Wednesday 30 December 2015

ሕይወት አልተስማማም!


ክፋትን በክፋት ፣ እያጠፉ መኖር
ርኩሰትን በርኩሰት ፣ እያጠፉ ማሴር

Thursday 24 December 2015

ክርስቲያን ያልሆኑት ኦርቶክሳውያን ወይስ ምህረተ አብ?! (ክፍል አንድ)




     ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር” (2ጢሞ.3፥16) የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸውን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትንም ሆነ የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን መንፈስ ቅዱስ ለእኛ የሰጠው፥ “ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ እናምን ዘንድ፥ አምነንም በስሙ ሕይወት ይሆንልን ዘንድ” ነው፡፡ (ዮሐ.20፥30-31)
      የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት አንድና አንድ ፤ ግልጽና ግልጽ እንጂ ስውርና ውስብስብ ፣ ለሰዎች እንዳይገባና እንዳይረዱት ተደርጎ የተጻፈ አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሰው ልጅን የማዳን ተስፋና ተስፋው በኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት ፤ መሞትና መነሳት የተፈጸመ መሆኑን በማስረዳት ይህን መዳን የምሥራች ብለን ለፍጥረት ሁሉ በድፍረት ከመንፈስ ቅዱስ ጉልበት የተነሳ እንድንናገር እንጂ ሌላ ስውር አጀንዳ የለውም፡፡ ጌታችን የመምጣቱን ምስጢር ራሱ ሲናገር፥ “እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ” (ዮሐ.10፥10) ሲል ፤ ደቀ መዛሙርቱም ፤ “ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው” (1ጢሞ.1፥15)  በማለት መሰከሩ፡፡ ለቤተ ክርስቲያንም የተሰጠው ትልቁ ተልእኮና አደራ “ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” የሚል አለም አቀፍ ጥሪና ሰፊ የመከር ሥራ ነው፡፡ (ማቴ.28፥19)

Friday 18 December 2015

ግጭትና ጦርነት የማያስተምራት አገር



ስለራሳችን እንዲህ እንናገራለን ፦
-      እንግዳ ተቀባይ ሕዝቦች ነን ፤
-      ብዙ ብሔር ብሔረሶችና ሕዝቦች ተዋደው የሚኖሩባት አገር አለን ፤
-      ለቁጥር የሚታክት “ክርስቲያን” ፣ እልፍ አዕላፍ ገዳም ፣ መድረክ የሚያጨናንቁ አገልጋይ ጳጳሳት ፣ ካህናት ፣ ዲያቆናትና ዘማርያን አሉን ፤
-      ከእኛ ወዲህ ማን አለ አማኝ? ከእኛ በላይ ጸዳቂ ፤ ታማኝ አገር ወዳድ ወዴት አለ?! …
ስንታይ ግን፦
-      “ባዕድ እንግዳ” ለመቀበል ሆዳችንን እንደአገር ስናሰፋ ፥ ከጎረቤትና ከወገናችን ጋር ግን “ጠብ ያለሽ በዳቦ” በሚል መንፈስ የተያዝን ፤
-      አገልጋዮቻችን ጸንሰው ወልደው ፣ አሳድገው የሰጡን አንዱ መልክ ዘረኝነትና ልዩነት ነው ፤
-      ከእኛ በላይ ሁሌም ሰው የለም ብንልም ዘወትር ግን እየኖርን ያለነው ከሰው በታች ጅራት ሆነን ነው …
     ሰሞኑን በከፊል የአገራችን ክፍል ብጥብጥና ሁከት ፤ ደም ማፍሰስና ግድያ ነግሶ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ አድራጊው ሌላ ወራሪ ወይም እንግዳ አሸባሪ መጥቶብን አይደለም ፤ ሟችም እኛው፥ ገዳይም ያው እኛው ኢትዮጲያውያን ፤ ንብረት አውዳሚም፥ ንብረት የሚወድምበትም ያው የአንድ አገር ዜጎች ፤ የአንድ ርስት ወሰንተኞች ፤ የአንድ ወንዝ ጠጪዎች እኛው ነን፡፡
      እስኪ አስተውሉ፥ አንድ መቶ ዓመታት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ በእኛና እኛ መካከል የተደረጉ ጦርነቶችን ብናነሳ፦ በ1909 ዓ.ም በራስ ተፈሪና በንጉሥ ሚካኤል መካከል በሰገሌ ፣ በ1922 ዓ.ም በራስ ተፈሪና በራስ ጕግሳ በአንቺም ወይም በበጌምድር ፣ ከ1966-1983 ዓ.ም ወታደራዊው መንግሥት ደርግና ኢሕአዴግ በተለያየ ቦታ ያደረጉት አስቀያሚ ጦርነት ፣ በ1994 ዓ.ም ሁለቱ “ወንድማማች” ኢትዮጲያና ኤርትራ ያደረጉትን ጦርነት (ወታደራዊው መንግሥት በአንድ ጉድጓድ የፈጃቸው የንጉሡ ዘመን መሪዎችና ሌሎችም ሳይካተቱ) ይህን ሁሉ ስናነሳ ምን ይታወሰናል?!

Tuesday 15 December 2015

ቃሉ የሚለው፥ “ከቶ አላወቅኋችሁም ፤” ነው!

     

   በመጽሐፍ ቅዱስ በአገባቡ ወይም እንደተጻፈው ከማይነበቡ ጥቅሶች መካከል አንዱ፦ “ … ከቶ አላወቅኋችሁም ፤ እናንተ ዓመፀኞች ፥ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ።” (ማቴ.7፥23) በማለት የተጻፈልን ቃል ነው፡፡ ይህ ክፍልና ሌሎችም ከዚሁ ጋር የተያያዙም ንባባት ለአፈጻጸም ከፍ ያለ የሥነ ምግባርና የፍጽምናን መንገድ ይፈልጋሉ፡፡ ከዚህም የተነሳ ብዙዎች የተራራው ትምህርት ተብለው የሚታመኑትን ቃላት ማንም ሰው መፈጸም እንደማይቻለው ያስተምራሉ፡፡ በእርግጥም የእግዚአብሔርን ማናቸውንም ሥራ በእግዚአብሔር ጉልበት ፤ ራሱ እግዚአብሔርንም መማር የሚቻለን በራሱ በእግዚአብሔር ዕውቀት ገላጭነትና የጥበብ አስተማሪነት ነው፡፡ ይህ ማለት ግን የተራራውን ትምህርት በራሱ በእግዚአብሔር ጉልበትና መንፈስ መፈጸም ይቻለናል ማለት እንጂ ፈጽሞ መፈጸም አይቻልም ማለት አይደለም፡፡
     ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራው ትምህርቱ ያስተማራቸው ትምህርቶቹ በብዙዎች ዘንድ እጅግ የተደነቁና የሚያስደምሙ ትምህርቶች ናቸው፡፡ እውነትም! የእግዚአብሔር አምላካችን መንገድና ሕጉ ፤ ሥራውም ፍጹም ነውና (ዘዳግ.25፥15 ፤ መዝ.18፥30 ፤19፥7) ፤ እኛም በእርሱ ዘንድ (ዘዳግ.18፥13) ፤ እንደእርሱም ፍጹማን እንሆን ዘንድ ተጠርተናል፡፡ (ዘፍጥ.17፥1 ፤ ማቴ.5፥48 ፤ 19፥21) አዎን! የእግዚአብሔር ቅዱሳንም በፊቱ ያለነውርና ነቀፋ ነበሩ፡፡ (ዘፍጥ.6፥9 ፤ 1ነገ.11፥4 ፤ ኢዮ.1፥1 ፤ ሉቃ.1፥6 ፤ 2፥25) ፍጽምና ወይም በእግዚአብሔር ፊት የበቃ ሆኖ መገኘት ለሰው የሚቻል ነገር አይደለም (ሮሜ.3፥11 ፤ 2ቆሮ.3፥5) ስለዚህም ስለፍጽምናና ቅድስና ስናስብ በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል በተሰጠን ጸጋ እንጂ (ሮሜ.3፥21-24) በሕግ ወይም በራሳችን የምናደርገውም ፤ እናደርገውም ዘንድ የሚገባን አንዳችም ነገር የለም፡፡

