Wednesday 24 May 2017

አርጓል በክብር

መቃብሩን በድንጋይ በማኅተም ቢያትሙ
አልተነሣም ብለው በገንዘብ ቢስማሙ

Tuesday 23 May 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል ዘጠኝ)

Please read in PDF
3.     ከራን ተቀባይ ነው“እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ በጎ ወታደር ሆነህ፥ አብረኸኝ መከራ ተቀበል” (2ጢሞ.2፥3)፡፡ የእውነተኛ አማኝም ሆነ አገልጋይ ዋና መገለጫው፣ ከጠላት ዘንድ የሚመጣበት ብርቱ ሰልፍና ዋና ተቃውሞ ነው፡፡ ክርስቲያንን ከዓለም ጋር የሚያስማማው ምንም የሕይወት ዘይቤ ወይም ሥርዓት የለውም፡፡ ጌታ ራሱም፣ “በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” (ዮሐ.16፥32) በማለት መከራው የማይቀርና ነገር ግን አሸናፊው ቀድሞ መከራውን ስላሸነፈው ፍርሃት እንደማይገባ አስረግጦ ነግሮናል፡፡ ዓለም ስለእኛ የምትመሰክረው “በጎ ነገር” ካላት፣ ክርስትናችንን ቆም ብለን መፈተሽ ይገባናል፡፡
    ቅዱስ ጢሞቴዎስ በኋለኛው ዘመኑ በመከራው ጽናትና እየሆነ ባለው ነገር ፈጽሞ በፍርሃት ተውጦ ነበር፡፡ ስለዚህም ከመከራው ጽናት የተነሣ መንፈሳዊ ድፍረትን አጥቶ ነበር፤ (2ጢሞ.1፥7)፡፡  በመፍራትም ወደኋላ እንዳይል አበክሮ ቅዱስ ጳውሎስ ያበረታታዋል፡፡ እምነታችንም፤ አገልግሎታችንም በክርስቶስ ጸጋ ላይ የተመሠረተ ነው፤ ደግሞም ይህን ብርቱ ሥራ መከራ በመቀበል ልናምነውና ልናገለግለው ይገባናል፡፡ ውጊያችንም ሁሉ ታላቅ ወታደራዊ ጽናትን በሚጠይቅ ማንነት ውስጥ ማለፍ ይገባናል፡፡

Friday 19 May 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 3)

Please read in PDF

ዘፈን ራሱ ኮሞስ ነው!

    ዘፈን የሚለውን ሃሳብ አስቀድመን ስንተረጉም፣
1.      በጥንት ግሪክ ለወይን አምላክ በሚደረግ ታላቅ ግብር ላይ ተሰልፎ መዞር፣ መፈንደቅ፣ መጨፈር፣ መጯጯኽ፣ መፈንጠዝ፣ ኢ ሥነ ምግባራዊና ገደብ የለሽ በኾነ የአልኮል መጠጥና ገደብ የለሽ በኾነ የአልኮል መጠጥና በምግባረ ብልሹነት እርካታ ለማግኘት የሚደረግ ወሲባዊ ጭፈራ( ... Drinking parties involving unrestrained indulgence in alcoholic beverages and accompanying immoral behaviour, - ‘orgy, revelling, carousing.)
2.     በአማልክት (በጣዖታት) ፊት በቡድንና በግል ሚደረግ ፈንጠዝያ፣ ዝሙትና መጠጥ ባካተተ መልኩ የሚደረግ ጭፈራ፣
3.     በቡድን በተደራጀ መልኩ በተለያየ ሁኔታ የሚደረግን አደባባያዊ ትርኢት መልክ ያለው የመንደር ክብር በዓል፣ ጭፈራ፣ ዘፈን፣ ግጥም፣ ዜማ፣ መሽከርከርን ... የሚያመለክት ትርጉም ያለው ነው፡፡”
ብለን በክፍል አንድ ላይ ማቅረባችንን መርሳት የለብንም፡፡
     እናም፣ ዘፈንን ኃጢአት ነው የምንለው “ዘፈን” የተባለውን “አንድ ቃል” አንጠልጥለን፤ እርሱኑ ደግሞ ለጥጠን አይደለም፡፡ ቀድሞ እንደተናገርነው የምንተረጉመውን ሁሉ የምንተረጉመው ለእግዚአብሔር ክብርና ለእኛ ጥቅም ነው፡፡ ከላይ በተለያየ ይዘት በትርጉም ከተጠቀሱት ውስጥ፣ ዝርዝር ሃሳብ እናውጣ ብንል፤ ዘፈን ማለት፦
1.     መንፈሳዊ አምልኮ ጋር መዛመድ የማይችል ርኩስ ጠባይን አመልካች ነው፡፡ በተለይም በጣዖታት ፊት የሚደረግ ማናቸውም የደስታ መግለጫ ሥርዓትን ማከናወን፣ “ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ” (ዘጸ.20፥3) የሚለውን ሕግ ለማስቃረን አሳላጭ መንገድ ስለሆነ፣ ዘፈን አደገኛነቱ ምንም አያጠያይቅም፡፡

