔር ወገን እንደሆኑ በቀደመው ኪዳን ቢታወቅም፤ አሁን ግን ይህ የለም፡፡ በግልጥ ቃሉ “ከእስራኤል የሚወለዱ ሁሉ እስራኤል አይደሉም” ብሏል፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሔር እስራኤል ከአይሁድ ብቻ ሳይሆን ከማንኛውም ህዝብ በክርስቶስ በማመን አዲስ ፍጥረት በመሆን የእግዚአብሔር እስራኤል ይሆናሉና፡፡

Monday 14 July 2014

“በልባቸው ወደግብጽ ተመለሱ”(ሐዋ.7÷39) (ክፍል - 2)


v ሙሴ ከእግዚአብሔር “እርሱን ስሙት” የተባለለት ሰው ነበር፡፡ ምክንያቱም “ይሰጠን ዘንድ ህይወት ያላቸውን ቃላት የተቀበለ” ነውና፡፡(ሐዋ.7፥37-38) ነገር ግን “አባቶች” የነበሩቱ ሊታዘዙት አልወደዱም፤ ይልቁንም ገፉት እንጂ፡፡ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያንም ፤ታናናሽና ታላላቅ አይሁድም ነቢያት የመሰከሩለትና አብ በድንቅ በተገለጠው የደብረ ታቦር መገለጡ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት…”(ማቴ.17፥5) ብሎ የተናገረና በሥጋ የወለደችው እናቱ ድንግል ማርያምም “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ” በማለት የተናገረችለት ናት፡፡ነገር ግን ሙሴን ባለመታዘዝ እንደገፉት ሁሉ፤ ልጆች የተባሉቱም ክርስቶስ ኢየሱስን ብዙ ጊዜ ጠሉት፤ገፉት፤ሊገድሉትም ይፈልጉት ነበር፡፡(ዮሐ.5፥16)
    የእስራኤል ልጆች በዚያን ጊዜ በምድር ካሉት ሁሉ እጅግ ትሁት የነበረውን(ዘኁ.12፥3) ሙሴን  ባለመስማታቸው ካገኛቸውና ሙሴንም ካስቆጣው አንዱ ኃጢአት ክፉ ምኞት ነው፡፡(ዘኁ.11፥4፤10)፡፡ ክፉ ምኞታቸው ለገዛ መቃብራቸውና ለሞት አሳልፎ ሰጣቸው፡፡(ዘኁ.11፥34)፡፡ ጲላጦስ፦ አይሁድና “…የካህናት አለቆች በቅንዓት አሳልፈው እንደሰጡት ያውቅ ነበር”(ማር.15፥6) ማወቅ ብቻ አይደለም ፤ “ኢየሱስን ግን ለፈቃዳቸው አሳልፎ የሰጠው”(ሉቃ.23፥25) መሪው ጲላጦስ ከአይሁድ ጋር የተባበረበት አንዱ መንገድ ክፉ መሻታቸውንና ሃሳባቸውን እያወቀ፤ ህግ ተላልፎ ለክፉ ምኞታቸው አሳልፎ መስጠቱ ነው፡፡ ይህ ድርጊት አይሁድን “ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን” እስኪሉ ዕውር አድርጓቸዋል፡፡(ማቴ.27፥25)

Wednesday 9 July 2014

ተበልጧል በሁሉ

Please Read in PDF

ትዳር ያቀለጠህ፣ ሥልጣን ያባለገህ፤
ሀብት ያሞላቀቀህ፣ ዝና ያሰከረህ፤
ዕውቀት ጨርቅ ያስጣለህ፤
ለዚህ አለም ነገር፣ የምትንቆራጠጥ፤
በሌላውስ ይቅር፣ በክርስቶስ ጌታ፣ በዚህ አትበለጥ፡፡

Friday 4 July 2014

“በልባቸው ወደግብጽ ተመለሱ”(ሐዋ.7÷39) (ክፍል - 1)