Friday 11 December 2015

ወንድሜ ማን ነው? (ክፍል ሁለት)

     

     ቃየን በልቡ ያሰላሰለውን ኃጢአት ከፍጻሜ ማድረስ አድብቷል፡፡ “ኃጢአተኞች እነሆ ቀስታቸውን ገትረዋልና፥ ፍላጻቸውንም በአውታር አዘጋጅተዋልና፥ ልበ ቅኖችን በስውር ይነድፉ ዘንድ።” (መዝ.10፥1) እንዲል ልበ ቅኑን አቤልን ይነድፍ ዘንድ ቃየን በስውር ይናደፍ ዘንድ ተነሳ፡፡ ስለዚህም፥ “ቃየንም ወንድሙን አቤልን፦ ና ወደሜዳ እንሂድ አለው።” ልምድ ያላቸው ወንጀለኞች “ትልቁ ክፋታቸው” ወንጀሉ እንዳይታወቅና ፤ እውነተኛ ፍርድ እንዳያገኙ የምስክር ደብዛ ያጠፋሉ፡፡
       ቃየን ወንድሙን “ወደሜዳ እንሂድ” ያለው አብሮት ሊጫወት ፤ እንደወንድምም ሊያወጋው አይደለም፡፡  አቤል ግን ወንድሜ እንዲህ ያደርግብኛል ስላላለ አብሮት ሄደ፡፡ ለዳኝነት ብይን መስጫው ቁልፉ ምስክር ወይም ማስረጃ ነው፡፡ ቃየን ያለምስክር “በሜዳም ሳሉ ቃየን በወንድሙ በአቤል ላይ ተነሣበት፥ ገደለውም።” (ዘፍጥ.4፥8) የጨለማ ሥራ ካልተሸሸገ በቀር ብቻውን መቆም አይችልም፡፡ “የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ።” (ዮሐ.8፥44) እንደተባለ የዲያብሎስን ፈቃድ ሊያደርግ እግሩን አስቸኰለ፡፡ ኃጢአተኞች ትልቁን ምስክር ህሊናቸውን ዘንግተው የሰው ምስክር ይሸሻሉ፡፡ እግዚአብሔር ግን ሁሉን ያያል!!!

Sunday 6 December 2015

ጌታ ካላለበት



ከመድረኩ ቆመህ ከአውደ ምህረቱ፤
ተፋተህ ተራቁተህ ከእግዚአብሔር ፍርሃቱ፤
“በʻኔ የሚናገር ጌታ ነው” በማለት፤
ለምን ትጮኻለህ? የውስጥህን ክህደት፤

Friday 4 December 2015

ድንግል ማርያም በድንግል ማርያም አንደበት (የመጨረሻ ክፍል)


6.  የእግዚአብሔርን መጋቢነት

           “የተራቡትን በበጎ ነገር አጥግቦአል ፤ ባለ ጠጎችንም ባዶአቸውን ሰዶአቸዋል።” (ሉቃ.1፥53)

      እግዚአብሔር የተራቡትን ከመራባቸው በፊት አዝኖ ሲያስብላቸው (ዘፍጥ.41፥25 ፤ ሐዋ.11፥28) ፤ በተራቡና በሚያስፈልጋቸው ጊዜ ሲያጠግባቸው አይተናል፡፡ (ዘፍጥ.41፥54-56 ፤ ዘጸ.16፥6-18 ፤ ማቴ.6፥26 ፤ 31-32) ድንግል ማርያም በምድር ላይ ትኖር በነበረችበት ወራት ድኃ እንደነበረች የሚያሳየን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል አለ፡፡ (ሉቃ.2፥22-24) በእርሱ መጥገብንም በሚገባ ታውቀዋለች፡፡ እንዲህ ያለውን ምስክርነት “ጠግበው የነበሩ እንጀራ አጡ፥ ተርበው የነበሩ ከራብ ዐርፈዋል” በማለት ቅድስት ሐናም ምስክርነት ስትሰጥ እናያለን፡፡ (1ሳሙ.2፥6)

Tuesday 1 December 2015

የኖድ ምድሩ ሰው (ዘፍጥ.4፥16)

     

    እግዚአብሔር ፍጥረትን ከፈጠረበት ጥበብ በሚልቅ ጥበብ፥ የሰውን ልጅ ፈጠረው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እንደሚሉትም ሌሎቹን በቃልና በዝምታ ሲፈጥር ሰውን ግን “በእጁ አበጅቶ ግብር እምግብር” ፈጠረው ይሉናል፡፡ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም፥ ሰው እጅግ በታላቅ ክብርና ሞገስ መፈጠሩን ይናገራሉ፡፡ (ዘፍ.1፥27 ፤ 2፥7 ፤ መዝ.139፥14 ፤ 145፥10) ዕለትም ዕለትም ከእግዚአብሔር ጋር እጅግ የሚያስደንቅ ንግግርና ጨዋታ ያደርግ እንደነበርም ታላቁ መጽሐፍ ሲነግረን ልባችን እጅግ መደመሙና እጁን በአፍ ጭኖ መደነቁ አይቀርም ፤ ትልቁ ጌታ ከፍጡሩ ጋር ዕለት ዕለት እንደመነጋገር የሚያስደንቅ ምን አለ!? (ዘፍጥ.3፥8)
     ታላቁ መጽሐፍ፥ ዘፍጥረት ምዕራፍ አንድንና ሁለትን እጅግ የሚደንቅ ትስስር ከአምላኩ ጋር እንደነበረው የሚነግረን ብዙም ሳይርቅ በሦስተኛው ምዕራፍ አሳዛኙን ውድቀት ይነግረናል፡፡ ዔደን ገነት ልዩና የእግዚአብሔር ሠላም የሰፈነባት ሆና ለሰው ልጅ የተሰጠች ፤ እንዲሁም የሰው ልጅ ቅዱስና ጻድቅ እግዚአብሔር ራሱን በሚገልጥበት በኪሩቤል አጠገብ መኖር እንዳልሆነለት ፥ በኃጢአት ምክንያት ሁከት ፣ ፍርሃት ፣ ሽሽት ፣ ዔደን ገነት ጭንቀት የሰፈነባት ሆና ሰው ማረፊያ ሲያጣባት እናስተውላለን፡፡  ኖድ ማለት የስሙ ትርጓሜ መቅበዝበዝ ማለት ነው፡፡

Friday 27 November 2015

ወንድሜ ማን ነው? (ክፍል አንድ)

    
        Please read in PDF

  ይህን ጽሁፍ ከመጻፌ በፊት ለብዙ ሰዓታት ውስጤ ከገለባ ይልቅ እስኪቀልብኝ ድረስ “አስቀድሞ ነገር፥ እኔ ራሴ ለሌላው በተለይም ለሃይማኖት ቤተ ሰዎቼ ወንድም መሆን እችላለሁኝ?” ብዬ ከራሴ ጋር ተሟግቻለሁኝ፡፡ ምናልባት ጥያቄው ያን ያህል ከባድ ላይመስል ይችላል ፤ ይህን ጥያቄ ይዘን ወደታላቁ መጽሐፍ ሚዛንነት የተጠጋንና ራሳችንንም በታላቁ መጽሐፍ ሚዛንነት ያየን እንደሆን ግን እጅግ የሚስቡና እይታችንን የሚያጠሩ እውነቶችን እናስተውላለን፡፡
      “ወንድም” የሚለውን ቃል ታላቁ መጽሐፍ ሲፈታው፥ ከአንድ እናትና አባት የሚወለዱትን ብቻ ሳይሆን የአንድ አገር ተወላጆችን (ዘጸ.2፥11 ፤ ሐዋ.7፥23-26) ፤ ከጥብቅ ወዳጅነት የተነሳ እጅግ የተቀራረቡትን (2ሳሙ.1፥26-27) ፤ ከቅርብ ዘመድ የተነሳ የተወዳጁትን (ዘፍ.36፥10 ፤ ዘኊል.20፥14 ፤ ሮሜ.9፥3) ፤ በቃል ኪዳንም (1ነገ.5፥1 ፤ 12) ወንድማማችነት እንዳለ ይነግረናል፡፡ ወንድማማችነት ምንም እንኳ መሠረቱ በደም መወለድ ቢሆንም፥ ከዚሁ ጋር ሊተካከል በሚችል መልኩ ደግሞ ታላቁ መጽሐፍ በአላማ የተሳሰሩትን እኩል አስተካክሎ ያስቀምጣል፡፡

