Sunday 21 August 2022

ስለ ኹለቱ መጻሕፍቴና አዲሱ መጽሐፌ ጥቂት ነገር!


ከአኹን ቀደም ኹለት መጻሕፍት በዕቅበተ እምነት ዙሪያ አሳትሜአለሁ፤ በአጭሩ፣ የመጀመሪያውን መጽሐፍ በአብዛኛው ያሰራጨኹት በማኅበራዊ ሚድያ ለምተዋወቃቸው ወንድምና እህቶች ነበር፤ ነገር ግን ከ2000 ኮፒ ውስጥ መጽሐፉን ለማሳተም ተበድሬ ለመክፈል፣ በዕዳ ካስያዝኩት 800 መጻሕፍት ውጭ፣ ካከፋፈልኩት ከ406 በላይ የሚጠጉት መጻሕፍት ቢሸጡም፣ የተሸጡበት ብር ግን ለእኔ አልደረሰኝም። ኹለተኛው መጽሐፌ ደግሞ ገና በስርጭት ላይ ነው። በጽሑፍ ዓለም አሳትሞ፣ መልሶ ማሰራጨት እጅግ ከባድና ፈታኝ ሥራ ነው።



በታማኝነት መጻሕፍቱን የምንልክላቸው ሰዎች ደግሞ፣ ከሸጡ በኋላ ብሩን ለመላክ ወገቤን ሲሉ፣ ከኅትመትና ስርጭት ጋር ተያይዞ፣ “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” ይኾናል። በዚያ ላይ ኹለቱም መጻሕፍት ከቅርብ ወዳጆቼና[በተለይም ዛሬ ላይ ምዩጣን ኾነው ያፈገፈጉት መጽሐፉ እንዳይሰራጭ በብርቱ መታገላቸውና] አኹንም “አብሬአቸው ከማገለግላቸው” ጭምር፣ ጠንካራ ተቃውሞ በማስተናገዴና፣ “አብዛኛው” የክርስትና መንደር ለእነዚህ “ኑፋ**ቄያት” የቅርብ ተጠቂ መኾኑ፣ ነገሩን ከኅትመትና ከስርጭቱ ተግዳሮት በላይ ያከፋዋል!

ትልቁ ደስታዬ ግን ሰዎች ከኑፋ**ቄ ሲድኑና ሲመለሱ ማየት ነው። በዚህ ረገድ አያሌ ምስክርነቶችን በመስማቴ እጅግ ደስ ይለኛል። ለማትረፍና ብዙ ገንዘብ ለማጋበስ አልጽፍም፤ ይልቁን ለእግዚአብሔር መንግሥት መስፋትና ሰዎች ከሐሳ**ውያን ይድኑ ዘንድ፣ ጥቂት ነገር ማበርከት ከቻልኩ በቂዬ ነው። እናም በተመሳሳይ መልኩ ሦስተኛ መጽሐፌን ለማሳተም ዝግጅቴን አጠናቅቄ በመንገድ ላይ ነኝ። ሦስተኛው መጽሐፌ በአፍሪካና በአገራችን ባህላዊ እምነቶች ዙሪያ የሚያጠነጥንና በተለይም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ክርስትናን እየተ**ጋፋ ስለ መጣው አገር በቀል ባህላዊ እምነቶችን የሚዳስስ መጽሐፍ ነው። ይህን አገልግሎት የኅትመት ክፍያ በመሸፈን፣ በመጋራት፣ በማሠራጨት ለመርዳት፣ ቀኝ እጁን ለሚሰጠኝ የሰላም ሰውና አማኝ እነሆ በሬ ክፍት ነው! በዚህ አድራሻም ልታገኙኝ ትችላላችሁ! (email; abentek2@gmail.com ጻፉልኝ ወይም 0911044555 ወይም 0928724849 በእጅ ስልኬ ደውሉልኝ) የጌታ ጸጋና ሰላም ከኹላችን ጋር ይኹን፤ አሜን።

“እርስ በእርሳችንም ለፍቅርና ለመልካም ሥራ እንዴት እንደምንነቃቃ እናስብ” (ዕብ. 10፥24)

No comments:

Post a Comment