Please read in PDF
     
     የጌታ ኢየሱስ መንግስት እየሰፋች፤ ብዙዎችንም እየወረሰች የመጣችውን የመጀመርያቱን የኢየሩሳሌምን ቤተ ክርስቲያን ጉዞ ለማስቀጠል “በመልካም የተመሰከረላቸውን መንፈስ ቅዱስና ጥበብም የሞላባቸውን ሰባት ሰዎችን ሐዋርያት መርጠው ለማዕድ አገልግሎት ሾሟቸው፡፡”(ሐዋ.6፥6) ከእነዚህ ከሰባቱ ታላቁ ዲያቆን እስጢፋኖስ “ ጸጋንና ኃይልን ተሞልቶ በሕዝቡ መካከል ድንቅንና ታላቅ ምልክትን ያደርግ ነበር።”(ሐዋ.6፥8)፡፡ ይህ ብርቱ የእግዚአብሔር ሰው ሰማዕት ሆኖ፤ ሞቱ ብዙዎችን ለጥቅም ከመበተኑ በፊት  የቀደሙትን የእስራኤልን ዘሥጋ ህይወትና አሁን የኪዳኑን ፍጻሜ እያዩ ያላመኑትን ፈሪሳውያንና የመቅደሱን ታላላቅ ካህናት እያነጻጸረ ሳይሸነግልና ሳይፈራ በብርቱ ቃል ወቀሳቸዋል፡፡

የግብጽ እስራኤል

     እስራኤል ልጆቹ ወደግብጽ ሲወርዱና በኋላ ላይ እርሱም አብሮ በረሃብ ምክንያት ሲሰደድ የመረረ ልቅሶ፣የልጁ የዮሴፍን ውለታ የሚረሳ አዲስ ንጉስና ህዝብ … እንደሚነሳ ያስተዋለ አይመስልም፡፡ እነርሱም ጥቂት በጥቂት ልባቸው በዚያ እየቀለጠ፣ የተገባላቸውን ኪዳንና ተስፋ ረስተው፣ ፈጽሞ ልባቸው በጣዖት አምልኮ ሊያዙ እንደሚችሉ ለቅጽበት እንኳ አላስተዋሉትም፡፡ ሰባ የእስራኤል ነፍስ ወደግብጽ ሲወርዱ (ሐዋ.7፥14)ሁለት ሚሊየን ገደማ ይሆኑም እንደሆነ ማን ለአፍታ እንኳ አሰላሰለ? አዎ! እስራኤል ወደግብጽ ሲወርዱ ሆዳቸውን እንጂ ጌታ እግዚአብሔር ለእነርሱ ያሰባትን ሃሳብ ፈጽመው ያስተዋሉም አልነበሩም፡፡
      ግብጽ ለእስራኤል ዘሥጋ የባርነት ቀንበር በመጫን ለእስራኤል ዘነፍስ ደግሞ መዳን ምክንያትና ቤዛ ለሆነው ስደተኛ ህጻን አባቱ እስኪጠራው (ሆሴ.12፥2፤ማቴ.2፥15) ማረፊያ በመሆኗ በታላቁ መጽሐፍ ተቀምጣለች፡፡ የእስራኤል ልጆች ግብጽን ባሰቧት ጊዜ በብዙ ቅንአት ይቃጠላሉ፡፡ ወንዶች ልጆቻቸውን ገና በማህጸን የገበሩባት፣ ጉልበቶቻቸው አለልክ የተበዘበዘባት ፣ ስድብን የጠገቡባት፣ ውለታቸውና ብድራታቸው በባዶ የተጣፋባት፣ የድካማቸውን ወዝ ያጡባት ፣ ምግብ ለጌቶቻቸው እያበሰሉ የተራቡባት ፣አስገባሪዎቻቸው ወዛቸውን የመጠጡባት ፣በልቅሶ ሸለቆ እንባቸውን የታጠቡባት ፣በዋርካዎቿና በዛፎቿ ጥላ ሥር የተከዙባት ፣በኮረብታዎቿ ሁሉ ላይ ምሬታቸውን ያሰሙባት ፣ራሔል እንባዋን ወደራማ የረጨችባት፣ እንግዶች አማልክት ነፍስና መንፈሷን ያስጨነቁባት ፣ እየዳኸች በባርነት ምጥ የተንፏቀቀችባት … የምድር ተስፋዋ ሁሉ ተሟጦ ክንድ ከኤሎሒም የተላከላትን ያቺን የግብጽ ምድር ኑሮ፣ ፊትና መልክ እንኳንስ እርሷ እስራኤል እኛም መቼም አንዘነጋውም፡፡

Monday 30 June 2014

የጠፋው ልጅ ወንድሞች(ሉቃ.15፥28)