Monday 23 November 2015

ግድ የለም ታገሰው



ጌታ …
ዝም ያለ ሲመስል
በጆሮ እንዳልሠማ
በአይኑም እንዳላየ
                        ቀና ቀና ይላል
                        የመከራው መከር
                        ጭንቅ እያበራየ

Monday 16 November 2015

ድንግል ማርያም በድንግል ማርያም አንደበት (ክፍል ስድስት)




5.  እግዚአብሔርፍርድያደላድላል

“ … ትዕቢተኞችን በልባቸው አሳብ በትኖአል ፤ ገዥዎችን ከዙፋናቸው አዋርዶአል ፤ ትሑታንንም ከፍ አድርጎአል” (ሉቃ.1፥51-52)

    ብዙዎቻችን የክፉዎችን ክፋት አይተን፥ ለእግዚአብሔር ከማሳሰብና በፊቱ ጥቂት ከመታገስ ካለመቻልም በላይ፥ በብዙ ማጉረምረም የተጠመድን ነን ፤ በውጪው አለም የሚኖሩ እልፍ አዕላፍ ዲያስፖራዎቻችንና አገር ቤትም ያሉ ጥቂት የማይባሉ ወገኖች መንግሥት በመክሰስ የተጠመዱ ናቸው፡፡ አንድ ነገር እንደአማኝ እጅግ አምናለሁ ፥ መንግሥት ያጥፋም ፤ አያጥፋም ከሁሉ በፊት ጸሎት እንደሚገባው (1ጢሞ.2፥1-2) ፤ የሚያጠፋ ከሆነም ደግሞ በአገባቡ ሊመከር ፣ ሊወቀስ  ፣ ሊገሰጽ እንዲገባው አምናለሁ፡፡ ይህን ሳያደርጉ ከመሬት ተነስቶ ቱግ ማለት ከድንግል ማርያም የምስጋና ቃል አለመማር ነው፡፡ 

Tuesday 10 November 2015

ከፍቶታል በሩን






የሴቲቱ ዘር፥ የእባቡን ራስ ʼሚቀጠቅጠቀው፤
የአብርሃም ዘር፥ የምድርን ነገድ የሚባርከው፤
ከዳዊት ወገብ፥ በትር የሚሆነው ለምለም ቁጥቋጦ፤

Wednesday 4 November 2015

ጣሊያናዊው የደብር አለቃና - የተከሰሰበት ግብረ ሰዶማዊነቱ




 Please read in PDF

       ስለተከሰሱ ሰዎች መብት የኢትዮጲያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት ሕገ መንግሥት “በፍርድ ሂደት ባሉበት ጊዜ በተከሰሱበት ወንጀል እንደጥፋተኛ ያለመቆጠር ፥ መብት አላቸው፡፡” በማለት ይገልጣል፡፡ (ሕ/መን.አን.20(3)) ነገር ግን “ሕጻናትን የሚመለከቱ እርምጃዎች በሚወሰዱበት ጊዜ በመንግሥታዊ ፥ ወይም በግል የበጎ አድራጎት ተቋሞች ባለ ሥልጣኖች ወይም በሕግ አውጪ አካላት፥ የሕጻናት ደህንነት በቀደምትነት መታሰብ አለበት፡፡”
    በቀደምትነት መታሰብ ያለበት ብቻ ሳይሆን ፦
“ማንኛውም ሕጻን ጉልበቱን ከሚበዘብዙ ልማዶች የመጠበቅ ፥ በትምህርቱ፥ በጤናውና በደህንነቱ ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሥራዎች እንዲሠራ ያለመገደድ ወይም ከመሥራት የመጠበቅ መብትም እንዳለው” በግልጥ አስቀምጧል፡፡
(ሕገ መን.አን.36(1)መ)

Wednesday 28 October 2015

ኢየሱስን የሚጋርዱ - ባህላዊ “ሰባኪ” ዎቻችን



       
                                                 Please read in PDF

     የክርስቶስ አገልጋይ ትጥቁ አጭር (ማቴ.10፥5-11) ፤ ዕለት ዕለት መስቀሉን ተሸክሞ በመከተል የሚኖር (ማር.8፥34) ፤በቁም ሳለ ከሚገድል ቅምጥልነት የራቀና “ወደዓለም ምንም እንኳ አላመጣንምና፥ አንዳችንም ልንወስድ አይቻለንም፤ ምግብና ልብስ ከኖረን ግን፥ እርሱ ይበቃናል።” የሚል ቅዱስ አቋም ያለው (1ጢሞ.5፥6 ፤ 6፥7-8) ፤ በሕይወቱ (ሮሜ.12፥2) ፣ በንግግሩ (ቈላ.4፥6) ፣ በመንገዱ ሁሉ የአምላኩን ስም የሚያስመሠግንና ከማስነቀፍ ፈጽሞ የራቀ ፤ ለሁልጊዜ ለፈጣሪው የሚያደላና የሚኖር ፤ ለሕይወቱ ምሳሌና መርሕ የሚሆነውን ነገር ለመፈለግ ሁልጊዜ እግረ ልቡን ወደ ታላቁ ቅዱስ መጽሐፍ የሚያቀና ሊሆን ይገባዋል፡፡ (ሐዋ.17፥10 ፤ 1ዮሐ.4፥1)
እንዲህ ስል አገልጋይ ባዕለ ጠጋ መሆን የለበትም የሚል አቋም የለኝም ፤ ዳሩ ግን አማኝም ሆነ አገልጋይ መሠረታዊ የሆነውን ነገር፥ ማለትም ምግብን ፣ ልብስንና መጠለያ በማግኘቱ ፣ እርካታ ይኖረው ዘንድ አስፈላጊ ፤ የተገባም ነው፡፡ ይህ ማለት አገልጋይ እንደሚሠራው ሁሉ አገባብ ያለው ደመወዙ ይገባዋል ማለት ነው፡፡ እንዲሁ ገንዘብ የሚጠይቅ የተለየ ነገ ርቢከሰት ፣ በልግስና በመስጠት እግዚአብሔርን እያገለገለ (2ቆሮ.8፥3 ፤ 9፥6) “በመከራ ቀን ጥራኝ፥ አድንህማለሁ አንተም ታከብረኛለህ።” እንዲል፥ እግዚአብሔር እንዲሰጠው ወደእርሱ መመልከት ይኖርበታል፡፡ (መዝ.50፣15) ይህንን የምንለው ሁልጊዜ መንግሥቱንና ጽድቁን መቅደምና ማስከተል ከሌለብን ብቻ ነው፡፡ (ማቴ.6፥33)

Friday 23 October 2015

የፓትርያርክ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስን ንግግር ሳጤነው ምጥ አለበት!!!


ብዙዎች ያልጨከንለትና ያልደፈርንለት እውነት!!!

      በኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በተካሄደው 34  መደበኛ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ፥ ፓትርያርክ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጥቅምት 8 ቀን  2008 ዓ.ም ካስተላለፉት አባታዊ መልዕክት የሚከተለው መልዕክት ላይ ማተኮር ፈለግሁ፡፡
 
“ … የምዕመናን ፍልሰት በየጊዜው እየጨመረ የመሄዱ መነሻ ምስጢር ምንድን ነው? የሚለውን ጥያቄ ቤተ ክርስቲያናችን በአጽንዖት ልታጤነው ይገባል ፤ በዚህ ዙርያ የሚታየው ክፍተት ፈጣን ምላሽ በመስጠት መግቻ ካላበጀንለት ነገ ከባድ የሃይማኖትና የታሪክ ወቀሳ ማስከተሉ እንደማይቀር ልብ እንበል፡፡
     ለመሆኑ ምዕመናን ከቤተ ክርስቲያናችን እየወጡ  ወደሌላ ካምብ ለመግባት ለምን መረጡ?
-       የሚያስተምራቸውን ካህን አጥተው ነውን?
-       የቤተ ክርስቲያናችን ትምህርተ ሃይማኖት ክፍተት ኖሮት ነው?
-       የቤተ ክርስቲያችን አስተዳደር የማያረካ ሆኖ ነውን?
-       የካህን እጥረት ስላለ ነውን?
-       ወይስ ሌሎች ከእኛ የተሻሉ ሆነው ስለተገኙ ነው፤?
የዚህ ሁሉ መልስ በእያንዳንዳችን ኅሊና ውስጥ ቁልጭ ብሎ ስለሚታወቅ የጥያቄው መልስ ለእናንተው ሰጥተናል፡፡  … ”

     ደግሞም ልቀጥል፦ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መጀመርን አስመልክቶ ጥቅምት 12 ቀን 2008 ዓ.ም  ቅዱስነታቸው በሰጡትም መግለጫም እንዲህ አሉ፦

Wednesday 21 October 2015

ድንግል ማርያም በድንግል ማርያም አንደበት ክፍል - 5






4.  በመንፈስ ቅዱስ ደስታ የተመላችም ነበረች

     ደስታ ከመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች አንዱ ነው፡፡ (ገላ.5፥22) ደስታ፥ የመብልና የመጠጥ ፣ በወገን መካከልም የመቀመጥ ፣ በተድላ የመንቀባረር ፣ የመልበስና የማማር ጉዳይም አይደለም ፤ ተድላና ደስታን ለማየት ለመቅመስም የእግዚአብሔር በጎ ፈቃድ ያሻል፡፡ “ያለ እርሱ ፈቃድ የበላ ደስ ብሎትም ተድላን የቀመሰ ማን ነው?” (መክ.2፥25) እንዲል ደስታችንም ፍጹም የሚሆነው በእርሱ ብቻ ነው፡፡ (ዮሐ.15፥11) ዘወትር ለሁልጊዜ በጌታ ልንደሰት እንደሚገባንም ቃሉ ይነግረናል፡፡ (ፊልጵ.4፥4 ፤ 1ተሰ.5፥16)
    ድንግል ማርያም ትልቁ ሐሴትና ደስታዋ በእግዚአብሔር መድኃኒትነት ላይ ያላት መደገፍ ነው፡፡ “መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች” የሚለው መዝሙሯ፥ “እግዚአብሔር ሕያው ነው፥ አምላኬም ቡሩክ ነው፥ የመድኃኒቴም አምላክ ከፍ ከፍ ይበል።” (መዝ.18፥46) ከሚለው ከዳዊት መዝሙር ጋር ፤ “ … የጽድቅንም መጐናጸፊያ ደርቦልኛልና በእግዚአብሔር እጅግ ደስ ይለኛል፥ ነፍሴም በአምላኬ ሐሤት ታደርጋለች።” (ኢሳ.61፥10) ከሚለው ከኢሳይያስ መወድስ ጋር ፤ “ … እኔ ግን በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል በመድኃኒቴ አምላክ ሐሤት አደርጋለሁ።” (ዕንባ.3፥18) ከሚለው ከዕንባቆም የጽናት ዝማሬ ጋር ፍጹም የሚዛመድ ነው፡፡

Tuesday 13 October 2015

አድመኝነት - ከማን የተማርነው ነው?



      
                                   Please read in PDF
            

   ጌታ ኢየሱስ በተያዘባት በሐሙስ ማታው ግርግር፥ ደቀ መዛሙርት አይሁድ ጌታን ቆርጠው ለመግደል በብዙ ጦርና አድማ ተደራጅተው ምክራቸውን እንደጨረሱ ሲያውቁ ፦ “ጌታ ሆይ፥ እነሆ፥ በዚህ ሁለት ሰይፎች አሉ አሉት።” (ሉቃ.22፥38) የአይሁድ የካህናት አለቆች ሙሉ ለሙሉ በአድማ ሲነሳሱ ስላዩ፥ ደቀ መዛሙርቱም ምላሽ ለመስጠት በሰይፍ ለሚያስታጥቅ አድማ ለራሳቸው ተዘጋጁ፡፡ ጌታ ኢየሱስ እንዳያደርጉት በምፀት ቃል “ይበቃል” ቢላቸውም፥ እነርሱ ግን ቃል በቃል ተርጉመው፥ አድማቸውን ወደጥቃት አሸጋግረው የአንዱን ወታደር ጆሮ በመቁረጥ ደመደሙ፡፡ ጌታ ግን “ሰይፍ የሚያነሡ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋሉና ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ።” በማለት በተግሳጽ ቃል ተናገረ፡፡ (ማቴ.26፥52)
     ደቀ መዛሙርቱ ጌታ ከእነርሱ ጋር የተስማማ መስሏቸው ይህን ቢያደርጉም፥ ጌታ ግን ድርጊቱን አብዝቶ ተጠይፏል፡፡ በእርግጥም አድመኝነት የሥጋ ፍሬ ነው ፤ (ገላ.5፥20) ትርጉሙንም ስናሰላስለው ለመለያየት የመጀመርያ ምልክት የሆነ ፤ የግል መሻትና ፍላጎት ባላቸው ሰዎች መካከል የሚፈጠር መለያየት ፤ በፍጻሜም የቤተ ክርስቲያንን አንድነት የሚያጠፋ  ወይም የሚቃወም ድርጊት ነው፡፡ ይህም በአንድ ሃሳብ የሚስማሙና የግል ሃሳባቸውን የሚያስቀድሙ ሰዎች ወገናዊነትን ፤ እኛዊነትን ፤ እኔዊነትን በመፍጠር ፥ በሌላው ላይ በማሾክሾክ ፤ በማማት ፤ በመጥላትም ጭምር ራሳቸውን በማግለል ቡድናዊነትን በመመሥረት በሌላው ላይ የበላይነትን ለማሳየት የሚያደርጉት ድርጊት ነው፡

Wednesday 7 October 2015

አንተ ስትደክም …


          Please read in PDF                     


ብትጠቁር ብትከሳ
ብትሞግግ በአበሳ
አጀቡ የሐዘን
ምትክህ ሰቀቀን …

Friday 2 October 2015

ግብረ ሰዶማዊነትን ለመቃወም ሙጋቤያዊ አቋምም ከመሪዎቻችን ያስፈልጋል!

   
                          Please read in PDF     

                        እኛ ግብረ ሰዶማውያን አይደለንም!!!” (ሮበርት ሙጋቤ)


    በዘመናችን መንፈሳዊ ማንነታችን ስለተጐሳቆለብን ኃጢአትን በአለም መድረክ የሚቃወሙት አለማውያን መሪዎች፥ ከእኛ ይልቅ በብዙዎች ዘንድ የመደመጥን ዕድል ያገኙ ይመስላል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በቅድስና ፍጹም ስትዋብ በአለማውያን መሪዎች ላይ ተጽዕኖ ስለማሳደሯ ምንም ጥርጣሬ የለውም፡፡ ከቤተ ክርስቲያን መለያ ባሕርያት መካከል አንዱ ክርስቶስ በገዛ ደሙ መሥርቷታልና ቅድስት መሆኗ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የቅድስናን ጠባይ ገንዘብ ያደረገችው፥ ከመሠረታትና ቅድስና የባሕርይ ገንዘቡ ከሚሆን ከክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡
     ቤተ ክርስቲያን ከአለማውያን መሪዎች ጋር ያላት ግንኙነት እጅግ ጤናማ መሆን አለበት፡፡ ግንኙነቱ ጤናማ መሆን አለበት ስንል፥ መርሑ ቅድስናና ንጽሕናን ብቻ በተከተለ መንገድ መሆን መቻል አለበት ማለታችን ነው፡፡ ቅድስና በኃጢአተኛው ላይ እጅግ ከፍ ያለ ተጽዕኖ ማሳደር ይችላል፡፡ በቤተ ክርስቲያን በስደት ዘመን የሰማዕታትን አንገት ይቀሉ የነበሩት ወታደሮች፥ በሚያስደንቅ መንገድ የጌታ ባለሟሎች የሆኑትና ከመግደል ለጌታ እስከመሞት የደረሱት የሰማዕታቱን የቅድስና ጉልበት አንገት በመቁረጥ ፤ በማቃጠልና በብዙ መከራ ማሸነፍ ስላልቻሉ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር የክርስቶስ ኢየሱስን ሕይወትና ቃሉን እጅግ በመውደድና በማንበብ ለአገራቸው ሕዝቦች እጅግ ቅን የነበሩትን እንደመሃተመ ጋንዲ ያሉ መሪዎችንም ማንሳትም ይቻላል፡፡