Monday 15 May 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 2)

Please read in PDF
በመጽሐፍ ቅዱስ “ዘፈን” የተገለጠበት አገላለጥ
   በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ፣ በተለይም በአማርኛው በተመሳሳይ ቃል ወይም ሐረግ ተጠቅሶ የተለያየ ፍቺ ያለው ቃል ብዙ ቦታ ይገኛል፡፡[1] ስለዚህ ቅዱሳት መጻሕፍትን ስናጠና የቃሉን መመሳሰል ሳይሆን ቃሉ ያለበትን ወይም የተነገረበትን ዓውድ በትክክል ማጥናትና መስተዋል ይገባናል፡፡ “ዘፈን”ም ለተለያየ ሃሳብ፤ በተለያየ ዓውድ ተነግሯል፡፡ እናም እንደየተነገረበት ዓውዱ የተለያየ ትርጉሞችና ሰፊ ሃሳቦችን ይዟል ማለት ነው፡፡ ጥቂቱን ብንመለከት እንኳ፦
1.    “ዘፈን” በቅዱስ አምልኮ ውስጥ ሲጠቀስ፤
    በብሉይ ኪዳን የእስራኤል ልጆች በዘፈን ለእግዚአብሔር መንፈሳዊ አምልኮን ያቀርቡ ነበር፡፡ የእስራኤል ልጆች ከግብጽ ምድር፤ ከባርነት ቤት ሲወጡ፣ ፈርዖንንና ሠረገላውን ሁሉ በባሕር አስጥሞ፣ ለእነርሱ ግን ሞገስንና ግርማን ሰጥቶ፣ የኤርትራን ባሕር በድል ሲሻገሩ በዝማሬ አመሰገኑ፤ (ዘጸ.15፥1)፡፡ በሌላ ሥፍራ፣ “ዳዊትም በሙሉ ኃይሉ በእግዚአብሔር ፊት ይዘፍን ነበር፤ ዳዊትም የበፍታ ኤፉድ ለብሶ ነበር፤ … የእግዚአብሔርም ታቦት ወደ ዳዊት ከተማ በገባ ጊዜ የሳኦል ልጅ ሜልኮል በመስኮት ሆና ተመለከተች፥ ንጉሡም ዳዊት በእግዚአብሔር ፊት ሲዘልልና ሲዘፍን አየች፤ በልብዋም ናቀችው፡፡ … በእግዚአብሔር ፊት ዘፍኛለሁ፤ በእግዚአብሔር ሕዝብ በእስራኤል ላይ አለቃ እሆን ዘንድ ከአባትሽና ከቤቱ ሁሉ ይልቅ የመረጠኝ እግዚአብሔር የተባረከ ይሁን ስለዚህም በእግዚአብሔር ፊት እጫወታለሁ፤” (2ሳሙ.6፥14-16 ፤ 21) በማለት ራሱም ገልጦታል፡፡

Wednesday 3 May 2017

ዘፈን - የወደቀው መልአክ እንጉርጉሮ (ክፍል 1)