ከሌሎች ወንጌላት ይልቅ ጠፍቶ ስለመገኘት ሉቃስ ብዙ ምሳሌዎችን ይሰጠናል፡፡“ጠፍቶ የተገኘው” ህጻኑ ኢየሱስ(ሉቃ.2፥46)፣ ጠፍቶ የተገኘው በግና ድሪም (ሉቃ.15፥3-11) ሉቃስ የዘገባቸው እውነትና ምሳሌዎች ናቸው፡፡በእርግጥ በኃጢአት ጠፍቶ ለበጎነት እንደመገኘት ያለ ፍጹም ሰማያዊ ደስታ የለም፡፡(ሉቃ.15፥10)
     የጠፋው ልጅ የአባቱን ሀብት ለመካፈል ሲነሳ ወደአባቱ ቤት ለመመለስ ፈጽሞ ያሰበ አይመስልም፡፡ከአባቱ ቁጥጥር ውጪ በመሆን ያሻውንና የወደደውን ሊያደርግ በመፈለግ ወጥቶ የሄደ ነው፡፡“ገንዘቡን ሁሉ ሰብስቦ የሄደው ወደሩቅ ሀገር ነው፡፡”(ሉቃ.15፥13) በሄደበት ሀገር ግን ሀብቱን በተነ፡፡ እንዳይመለስም እጅግ ርቆ ሄደ፡፡ የኃጥዕ መንገድ ከእግዚአብሔር የተለየ ነውና ሩቅ ነው፡፡ ከእግዚአብሔር የተለየው አዳም መልካም በሚመስለው መንገድ ሲጓዝ ፤በገነት እያለ ከእግዚአብሔር ሩቅ ነበር፡፡(ዘፍ.3፥6) በተመሳሳይ መንገድ ዮናስ ከእግዚአብሔር ፊት ወደተርሴስ የሄደው ዋጋ ከፍሎ፤ከስሮ ፤ርቆም ነው፡፡(ዮና.1፥3)
     የጠፋው ልጅ ከመራቁ ባሻገር በረሃብ ምክንያት የሚጨነቅም ሆነ፡፡ የረሃቡን ጭንቀት ለማስታገስ “ … ሄዶም ከዚያች አገር ሰዎች ከአንዱ ጋር ተዳበለ፥ እርሱም እሪያ ሊያሰማራ ወደ ሜዳ ሰደደው።እሪያዎችም ከሚበሉት አሰር ሊጠግብ ይመኝ ነበር፥ የሚሰጠውም አልነበረም።”(ሉቃ.15፥15) ይላል፡፡ የጠፋው ልጅ የእሪያ እረኛ በመሆን ያደረገው ይህ ድርጊት በአይሁድ ልማድና  በኦሪት ህግ እጅግ ርኩሰት ነው፡፡(ዘሌ.11፥7) ይህ ብቻ አይደለም ለእንሰሳት የሚሰጠውን የእህል ገለባ (አሰር) ሊበላ እየተመኘ እንኳ ሊያገኝ ያልቻለ ነበር፡፡

Thursday 26 June 2014

ሰቀሉህ ብዬማ እኔስ አላነባ!

Please read in PDF:- sekeluh byema enes alaneba!

ስለአይሁድ ጅራፍ፤ ችንካርና እንግልት፣
ስለ አክሊለ እሾሁ ሚስማርና ቁስለት፣
ጎንህ በጦር  ስለት ስለመወጋቱ፣
በጠቆረ ህሊና በዘንግ መቀጥቀጡ፣
ለሞት ለመቃብር ይህ አላበቃህም፣
ባለብዙ ምህረት ኢየሱስ መድህን፡፡

     የግፍ ግፋታቸው በጥላቻ ገፍቶህ፣
     የአመጻ ፍትህ አሽቀንጥሮ ደፍቶህ፣
     በማይራራ መዳፍ ከግንድ እያማቱ ፣
     በደል ሳያገኙ ባ’ድማ እየተንጫጩ፣
     አቁመው ዕርቃንህን የኋሊት ጠፍረው፣
     ስላሉህ አይደለም ስቀለው! ስቀለው!
     የ’ኔን ሞት ጌታዬ አንተ ለ’ኔ የሞትከው፡፡

Friday 20 June 2014

“ሁላችሁ ወንድማማች ናችሁ”(ማቴ.23፥8) – (የመጨረሻ ክፍል)