Tuesday 29 September 2015

ድንግል ማርያም በድንግል ማርያም አንደበት ክፍል - 4


                             Please read in PDF          

3.  እምነት

      ያለእምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም ፤ ያለእምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት ካልተቻለ ልናምን የሚገባን እግዚአብሔርን ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ (ዕብ.11፥6) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል ላይ ሁለት ጊዜ የተደነቀውና ምስክርነትም የሰጠው ከእስራኤል መካከል ያጣውን እምነት ከአህዛባውያን አማኞች በማግኘቱ ነው፡፡ (ማቴ.15፥28 ፤ ሉቃ.7፥9) ብዙ ቅዱሳንም እግዚአብሔርን ደስ ያሰኙት “ጻድቅ ግን በእምነት ይኖራል” እንዲል በእምነታቸው ነው፡፡ (ዕብ.11፥4 ፤ 5 ፤ 7 ፤ 8 ፤ 17 ፤ 20 ፤ 21 ፤ 22 ፤ 23 ፤ 28-40)

Saturday 26 September 2015

መስቀልና ራስን (እኔነትን) መካድ

     
                            Please read in PDF      

   ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ገና ከመሰቀሉ በፊት ስለመስቀሉ፥ “ … መስቀሉንም የማይዝ በኋላዬም የማይከተለኝ ለእኔ ሊሆን አይገባውም።” (ማቴ.10፥38) በማለት አስተማረ፡፡ በአሁን ጊዜ፥ ይህ የጌታችን ትምህርት ከመሰቀሉ በፊት እንደተናገረውና እንደተጻፈው ሃሳብ ሳይሆን እንደራስ ሃሳብ ከሚተረጎሙ ክፍሎች አንዱ ነው፡፡ በእርግጥም ጌታችን ከመሰቀሉ በፊት ሰሚዎቹ መስቀልን እንዴት ነበር ሲረዱት የነበረው? ጸሐፊው ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊስ ሰሚዎቹ እንዴት መረዳታቸውን አስተውሎ ይሆን የጻፈው? “መስቀል” ተብሎ የተነገረው ቃል ጌታ ከመሰቀሉ በፊትና ከተሰቀለ በኋላ ሁለት አይነት መልክ አለው ወይም የቃሉ ሃሳብ አንድና አንድ ነው? ሰሚዎቹ ያስተዋሉት መስቀል ጌታ ወደፊት የተሰቀለበትን መስቀል ነው ወይስ ጌታ የዚያኔ ሊናገር ያሰበውን ነው? እኛስ እንዴት ነው እየተረዳን ያለነው? የሚለውን ሐቲታዊ ጥያቄዎችን ማንሳቱ ሃሳቡን የጌታን ሃሳብ በአገባቡ ለመረዳት ያግዘናል፡፡
     “ታላላቅ” የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች፥ የመጽሐፍ ቅዱስ ሃሳብ አንድና ወጥነት ያለው መሆኑን በመስማማት ቃል ይናገራሉ፡፡  ከሁሉም ይልቅ ደግሞ ወንጌላውያን ወንጌልን በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ወይም ቃኚነት ሲጽፉ ታሪክ ቀመስ እንደመሆኑ መጠን አንዳች በማያቅማማ ሁኔታ የጌታችንን ቀጥተኛ ንግግሮችንና ትምህርቶችን አስፍረውታል፡፡  መንፈስ ቅዱስ፥ ቅዱሳን አባቶችን ቅዱሳት መጻሕፍትን እንዲጽፉ ሲነዳቸው ውስብስብና እንዳይገባቸው ወይም እንዳይገባን አድርጎ አልገለጠም ፤ አላጻፈውምም፡፡  በእርግጥም “ልጆችሽም ሁሉ ከእግዚአብሔር የተማሩ ይሆናሉ” (ኢሳ.54፥13 ፤ ዮሐ.6፥45) ተብሎ እንደተነገረ፥ የሚድኑትና የዘላለም ሕይወትን የሚያገኙት ስለእግዚአብሔር ቃል ከእግዚአብሔር ከራሱ የተማሩት ብቻ ናቸው፡፡

Thursday 17 September 2015

እኔን ዛሬ ማረው!




ጉብዝናዬን ላ’ጢአት ፣ ብርታቴን ለነውር ፤
ውበቴን ለወጥመድ ፣ አውዬ የማድር ፤
እኔ ነኝ ጌታዬ ፣ እኔ ነኝ ፣ እኔ ነኝ፤
በግ ከሚያርዱ ጋራ ፣ እሳት ስሞቅ ’ምገኝ፡፡

Wednesday 9 September 2015

ዘመናችን የመባረኪያው ምስጢር



እንኳን ከዘመን ዘመን አሸጋገራችሁ፡፡ አሜን፡፡

       መጽሐፍ ቅዱስ ዘመን የሚለውን ቃል፥ አንድ ረዥም ጊዜን (ገላ.4፥4) ፣ የአንድ ወቅት አገዛዝን (ማቴ.2፥1-2 ፤ ሐዋ.12፥1) ፣ አንዳንዴ ሰዓት በሚለው አገላለጥ አምልኮን ወይም የመዳንን ጊዜ (ማር.1፥15 ፤ 2ቆሮ.6፥2 ፤ኤፌ.2፥6 ፤ 2ጢሞ.1፥9) ፣ ሌላም ተግባር የተከናወነበትን ወይም የሚከናወንበትን ጊዜ (1ጢሞ.4፥1-2 ፤ 1ጴጥ.1፥5-6) ፣ ውስን ጊዜንና (መዝ.102፥24) የመሲህ ኢየሱስ በምድር የነበረበትን ጊዜና (1ጢሞ.2፥6 ፤ ዕብ.1፥1) ሌሎችንም ለማመልከት ቃሉን ይጠቀምበታል፡፡  ስለዚህ ዘመን የሚለውን ቃል እንደሚገኝበት አውዱ፥ በጥንቃቄ ልናየውና ልንተረጎመው ይገባናል ማለት ነው፡፡
   ጊዜያትን የፈጠረ፥ “የዘመኑ ቍጥር የማይመረመር” (ኢዮ.36፥26) ፣ “ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ  … አንተ ግን ያው አንተ ነህ፥ ዓመቶችህም ከቶ አያልቁም።”(መዝ.90፥2 ፤ 102፥27) የተባለለት ቅዱስ  እግዚአብሔር ነው፡፡ (ዘፍጥ.1፥5 ፤ መዝ.102፥24) ስለዚህም ዘመን ከእግዚአብሔር ለሰው ልጆች በስጦታነት ተሰፍሮ ፤ እንኖርበት ዘንድ የተሰጠን በረከት ነው፡፡ ( ዘፍጥ.6፥3 ፤ ኢዮ.14፥5 ፤ 21፥21 ፤ 31፥15 ፤ 39፥4-5 ፤ 139፥16 ፤ ሐዋ.17፥26) የዘመናችን መርሑም አንዱ ሲያልፍ ሌላው እንዲተካ “በብዙ ተባዙ” (ዘፍጥ.1፥28 ፤ 9፥1) ፤ በማለፍ ሕግ ላይ ተመስርቶ ነው፡፡ (መዝ.103፥15)

