Friday 30 November 2018

በደጅ ነው!

Please read in PDF

እዚያ ማዶ ጭስ ይጨሳል
ከዚህ ማዶ ፍህም አመድ ይወልዳል
እዚያ ማዶ ይበርዳሉ
እዚህ ማዶ ለብበዋል [ለብ ብለዋል]

Sunday 25 November 2018

ነገሌ አርሲ ኪዳነ ምሕረት ዛሬም የስብከት ርዕሳቸው እኛ ነን!


   ከነጌሌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ባሻገር፣ በኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን በግልጽ በከሳሾቻችን “አእላፋት” ክስ ተከሰን የቀረብነው 2005 ዓ.ም ነበር፤ ከዚያኔ ክሶች የማይዘነጋኝ፦ “ኢየሱስን መካከለኛችን ነው” ብሎ ኮርስ ላይ አስተምሯል ብለው፣ ያስተማርኩበትንና ለተማሪዎች የሰጠኹትን የራሴኑ ማስተማርያ አቀረቡ፤ በተመሳሳይ መልኩ ይኸንኑ ትምህርት ያስተማርኳትን “ጓደኛዬን” ምስክር አቁመው አስመሰከሩ፤ ያሳቀኝ ግን ከዚህ በኋላ የተናገሩት ነው፤ “እኛ ጐጃምና ጐንደር ከሚገኙ ከታወቁ ጠንቋዮች ጋር ጥብቅ የትምህርት ቁርኝት እንዳለን በጊዜው የኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን የስብከተ “ወንጌል” ኀላፊ ተናገረ። እንግዲህ በእነርሱ አመክንዮ “ጐጃምና ጐንደር ውስጥ ʻኢየሱስ መካከለኛዬ ነውʼ የሚል ጠንቋይ አለ ማለት ነው? …”፤ ለምን እንዲህ እንዳሉ ይገባኛል። ክሳችን ከወንጌል ውጪ እንደ ኾነ ሰዎች እንዲያምኑላቸው!!! ዳሩ ከከንቱና ከውሸት ልፍለፋ አይዘልም! ያንን ኹሉ አልፈን ዛሬም በምሕረቱ አለን! ነገንም የምንመካው በጌታችን ኢየሱስ ብቻ ነው! አንዳንዶች አብረውን ጀምረው ዛሬ ስለ ክርስቶስ ጨክነው አብረውን ባይቆሙም!

Friday 16 November 2018

የሚጤስን ክር የማያጠፋ እውነተኛ ብርሃን! (ኢሳ. 42፥3)

  Please read in PDF

 የሚጤስ ክር ምኑ ነው የማይጠፋው? ራሱስ ሊጠፋ የሚጤስ አይደለምን? የተቀጠቀጠ ሸንበቆ ምኑ ነው የማይሰበር? ያልጠቀጠቀጠ ሸንበቆ በራሱ ምን አቅም ኖሮት? እልቅ ድቅቅ፣ ስብር እንክትክት ያለውን ደካማ ኀጥዕ፣ መሲሁ እንደሚያቃና፣ እንደሚያበረታታ፣ እንደሚያጸና ነቢዩ ኢሳይያስ የሩቁን እጅግ አቅርቦ አይቷል። ለወደቀው ማኅበረ ሰብ፣ ኢሳይያስ የመጽናናትን ቃል ይናገራል፤ እስራኤል ነጻ ትወጣለች፤ ተበታትናም አትቀርም፣  እንደገናም ትደራጃለች፤ ተስፋ የተቆረጠባት አገር ሆና አትቀርም፤ የዛሉት ምርኮኞቿን የሚያበረታታ ኀይል ይመጣላቸዋል፣ ይሰጣቸዋልም እያለ ነቢዩ ሕዝቡን ያበረታታል። በፍጻሜው ግን ክርስቶስ ሰዎችን ከኅጢአት ነጻ አውጥቶ፣ በታላቅ ትድግናውና ቤዛነቱ ድኅነት እንደሚሰጣቸው የሚያመለክትና፣ ለኀጥዐን ፍጹም ቸርነትና ርኅራኄ እንደሚያደርግላቸው የሚያመለክት ክፍል ነው።


  አዎን! በሥጋ ሞቱ ሊያድነንና ሊቤዠን ወደዚህ ዓለም የመጣው ቅዱሱ መሲህ፣ መድኅን ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ፣ በኀጢአት ለወደቅነው ለእኛ የሕይወት ትንሣኤያችን ነው። በመምጣቱ ፈጽሞ አድኖናል፣ ተቤዥቶናል፣ አስታርቆናል፣ ከአባቱና ከእርሱ፣ ከመንፈስ ቅዱስም ጋር እንኖር ዘንድ የጽድቅ ብቃት ኾኖናል፤ እርሱ በበደላችንና በኀጢአታችን ሙታን የነበርነውን (ኤፌ. 2፥1)፣ እጅግ ሊጠፋ እንደሚጤሰው ክር ልንጠፋ የደረስነውን፣ ደቅቀን እንደ ሸንበቆ ያለነውን፣ አንዳች ጥቅም ያልነበረንን … የተጠጋጋን ብቸኛ መጠጊያ አምባችን ነው፤ ክርስቶስ ኢየሱስ ጌታችንና መድኀኒታችን።