            
    
            
   ፈሪሳውያን  ወንድማዊ መሪነትን ወደ አስፈሪ አለቃነት ለውጠውታል፡፡እኛንም እንደወንድም አለመተያየትና አለመዋደዳችን የጎዳን ብቻ አይደለም፤ ብዙዎችን ያሰናከልንበትም ከባድ ኃጢአት ነው፡፡ጥቂት የማይባሉ በአሜሪካ፣በአውሮፓ፣በካናዳና በሌሎችም የስደት ምድር ላይ ያሉት “አማኝ ተብለው” በጽዋና በጉባኤያት የሚሰባሰቡት በብሔር ተኮር ስብስብ፤ ያውም ከኦሮሞ ወለጋና አርሲ፣ከአማራ ጎንደርና ጎጃም፤ከደቡብ ወላይታና ሲዳማ … በሚል ተከፋፍለው “በቤተ ክርስቲያን” ሲሰበሰቡ ማየት የሚያመውን ያህል ምንም ህመም፤ከባድ ስቃይም የለም፡፡ እዚህ አይናችን ሥርም ያለው የሀገር ቤቱ የሚብስ እንጂ የሚሻል ነገር የለውም፡፡በብዛት የአንድ ሀገረ ስብከትን ሥራ አስኪያጅ ወይም ጳጳስ ዘርና ወንዝ ቆጥረው የሚሰባሰቡትን የቄስና የዲያቆን መንጋ ማየት እንግዳ አይደለም፡፡ሥር የሰደደው የዘረኝነታችን ዘር የእግዚአብሔር ነፍስ አብዝታ የምትጠየፈውን በወንድማማች መካከል ጠብ መዝራትን እንኳ ረስተነዋል፡፡(ምሳ.6፥19)
    አገልጋይ ግን እንዲህ ያለውን ነገር ሊያጠራ፤ እንደወንድም በቅርብ ሊመራ እንጂ አለቃ ሆኖ ሊያዝ አልተጠራም፡፡ ስለዚህ ፈሪሳውያን አለልክ ክብርን ሽተዋልና ፍፁም ወቀሳቸው፡፡ አለመታደል ሆኖ እንጂ አለቅነት ከወንድምነት አይበልጥም፡፡ ወደሌላ ከምትተላለፍ ህልቅናና ሹመት ይልቅ ለዘለዓለም አብሮን  የሚኖረው ወንድምነት ትልቅ ክብር አለው፡፡
    ወንድም ገመና ሸፋኝ ነው፤ ወንድም የገዛ ወንድሙን ገመና ለማይራራ ባዕድ አሳልፎ አይሰጥም፡፡ወንድማማችነት በደም ተሳስሯልና እስከመከዳዳት በሚያደርስ ክፋት አይያዝም፡፡ አዕምሮው ካልጎደለው በቀር ወንድም ወንድሙን “ወንድሜ አይደለህም” ብሎ ለመካድ አቅም አይኖረውም፡፡ወንድምነትን የሚክድ እርሱ ነው እንጂ ከዳተኛ ፤ወንድምነቱ ፈጽሞ የሚሻር አይደለም፡፡ ብዙ ጊዜ ወንድማችነትን ክደን ስንነካከስ፣ስንበላላ፣ስንጠፋፋ … ዓለም እንኳ ታዝባናለች፤  የስድብ ምክንያትም ሆነናል፡፡ መንፈሳዊነቱ ብቻ ሳይሆን የሀገራችንን ተጨባጭ የመሪዎችና የህዝቡን ቅርርቦሽ ስናይም እጅግ የመረረ ነው፤ዛሬም መሪ የሚባሉቱ በወንድምነት መንፈስ ህዝብን ማገልገል የሚቀፋቸውን ያህል ሌላ ነገር የሚቀፋቸው ያለ አይመስለኝም፡፡
     ለምን እንደሆን ለራሴ ግራ ይገባኛል፡፡ ብዙ ጊዜ ከሚያገለግሉኝ ወንድሞቼ መካከል ብዙዎቹ ትህትና የሚጎድላቸው ብቻ አይደሉም፤ እንደወንድም የማያቀርቡም ናቸው፡፡ የሚያሳዝነው ግን ሲነገራቸው እንኳ ለመስማት ዝግጁ አለመሆናቸው ነው፡፡ … ግን ከሁሉ በላይ በአማኑኤል የተዛመድን ወንድማማቾች ከደም ይልቅ በህያውና ለዘላለም በሚኖር፤ ከማይጠፋው ዘር በመወለድ አንድ የሆንን ነን፡፡እንኪያስ ከሥጋ ወንድምነት በሚልቅ የወንድማማች ፍቅር ልንዋደድ፣ልንከባበር፣ገመና ልንሸፋፈን፣ ሳንሸነጋገል በምክር ቃል በግልጥ ልንነጋገር፣ልንተያይ … በእውነት ይገባናል፡፡