Saturday 29 August 2015

ድንግል ማርያም በድንግል ማርያም አንደበት (ክፍል - 3)

1.    ምስጋና
       ለምስጋና የተሟሸ ቃል የምናወጣው፥ መንፈስ ቅዱስ አንደበታችንን ሲቃኘውና እኛም ቃሉን ከጸሎት ጋር በማጥናት የበሰለ ማንነትን መያዝ ሲቻለን ነው፡፡ እንዳንዶች ተአምራቱን አይተው ድንቅ መዝሙርን (ዘጸ.15፥1-21) ፤ አንዳንዶች በፊቱ ራሳቸውን በማፍሰስ ላደረሱት ጸሎት ምለሹን ከለመኑት ጌታ ባገኙ ጊዜ (1ሳሙ.2፥1-10) ፤ ሌሎች ደግሞ ድልን በፊቱ ባገኙ ጊዜ (መሳ.5፥1-31 ፤ 16፥24) ፤ የበረቱቱ ደግሞ ሙሉ ተስፋቸው እግዚአብሔር መሆኑን በመታመን (ዕን.3፥1-19) በእግዚአብሔር ፊት እንደዘመሩ ድንግል ማርያምም ልዩና ድንቅ ነገር በእርሷ እንደተደረገ ባመነች ጊዜ በቃሉ መሞላት ውስጥ ሆና የዘመረችው መዝሙር እጅጉን ልብ የሚነካ ነው፡፡
      አባቷ ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት (ማቴ.1፥20 ፤ ሉቃ.1፥27 ፤ 32) በገና እየደረደረ መልካም አድርጎ ይዘምር የነበረ መዝሙረኛ (1ሳሙ.16፥18-23 ፤ መዝ.33፥2) ፤ የመዝሙር መጽሐፎቹም በምስጋናና በውዳሴ እጅግ የተመሉ ነበሩ፡፡ (መዝ.111-117) ድንግል ማርያምም ከእርሱም ተምራለችና በምስጋና ተመልታ ስታመሰግን እናያታለን፡፡ ቃሉም ፥ “… በሁሉ አመስግኑ፤ ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ እናንተ ነውና።” (1ተሰ.5፥17-18) እንዲል፡፡
       ምስጋና የማጉረምረም ፤ የሽንገላ ፤ የሐሰተኝነት ፤ የስድብና ያለማመስገን ተቃራኒ ነው፡፡ (ዘጸ.16፥2 ፤ ዘኊል.14፥26-30) ዲያብሎስ ዘማሪ ስለነበር ፥ ከዚህ ክብሩ በገዛ ትዕቢቱ ሲዋረድና ሲወርድ ሸንጋይ (ኤፌ.4፥14 ፤ 6፥11) ፣ የእግዚአብሔርን ክብርና ሥራ በመንቀፍ የሚሳደብ (መዝ.74፥10 ፤ ኢሳ.52፥5 ፤ ራዕ.13፥5) ፣ በድምጹ ብቻ እያገሳ የሚያስፈራራ (1ጴጥ.5፥8) ፣ ሐሰተኛ (ዮሐ.8፥44) ሆነ፡፡ ለዚህም ነው እግዚአብሔርን (ዘሌ.24፥16 ፤ 1ነገ.20፥10) ፤ እናትና አባቱን የሚሰድብ (ዘጸ.21፥17 ፤ ምሳ.20፥20) እንዲገደል ፍርዱ እንዲሆን በሕግ የተደነገገው፡፡

Wednesday 19 August 2015

አርሞንዔም - ጌታ ክብሩን የገለጠበት ተራራ

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከስድስት ቀን በፊት በጥንት ስሟ “ፓኒያስ” ፥ በአሁን ስሟ ደግሞ “በናያስ” በምትባለው ከገሊላ ባሕር በስተሰሜን ከሔርሞን ተራራ ተዳፋት ሥር በነበረችው በፊልጶስ ቂሣርያ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደ ሆነ ይሉታል? ብሎ ጠየቀ፡፡” (ማቴ.16፥13) ንጹሐ ባሕርይው ጌታ፥ ደካሞችና ገና በእውቀት ያልጎለመሱትን ደቀ መዛሙርት “ሰዎች ማን ይሉኛል?” ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም የሰሙትን ሁሉ ሳያስቀሩ ነገሩት፡፡ “አንዳንዱ መጥምቁ ዮሐንስ፥ ሌሎችም ኤልያስ፥ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው” ብለው ተናገሩ፡፡ ሰዎች ስለጌታ የሰጡት ስያሜ፥ ቀርበውት ያዩት ወይም ከእርሱ የሰሙት አይደለም፡፡ የየራሳቸውንና ከሌሎች ጋር ሲያወሩት የደረሱበት “እምነታቸውን” እንጂ፡፡
      ሰዎች ስለእኛ የሚሉት አንድ ነገር ብቻ ሳይሆን ብዙ ነገር አላቸው ፤ የሚሉት ነገርም ከእኛ ጋር ምንም ዝምድና ያለውም ፤ የሌለውም ሊሆን ይችላል፡፡ ሰዎች ስለጌታ የተናገሩት ከእርሱ ጋር ምንም ዝምድና የሌለውን ነው፡፡ እኛም በተለይ ከታወቀ ነውርና ከኃጢአት ሕይወት ነጽተን በእውነተኛው በጌታ ወንጌል አገልግሎት ውስጥ ስንመላለስና ቤተ ክርስቲያንን በቅዱስ ቅንአት ስናገለግል ብዙ ጊዜ የምንባለው፥ ከእኛ ጋር ምንም ዝምድና የሌለው ነገር እንደሆነ ከዚሁ ለጌታ ከተነገረውና ከደቀ መዛሙርቱ ሕይወት እንማራለን፡፡ (ማቴ.9፥34 ፤ 12፥24 ፤ ሐዋ.21፥37-38 ፤ 24፥5-6) ስለዚህ ብዙ መባላችን ፤ ተብሎም በድርጊት ቢገለጥ ምንም ሊያስደንቀን ፤ ሊያስበረግገንም አይገባም፡፡ (1ጴጥ.4፥12)
    ጌታችን ሁሉንም ነገር ከደቀ መዛሙርቱ ካደመጠ በኋላ ጥያቄውን፥ “እናንተስ እኔን ማን እንደ ሆንሁ ትላላችሁ?” በማለት የጥያቄውን አቅጣጫ ወደእነርሱ ቀየረው፡፡ በአገልግሎት አለም ከብዙ አማኞችና አገልጋዮች ሕይወት የራቀው ጥያቄ ቢኖር ይህ ጥያቄ ነው፡፡ በዙርያችንም ያሉ ይሁኑ ከአጠገባችን ያሉ ምን እንደሚሉን በትክክል አለመረዳት ብዙ ጊዜ የንስሐ በራችንን እንኳ ሲዘጋብን ከማስተዋል እንዘነጋለን፡፡ አንድ አገልጋይ ወይም አማኝ የእግዚአብሔር ቤት እውነተኛ አገልጋዮችና አማኞች ለእርሱ ያላቸውን ነገር በሚገባ ማጤን አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ ይህን ስል አገልግሎቱን ሁሉ በጌታ ከመደገፍ ይልቅ በእነርሱ ቅኝት ሊመራ ይገባዋል እያልኩ አይደለም፡፡

Saturday 15 August 2015

እንደብዙ አጋር!