Monday 12 November 2018

ቤተ ክርስቲያን፣ ተጐታችና ዘመነኛ ችግሮቿን አስተውላ ይኾንን!? (ክፍል 3)

Please read in PDF

1.1. ጥንቈላ
 ይህ ችግር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በግልጥ እንዳለ ይታወቃል፤ ግን አይደፈርም፣ ደፍረው የሚናገሩ ይገደላሉ፣ ይገለላሉ፣ ይተቻሉ፣ ይነቀፋሉ፣ ይወገዛሉ፤ ነገሩ ግን ሥር ሰድዷል፤ ከምንናገረው በላይ በቤተ ክርስቲያን ስምና አከባቢ ተሰግስገው አሉ፤ ዓርማቸው፣ መለያቸው፣ መታወቂያቸው … ቤተ ክርስቲያኒቱ የእኔ በምትላቸው ንዋያትና ሰዎች ጭምር ነው። መስተፋቅር፣ አንደርቢ፣ ሰብስቤ፣ “አስማት” … የሚባሉ የጥንቆላ ሥራዎች በብዛት የሚሠሩት በቤቱ ጥቂት በማይባሉ ቀሳውስትና ደባትራን ነው። ይህን ያጋለጡ ብዙዎች አይሰደዱ ተሰደዋል፣ አይንገላቱ ተንገላተዋል፤ ይህ ሲኾን እማኝ ምስክር ከሚኾኑት መካከል አንዱ ነኝ! ጠንቋይ ቀሳውስትን፣ ደባትራንን፣ መሪ ጌቶችን፣ መነኮሳዪይቶችን … በመቃወማቸው የተሰደዱ፣ የተዋረዱ፣ የተገደሉ … ሰዎችን ከሚያውቁ ምስክሮች አንዱ ነኝ!
    የእግዚአብሔርን እውነተኛ አስተማሪነት (ኢሳ. 30፥20) አለመቀበል፤ በትምህርቱም አለመጽናት የሐሰት መምህራን ትምህርት ሾልኮ ለመግባት ሠፊ በር ይከፍታል (2ጴጥ. 2፥1)፤ በቤተ ክርስቲያናችን እንደ ቤተ ክርስቲያናችን የመጻህፍት ጽህፈት ቀኖና መሠረት በቀለማት አጊጦ ከሚባዙትና ከቤተ ክርስቲያኒቱ መጻህፍት ጋር ታትሞ እኩል በየመጻህፍት መደብሩ ከሚሸጡት መጻህፍት መካከል አንዱ ዐውደ ነገሥት የሚባለው የጥንቈላ መጽሐፍ ነው። መሥተፋቅር፣ አስማት የሚደግሙ፣ ሞራ ገላጮች፣ መናፍስት ጠሪ፣ ሙታን ሳቢዎች … እና ሌሎችም የጥንቈላ ሥራዎች ሁሉም ለማለት ሊያስደፍር በሚችል መልኩ የሚከናወነው ከደብተራ እስከ ካህናት ባሉት የቤተ ክርስቲያኑቱ አገልጋዮች ነው።

Thursday 8 November 2018

ነጠላ አስከባሪው!

ሕይወቱ በኮንሰርት በዘፈን ጨቅይቶ
ኀጢአት ነግሦ በʻርሱ ከጸጋ ደኽይቶ

Saturday 3 November 2018

ቤተ ክርስቲያን ተጐታችና ዘመነኛ ችግሮቿን አስተውላ ይኾንን!? (ክፍል 2)

Please read in PDF

ኹሌም የቤተ ክርስቲያንን ችግር አንስተን ከብዙ ወገኖች ጋር በግልም በጋራም ስንወያይ፣ ውስጤን የሚነካኝና የሚያስጨንቀኝ ነገር ይህ ነው። ወደ ዋናው የችግሩ መንስኤ መሄድን አንፈልግም። በደፈረሰው ወራጅ ላይ እንከራከራለን፣ የወራጁን ምንጭ የማጥራት ሥራ ላይ ለመረባረብ እንገፋፋለን እንጂ መሠረታዊውን ችግራችንን፣ ከምንጩ ያፈነገጠውን ነገራችንን አጢነን፣ አስተውለን በልበ ሰፊነት ልናይ፣ ልንወያይ፣ በልበ ሰፊነት ተነጋግረን … መፈለግንም ማድረግንም (ፊልጵ. 2፥13) ከሚሠራው ጋር ለመሥራትና ለመቃናት አንተባበርም። ምንጩ ሲጠራ ወራጁም እንደሚጠራ እናውቃለን እንጂ አምነን ለመነሣት ለክፋት ጨካኞችና ለእግዚአብሔር ፍጹም ያደላን አይደለንም። ከዚህ የሚከፉት ይልቅ ያሉትን ችግሮች ብናይ በአሁን ሰዓት በግልጽ ከሚታዩት ችግሮች አንዱና ዋናው፦