Monday 16 June 2014

“ሁላችሁ ወንድማማች ናችሁ”(ማቴ.23፥8)(ክፍል አንድ)

    Please read in PDF :- hulachihu wendmamach nachihu 1

 “ወንድም” የሚለው ቃል በቀጥታ ትርጉም ከአንድ እናትና አባት የተወለዱ ተወላጆችን የሚያመለክት ሲሆን በታላቁ መጽሐፍ ግን ከተወላጅ ባሻገር ለሌሎች ወገኖችም በተለያየ ጊዜ ተሰጥቶ ሥራ ላይ ሲውል እናገኛለን፡፡  ጥቂቱን ብንመለከት፦
ሀ. በሀገር ተወላጅነት
    የአንድ ሐገር ተወላጆች ብቻ በመሆን ወንድም መባባል እንደሚቻል መፅሐፍ ቅዱስ ሙሴንና  የእስራኤልን ልጆች በመጥቀስ እንዲህ ይላል፦ “በዚያም ወራት እንዲህ ሆነ፤ ሙሴ ጎበዝ በሆነ ጊዜ ወደወንድሞቹ ወጣ፤ የሥራቸውንም መከራ ተመለከተ፥ የግብፅም  ሰው የወንድሞቹን የዕብራውያንን ሰው ሲመታ አየ” (ዘፀ.2፥11 ፤ ሐዋ.7፥23-26)፡፡ በእርግጥም ሙሴ ለሀገሩ ለእስራኤል ልጆች ሁሉ ፍፁም ታላቅ ወንድም(ወንድም ጋሼ) ነበር፡፡
ለ.  ከጥብቅ ወዳጅነት የተነሣ
     ግብረ ሰዶማውያን በክፉ የተሰጡለትን የኃጢአት እሾህ መፅሐፍ ቅዱሳዊ ለማስመሰል እጅ ጠምዝዘው ከሚተረጉሙት ታሪክ አንዱ የዳዊትንና የዮናታንን የጠበቀ ወንድማዊ ፍቅርን በመጥቀስ ነው፡፡ ዳዊትና ዮናታን ወዳጅነታቸው እንደወንድም የነበረ መሆኑን ፥ዳዊት ዮናታን በተገደለ ጊዜ በእንባ ቃል በአንደበቱ እንዲህ አለ፦ “ወንድሜ ዮናታን ሆይ፤ እኔ ስለአንተ እጨነቃለሁ፤ በእኔ ዘንድ ውድህ እጅግ የተለየ  ነበር፤ ከሴት ፍቅር ይልቅ ፍቅርህ ለእኔ ግሩም ነበር ፡፡ (2ሳሙ.1፥26-27 )

Wednesday 11 June 2014

የኢየሱስ ዝቅታ …

Please read in PDF :- yeEyesus zikta

ሐማዊ ከፍታ …
ሰማይ ሰማይ ሰማይ - አርጤክስስ ዙፋን ሥር፤
ከዚያ ዝቅ ሲሉ - ሌላ ሥፍራ የለም - ከመቃብር በቀር፡፡
     የኢየሱስ ዝቅታ …

Friday 6 June 2014

መንፈስ ቅዱስ ግን ለምን ነው የተረሳው?