          Please read in PDF


እንደሚራራ እንደሚያሻግር
እንደሚያጽናና እንደሚያፈቅር
ከጐን እንዳለ ቀኝ ደግፎ
በብርታት ቆሞ በድካም ታቅፎ

Tuesday 11 August 2015

ድንግል ማርያም በድንግል ማርያም አንደበት ስትገለጥ(ክፍል - 2)



         ድንግል ማርያም የክርስቶስ የቃሉ ሙላት እንዳላት በታላቁ መጽሐፍ ከዘመረችው መዝሙር ዋቢ ብንጠቅስ ፥ ለምሳሌ ፦
  
       ነፍሴ ጌታዬን ታከብረዋለች ፤ (መዝ.34፥2 ፤ 44፥8 ፤ 103፥1-4) ድንግል ማርያም የወለደችውን ጌታ “ጌታዬ” ብላ ታከብረዋለች ፤ ታመልከዋለችም፡፡ “ድንግል ፈጣሪዋን ወለደች” እንዲል ፤ እርሷ ፈጣሪዋን ታከብረዋለች ፤ በፍርሃት ታመልከዋለችውም፡፡
       መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች ፤ ( መዝ.18፥46 ፤ 42፥11 ፤ 43፥5 ፤ 69፥32 ፤ 107፥42 ፤ 119፥74 ፤ ኢሳ.45፥15-17 ፤ 45፥21 ፤ 61፥10 ፤ ኤር.9፥24 ፤ ሆሴ.13፥4 ፤ ዕን.3፥18 ፤ 1ጢሞ.2፥3 ፤ 4፥10) የወለደችውን ያንኑ ጌታዋን “መድኃኒቴ” ብላም ትጠራዋለች፡፡ መድኃኒቱ ለእርሷም ፤ ለእኛም ፤ ለአለሙ ሁሉ ነውና፡፡

Friday 7 August 2015

ድንግል ማርያም ፥ በድንግል ማርያም አንደበት ስትገለጥ (ክፍል - 1)

    
                                          Please read in PDF

  የዘመኑ ፍጻሜ ሲደርስ (ገላ.4፥4) በገሊላ ግዛት ናዝሬት በምትባለው ከተማ፥ የሚያስደንቅ የምሥራች  ዜና ተሰማ፡፡ ምሥራቹም በኃጢአት የተበከለው ዓለም ሊቀደስ ፣ ለዓለሙ ሁሉ የሚሆን ምሥራችና መድኃኒት ሕጻኑ ኢየሱስ ሊወለድ እንዳለ ፣  መልአኩ ገብርኤል ከመለኮት ዙፋን ችሎት የተቆረጠውን ውሳኔ ሊያሰማ ወደምድር መጣ፡፡ (ሉቃ.1፥26) ናዝሬት በሰው ሕሊና “መልካም ሰው አይወጣባትም ወይም አይገኝባትም” (ዮሐ.1፥47) ብትባልም፥ ዛሬ ግን መልካም ሰው ድንግል ማርያም ተገኝቶባታል፡፡

Monday 3 August 2015

ክርስቶስን በሚያባብል ቃል ለምን? (የመጨረሻ ክፍል)



ኃጢአትን በማለዘብ አንቃወምም!

       እንኪያስ! ኃጢአትንና ኃጢአተኝነትን በማለዘብ ወይም በማድበስበስ አንቃወምም፡፡ መቃወም ያለብን ፊት ለፊትና በድፍረት ነው፡፡ ወንጌልን ለመስበክ የምንደፍርበትን ድፍረት ኃጢአትን ለመቃውም ካልደፈርንበት ምስክርነታችን በጌታ ፊት የተናቀና የተጣለ ነው፡፡   በተለይም ተመክረው ፣ ተዘክረው ፣ ተወቅሰው ፣ ተገስጸው ፣ ተለምነው ፣ በቁጣም ቃል ብዙ ተብለው አልሰማ ፤ አልመለስ ያሉትን ሐሰተኛ የአዞ እንባ አንቢ አባባዮችን እንደአረመኔና እንደቀራጭ ቆጥሮ (ማቴ.18፥17) ያለፍርሃት መቃወም አገባብ ነው፡፡

Monday 27 July 2015

“መለከት ድራማ”ና የመጽሐፍ ቅዱስ ይትበሐልን አጠቃቀሙ



                                                    Please read in PDF

“ምነው የ“ጥበብ” መንገድን ከፈጣሪ ቃል ጋር ካልተዘባበታችሁ በ“ጥበብነቷ” ብቻ ማሳየት አይቻላችሁምን? ስለምንስ የማሰናከያን ድንጋይ በትውልድ መንገድ  ላይ  ታስቀምጣላችሁ?”

     “መለከት” ድራማ በተከታታይነት በኢትዮጲያ ብሮድ ካስት ቴሌቪዥን በእሁድ መዝናኛ ፕሮግራም ይቀርባል፡፡  እንደመታደል ጊዜ ሰጥቶ ብዙም ድራማን የመከታተል ልማድ የለኝም ፤ ድንገት ግን እግረ መንገድ ከመጣ አያለሁ፡፡ በተለይ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስንና ጌታዬ ክርስቶስን “የሚዳስስ”ና በዚህም ዙርያ በአሉታዊም ሆነ በአዎንታዊ መልኩ የሚንጸባረቅ ከሆነ ትኩረቴን አሳርፍበታለሁ፡፡ እናም “መለከት”ን እንደዋዛ አየሁት ፤ የመጽሐፍ ቅዱስ ይትበሐልን በአንዱ ተዋናይ አማካይነት ሲጠቀም አየሁትና በማስተዋል አጤንኩት ፥ ከዚያም ሁለት ነገርን ከውስጡ እንዲህ አስተውዬዋለሁ፡፡

Friday 24 July 2015

አይበቃም እኮ!


                               Please read in PDF                                           

ልንበላላ ፣ ልንነካከስ ፤
ልንቋሰል ፣ ልንቦዳደስ ፤
ላንተዛዘን ፣ ልንከፋፋ፤
ተጨካክነን ፣ ልንጠፋፋ፤

Monday 20 July 2015

እኛ የክርስቶስን እንጂ የፖፑን (ጳጳሱን) ቃል አንከተልም!!!


                                     

                                                                             Please read in PDF                                                

የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና፤ ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና። (1ጴጥ.2፥21)

    የዘመን ፍጻሜ ደጅ ላይ ነንና ከሐሰተኛው ጠላት ዲያብሎስ (ዮሐ.8፥44) ብቻ ሳይሆን “የክርስትናን ካባና ላንቃ ከደረቡትም አንደበት ቀጥተኛውን የጠላትን ሐሳብ በአደባባይ እየሰማን ነው፡፡ የሮማው ፖፕ “ጌታ እግዚአብሔር አስሩን ሕግጋትና ሌሎችንም ለማሻሻል ሥልጣን እንደሰጣቸውና እንዳሻሻሉም ሰምተናል” ያውም “ግብረ ሰዶምን እንደቅዱስ ተግባር ከመቀበልና ሌሎችም እንዲቀበሉት ከሚያዝ ስብከት ጋር” ፡፡

Friday 17 July 2015

ክርስቶስን በሚያባብል ቃል ለምን? (ክፍል ሦስት)

      
                            Please read in PDF

      የሐሰት መምህራን እውነትን ጨክኖ በመናገር ከሚመጣ መከራና ስደት ይልቅ (2ጢሞ.3፥12)፤ እውነትን ከሐሰት ጋር ሸቃቅጦ በመናገር የሚገኘውን ሥጋዊ ጥቅምና የሚከተላቸው የበዛ ቁጥር ሊኖር እንደሚችል በሚገባ ያውቃሉ፡፡ ሙሴ ከላካቸው አሥራ ሁለት ሰላዮች ፥ አሥሩ ይዘው የመጡትን የሐሰት ወሬ ሰምተው ሕዝቡ ሁሉ ተገልብጠዋል፡፡ ለብዙ ዓመታት ከመራቸው እግዚአብሔርና ሙሴ ይልቅ አሥሩን ወዲያው ተቀበሏቸው፡፡ (ዘኁል.14፥2) “የእስራኤልም ልጆች ሁሉ በሙሴና በአሮን ላይ አጕረመረሙ ማኅበሩም ሁሉ፦ በግብፅ ምድር ሳለን ምነው በሞትን ኖሮ! ወይም በዚህ ምድረ በዳ ምነው በሞትን ኖሮ! እግዚአብሔርም በሰይፍ እንሞት ዘንድ ወደዚች ምድር ለምን ያገባናል? ሴቶቻችንና ልጆቻችን ምርኮ ይሆናሉ ወደ ግብፅ መመለስ አይሻለንምን?” ብለው እስከመካድ የደረሱት ከሐሰት መምህራን አባባይ ቃል የተነሳ ነው፡፡

Monday 13 July 2015

መሞቱ ጥቅም ነው!