Please read in PDF
ሰርጸ ፍሬ ስብሐት[1] ሆይ! ቃሉን ለራስህ ሃሳብ አትጠምዝዘው!
መግቢያ
    በአንድ ሰሞን “ኦርቶክሳዊ ተብሎ ባለመጠራቱና የሌላ ቤተ እምነት ተከታይ ሆኗል ተብሎ መጠርጠሩ ያናደደውን ዘፋኝ” ተመልክቼ፣ “ዘፋኝ ለኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ምኗ ነው?” ብዬ ሃሳቤን ማፍሰሴ የሚዘነጋችሁ አይደለም፤ በዚያን ሰሞንና ከዚያም በኋላ ዘፋኙን “በመገሰጼ” የበዙ ተቃውሞዎች ገጥመውኝ ነበር፤ ተቃውሞዎቹ ሁለት መልክ አላቸው፤ አንዳንዶች የሌላውን[የዘፋኝን] ኃጢአት የምታወራው አንተ ማን ነህ? የሚሉ ሲሆኑ፣ ሌሎች ደግሞ ዘፈን ያልተከለከለ መሆኑን፣ ሥራ(ሙያ) መሆኑን፣ “እግዚአብሔር የሚባርከው” መሆኑን፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ራሱ የተጠቀሰ መሆኑንና ዳዊት መዝፈኑን፣ “እግዚአብሔርን በዘፈን አመስግኑት” መባሉን፣ ብሎም መኃልይ መኃልይ ዘሰሎሞን ስለ“ተቃራኒ ጾታ” ግንኙነት ካወራ፣ እኛስ ምናለ እንዲያ ብናደርግ የሚል “ሙግት” መልክ ሊያቀርቡልኝ ብዙ ጥረዋል፡፡ በአብዛኛው ግን ስድብ መልክ ስለነበረው አያንጽም፣ ሰውንም አያስተምርም ያልኩትን ሁሉ ለራሴ ከማንበብ፣ ሰዎችም እንዳይመለከቱት በማድረግ ወደቅርጫት እንዲጣል አድርጌዋለሁ፡፡ በዚህም ምክንያት ስለዘፈን አስፍቼ ለመጻፍ ከብዙ ጊዜ በፊት አስብ፤ አሰላስል ነበር፡፡
     ለዚህ ጽሁፍ ሌላው መነሻ ምክንያት የሆነኝ፣ በጄ ቲቪ የቴሌቪዥን ጣቢያ ሰኞ በ16/8/09 እና 23/8/09[2] ምሽት አራት ሰዓት ገደማ በሚተላለፈው የ“ብራና” ፕሮግራም ላይ፣ ሰርጸ ፍሬ ስብሐት የተባለ ሰው ሙዚቃን(ዘፈንን) በተመለከተ አንድ “ጥናታዊ ጽሁፍ”፣ በአንድ ሌላ ቦታ ላይ አቅርቦ የነበረውን ሲያስተላልፍ ያሳያል፤ ለሰርጸ “ጥናታዊ ጽሁፍ” መነሾ ምክንያቱ ደግሞ፣ ዮናስ ጎርፌ የተባለ ሌላ ሰው ቤት ያጣው ቤተኛ- ሙዚቃ፣ ሙዚቀኛነትና ኢትዮጵያዊቷ ቤተ ክርስቲያን በሚል ዘፈንን[ሙዚቃን] ባስመለከተ በጻፈው መጽሐፍ ላይ የቀረበ ነው፡፡ ዮናስ ጎርፌ ለተባለው ሰው በወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ዓቃቤ እምነት ላይ የሚሠሩ ብዙዎች መልስን ስለሰጡት እርሱን ማንሳት አልፈልግም፡፡ ሰርጸ ግን፣ “ቤት ያጣ ቤተኛ” መጽሐፍን፣ “ከዚያኛው ቤት ሲሰደድ”[በእርግጥ ተሰዷል ብዬ ለማመን ብቸገርም] አዲስ ጎጆ ሊሠራለት ዳድቶ፣ ወደሚድያ እንዲመጣ የመፈለጉ አንድምታ፣ አደገኛነቱ የቱም መንፈሳዊና ለእግዚአብሔርና ለሕዝቡ ቅድስና የሚቀና አገልጋይ ይጠፋዋል ብዬ አላስብም፡፡