   Please read in PDF:- Menfes kidus gn lemn teresa? 
 የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ በጻድቃን በሰማዕታት፣በመላዕክት፣ በሥላሴ፣ በኢየሱስ፣ በአብ … ሥም “በመታሰቢያነት” የተሰሩ የገጠር አጥቢያ፣ አድባራት፣ ገዳማትና ካቴደራሎች አሏት፡፡ ከእነዚህ እልፍ ሺህ “አብያተ ክርስቲያናት” መካከል የመንፈስ ቅዱስን “መታሰቢያ ህንጻ” ማግኘት በምድረ በዳ መልካም ጥላ የመፈለግ ያህል እጅግ ይከብዳል፡፡ለምን ይሆን? … (በእርግጥ የመንፈስ ቅዱስ አማናዊ ማደርያ ቅዱሱ በጌታ ቤዛነት ያመነ አማኝ ሰውነት ቢሆንም! (1ቆሮ.3፥16፤ሮሜ.8፥9) የንጽጽሩም አላማ ስለመንፈስ ቅዱስ ያለንን ግንዛቤ አናሳነት ለመታዘብ እንጂ ድካምን ለማጉላት ከማሰብ አይደለም፡፡)

Monday 2 June 2014

እንዲሁ ይመጣል!

Please read in PDF :- Indihu yimetal!
ለምን ነው ‘ምታዩት እንዲህ አንጋጣቹ’፤
ወደሰማይ ፋና አይና‘ቹን ልካቹ’፤
በነፍስ ትካዜ በመንፈስ ታክታ’ቹ … ? ፤
ሳይረቅ እየራቀ ሲሄድ የምታዩት፤

Monday 26 May 2014

የትንሣኤው ምስክሮች

    የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን መካከል ሙስና መቃብርን አጥፍቶ መነሣት የክርስትና መሠረት የቆመበት ጽኑ ዐለት ነው፡፡ አሁን በክርስቶስ ኢየሱስ ደም በጸጋ ድነናል፤ ወደፊት ደግሞ ፍጹም እንድናለን፤ (ኤፌ.2፥8) ብለን ደፍረንና ጨክነን ጮኸን የምንናገረውና ቤተ ክርስቲያንም አሰምታ የምትሰብከው እርሱ ዝጉን መቃብር ሳይከፍት፤ የታተመው ድንጋይ ሕትመቱ ሳይፈታ፤ ሞትን ድል አድርጎ ከሙታን መካከል ስለተነሣ ነው፡፡
     የጌታ ትንሣኤ የስብከቶች ሁሉ ዋናውና የመጀመርያው፤ ትልቁም ርዕስ ነው፡፡ አንድ ሰባኪ የእግዚአብሔርን ቃል ሊናገር በወጣበት አውደ ምሕረት ላይ “ብዙ ቃል” ሰብኮ የጌታን ትንሳኤ ሳይናገር ቢወርድ፤ በእውነት! እውነተኛ ሰባኪ መሆኑ ያጠራጥራል፡፡ ምንም እንኳ ጥቂት እንከኖች ቢኖርባትም ያቺ በተራራ ላይ የተሠራችውና ታበራ የነበረችው የሐዋርያት ቤተ ክርስቲያን በአስቆሮቱ ይሁዳ ፈንታ ሌላ ሐዋርያ ሊመርጡ ባሉ ጊዜ ያስቀመጡት የመጀመርያው መስፈርት “ … ከእነዚህ አንዱ ከእኛ ጋር የትንሣኤው ምስክር ይሆን ዘንድ ይገባል”(ሐዋ.1፥22) የሚል ነው፡፡
    ደቀ መዛሙርቱ ያልተደራደሩበት እውነት “ከእኛ ጋር የትንሣኤው ምስክር” የሚሆን ብቻ እርሱ እውነተኛ የጌታ ሐዋርያ ነው ብለው ማመናቸው ነው፡፡ ጌታ ከሙታን መካከል መነሣቱን የሚያምኑና የሚያውቁ ብዙ ሰዎች በዚያን ጊዜ ነበሩ፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ጊዜ የተፈለገው፤ ጌታ “እንደ ቅድስና መንፈስ ግን ከሙታን መነሣት የተነሣ ”(ሮሜ.1፥4) መሆኑን ሳይፈራ ሳያፍር በአደባባይ የሚመሰክር ሐዋርያ ነው፡፡

Wednesday 21 May 2014

“Innoo ka’eera,asi hinjiru.” (Mat.16:6)