                      Please read in PDF   

የ“እኔ አልክድህም” ፣ ስሜታዊ ግለት ፤
ቀደም ቀደም የሚል ፣ የእዩኝ ማንነት ፤
አንተ ደግ መምህር !
አትሞትም ይቅር ! …

Thursday 9 July 2015

ሐዲስ ሕይወት



                                                 Please read in PDF



ምንጭ ፦ ቴዎፍሎስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ዘኢትዮጲያ መልእክት ፤ ፩ኛ አመት የፓትርያርክነት በዓለ ሢመት መጽሔት ፤ ግንቦት ፩ ቀን ፲፱፻፷፬ ዓ.ም ፤ ገጽ ፯- ፱፡፡

     ሰላም ለክሙ ወጸጋ እግዚአብሔር አቡነ ወእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘአፍቀረነ ወሐደሰ ለነ ፍኖተ ሕይወት በመንጦላዕተ ሥጋሁ ከመ ናንሶሱ ውስተ ሐዲስ ሕይወት ወወሀበነ ፍሥሐ ዘለዓለም ዘሎቱ ክብር ወስብሐት ለዓለም ዓለም፡፡
     የሰው ልጅ ዳግም ልደት ያገኘበት መንፈሱ ፤ ሕሊናው ፤ ሁለንተናው የታደሰበት ሁል ጊዜ በየቀኑ የሚታደስበት የዘለዓለም ፍሥሐ መገኛ የሚሆን የእግዚአብሔር ጸጋ ከእናንተ ጋር ይሁን፡፡

      ይህን የሐዋርያውን መልእክት መሠረት በማድረግ የእግዚአብሔር ረቂቅ ጥበብ በየጊዜው ያስነሣቸው አበው ሊቃውንት እየተመራመሩ ያደራጁትን የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በዘመናችን የቃልና የጽሁፍ ማሰራጫ ዘዴዎች አማካይነት በአዲስ መልክና አቀራረብ ተርጉመን ለማቅረብ ግዴታችንም ምኞታችንም ስለሆነ በልዑል እግዚአብሔር ፈቃድ ግንቦት  ፩ ቀን ፲፱፻፷፫ ዓ.ም የኢትዮጲያ ፓትርያርክ በኢትዮጲያ ምድር ከተሾመበት ጀምሮ በየጊዜው የሚታተም አንድ መጽሔት መሥርተናል፡፡ ስሙንም “ሐዲስ ሕይወት” ብለነዋል፡፡ ይህም ከላይ የጠቀስነውን የሐዋርያውን ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡

Sunday 5 July 2015

ክርስቶስን “በሚያባብል ቃል” … ለምን?! (ክፍል ሁለት)



                                       Please read in PDF

እኒህም፦
       ክርስቶስን እንደሌሎች በሚያባብል ቃል አንሰብክም፡፡
       ሐሰተኝነትንም በማለዘብ አንቃወምም፡፡

ክርስቶስን በሚያባብል ቃል ስላለመስበክ

“እምነታችሁም በእግዚአብሔር ኃይል እንጂ በሰው ጥበብ እንዳይሆን፥ ቃሌም ስብከቴም መንፈስንና ኃይልን በመግለጥ ነበረ እንጂ፥ በሚያባብል በጥበብ ቃል አልነበረም።” (!ቆሮ.2፥4-5)

   ወንጌል ስንሰብክ የሰዎችን ነጻነት (የአመለካከትና የማሰብ) አንጋፋም፡፡ ይህንን ላለመጋፋት ዕውቀትን በጥበብ የመግለጥ መንፈስ ቅዱሳዊ ጸጋን እንጂ (ሐዋ.17፥16-17 ፤ 1ቆሮ.12፥8) የማባበልና የመሸቃቀጥን መንገድ አንከተልም፡፡ የተቆረጠን እውነት ለመናገር በእርግጥም የቆረጠ ልብና መንፈሳዊ ጭካኔ ያስፈልጋል፡፡

Wednesday 1 July 2015

ዲያስፖራዎቻችንን አናምናቸውም!!!

     
                                       Please read in PDF

     ይህንን ፎቶ ሳይ፥ ደንግጬ ክው ብዬ ነው የቀረሁት!!!  ማን ያምናል ኢትዮጲያውያን “ግብረ ሰዶም በመጽደቁ ደስ ብሏቸው ሰልፍ ወጡ ፤ ወይም እንዲጸድቅላቸው እነርሱም ሰልፍ ወጡ” ቢባል?! ግን ይኸው ሆኖ አየን፡፡

   

Sunday 28 June 2015

ስለግብረ ሰዶማዊነት ከአየርላንድ ስህተት ምን እንማራለን?

     
                            Please raed in PDF                        

   ጌታ እግዚአብሔር የእስራኤል ልጆች ከግብጽ በወጡ ጊዜ እርሱን በማክበርና በመፍራት እንዲያመልኩት በዓላትን ሰጥቷቸዋል፡፡ ከተሰጡት በዓላት መካከል ደግሞ የፋሲካ ፣ የመከርና የዳስ በዓላት የትኛውም እስራኤላዊ ከሚኖርበት ከስደት ምድሩ በመምጣት በእስራኤል ምድር ተገኝተው እንዲያከብሩ አዟቸዋል፡፡ (ዘጸ.23፥14፥17) በእነዚህ የበዓል ወራት የእስራኤል ጎዳናዎች ሁሉ የሚሸቱት እጅግ የተወደደውን የመንፈሳዊነትን ለዛና ዝማሬ ነው፡፡
      ከጥቂት ዓመታት በፊት በካቶሊክና በፕሮቴስታንት ጎራ ክርስትናዋን ከፍላ ጎዳናዎቿን በደም ያጨየቀችው አየርላንድ ፤ አሁን በጎዳናዎቿ የተሰማው ነውር ጆሮን ጭው የሚያደርግ ነው፡፡ ግብረ ሰዶምን በወንጀል ህጓ ጠቅሳ በመከላከልና ለጋብቻ ባላት እሴቷ በአገራችን ካለው ሕግና እሴት ጋር እጅግ የተቀራረበ ነበር፡፡ አየርላንድ በወንጀል ህጓ በግልጥ ግብረ ሰዶምን መከልከል ብቻ ሳይሆን ፈጽመው የተገኙትንም ትቀጣ ነበር፡፡

Sunday 21 June 2015

ክርስቶስን “በሚያባብል ቃል” … ለምን?! (ክፍል አንድ)

    
                                               Please read in PDF

    ጌታ እግዚአብሔር የነጻነት አምላክ ነው ፤ የወደድነውን ፣ ሕሊናችን የመረጠውን ኃላፊነትን ከሚያስከትለው ውጤት ጋር የመቀበል ሙሉ ነጻነትን ሰጥቶናል፡፡ መንገዳችንን እንደእስራኤል ዘሥጋ ቀድመን ማጥራትና መምረጥ ከእኛ ነው የሚጠበቀው፡፡ መንገዶቹም በረከትና መርገም የሚባሉ እንጂ  ሌላ ሦስተኛ አማራጭ የለም፡፡ ይህንን እውነት ነቢዩ ቅዱስ ሙሴ ምድረ ርስትን ሊወርስ ላለው ፥ ለአዲሱ ትውልድ ሕጉን ለማስተማር ፤ የምክርንም ቃል በተናገረበት አንቀጹ እንዲህ ብሏል፦
“እነሆ፥ እኔ ዛሬ በፊታችሁ በረከትንና መርገምን አኖራለሁ፤ በረከትም፥ እኔ ዛሬ ለእናንተ የማዝዘውን የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ብትሰሙ ፣ መርገምም፥ የአምላካችሁን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ባትሰሙ፥ ዛሬም ካዘዝኋችሁ መንገድ ፈቀቅ ብትሉ፥ ሌሎችንም የማታውቋቸውን አማልክት ብትከተሉ ነው፡፡” (ዘዳግ.11፥26-29)