Please read in PDF

Goftaan IYesus Kirstos irra-daddarbaa fi cubbuu ilmaan namaa baadhachuudhaan fannoo irratti fannifameera. kanas barreesitootni wangeelaa sagalee tokkon mirkaneesaniru. (Mat.27:35,Mar.15:25,Luq.23:33,Yoh.19:18).duu’a fi dhiignii Goftaa IYesuus biyya lafa tanaafi ilmaan namaa hundaaf baayyee barbaachisaa dha. Sababn isaas dhiiga osoo hindhangalaasin dhiifamuun cubbuu waan hinjirref.(Ibr.9:22)
     Ilmaan namaa bittaa cubbuufi waanjoo seexanaa jalaa gaarummaa fi hojii isaaniitiin bilisa ba’u hindandeenye. qajeelummaatti fi hojiin gaariin keenya sababii cubbuu irra kan ka’een akka huccuu abaarsaatti ta’e (Isa.64:6) nuti  hundinuu karaa Waaqayyoorraa gorree ture. (Rom.3:12) kanaaf cubbuu nama tokko irraa kan ka’een gara biyya lafaa hundatti duuti dhufee. akkasumaas namootni waan yakkaniif du’i sanyii namaa hundaa walga’era.(Rom.5:12)
   Biyyii lafaa hundii abdii dhabee, du’a fi dukkanaan marfamee, seexanni bittaasaa yeroo babbal’ifatee jirutti, namni aarsaa hoolaa fi jibbichaa dhiyeesuus  gatii lubbuusaa wajjin waan walhinmadaaleef … baraarsa cubbuu fi nageenya sammuu waan argachuu hindandeenyeef Waaqayyoon ilmowwasaa hunda akkanumatti  waan nu jaalateef nu kenneera.(Yoh.3:16)

Monday 19 May 2014

አንደኛው መስቀል

Please Read in PDF
በህይወት የማይስማሙ በሞት ይጣመራሉ፡፡በክርስቶስ የሚካካዱ ለሰይጣን ሊገዙ በአንድ ያብራሉ፡፡በምድረ በዳ ሰው ለመግደል ፣የሰው ንብረት ለመዝረፍ የሚስማሙ ቀራንዮ ላይ መለያየት ይጀምራሉ፡፡በወንበዴነት ሚስማሙ የክርስቶስ በመባል ግን ይለያያሉ፡፡በኃጢአት የሚጣበቁ በጽድቅ ይነጣጠላሉ፡፡አይለያዩም የተባሉ የኃጢአት ባልንጀሮች ክርስቶስን በማመንና ባለማመን  እስከማይተዋወቁ ድረስ ይከፋፋሉ፡፡
       ቀራንዮ ድካማችን አይጸድቅባትም፡፡ድካማችንን በመስቀሉ ጠርቀን፤ ክፉ ምኞት አንቂ አሮጌውን ሰው ሰቅለን አዲሱን ሰው የምንለብስባት፤ ለአንዱ ጌታ መገዛታችንን በግልጥ ውሳኔያችንን የምንገልጥባት ስፍራ ናት፡፡ቀራንዮ ላይ ብዙ አማራጮች ብዙ መንገዶች የሉም፡፡ብዙ የመዳን ቀመሮች ፣ከሁለት የዘለሉ የድህነት ስሌቶችም የሉም፡፡ቀራንዮ ላይ ሁለት መንገዶች ብቻ አሉ፡፡አንዱ የሲዖል አንዱ ወደእግዚአብሔር ገነት፡፡ሦስተኛ ምርጫ የለም፡፡ብንፈልግም ፈጽሞ ማግኘት አይሆንልንም፡፡
        አንደኛው መስቀል ላይ ዘመኑን በውንብድና የጨረሰ፣ለክፋቱ ዳርቻ ሳያበጅ ከነክፋቱ የተገኘ ለጥፋቱም ተካካይ ፍርድ በህጉ የተሰጠው አንድ ደካማ ሰው አለ፡፡አለም ሞት ብትፈርድበትም ክርስቶስ ግን ዛሬም የርህራሔ እጁን ዘርግቶ እስከማታ "ልጄ ሆይ አትሙትብኝ እኔ ልሙትልህ!!!" እያለ ይለምነዋል፡፡ ከእግዚአብሔር መዝገብ ፍርድ እስካልወጣ አለም ሞት ፈርዳ ለፍርዱ መፈጸም ብትቻኮልም የህይወት ጥላችንን ማንም አያጥፈውም፡፡አለም ሞት ብትደግስም ክርስቶስ ግን የማይደክም የማዳን እጅ ዘርግቶለታል፡፡