Tuesday 26 March 2024

ነገረ ሥላሴን የምናጠናበት ምክንያት (ክፍል ፲)

 Please read in PDF

ካለፈው የቀጠለ …

  1. ስሞቹ አጠራርና አጠቃቀም ረገድ የሚያመጣው ተፋልሶ የለም።

የሥላሴን ትምህርት በትክክል የማይረዱ ሰዎች ከሚሠሯቸው ስህተቶች መካከል አንዱ፣ በስሞቻቸው አቀማመጥ መሠረት የሥልጣን ተዋረድና የማቀዳደም ሥራ መሥራታቸው ነው። በማቴዎስ ወንጌል አጠቃቀም ውስጥ፣ “አብ ወልድና መንፈስ ቅዱስ” ብሎ (ማቴ. 28፥19) መጥራት የተለመደና በብዙዎች ዘንድ “ተቀባይነት” ያለው አጠራር ነው።

በመለኮታዊ አጠራር አብዛኛውን ጊዜ አብ በቀዳሚነት ሲጠሩ፣ ወልድና መንፈስ ቅዱስ በመቀጠል ይጠራሉ፤ በምሥራቃውያንና ምዕራባውያን አብያተ ክርስቲያናትም ነባሩ አጠራር ይኸው ነው፤ አጠራሩ አምላካዊ ተዋረድን ወይም የጊዜ መቀዳደም የሚያስከትል እንዳይደለ፣ ሦስቱም አካላት እኩል ሥልጣን (ዮሐ. 5፥21) አላቸው፤ እኩል ክብር (ዮሐ. 5፥23) ይገባቸዋል፣ እኩል መለኮት (ዮሐ. 10፥30) ናቸው።

ይኹንና፣ በተወሰኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ውስጥ ደግሞ፣ ወልድ ቀድሞ የሚጠራበት ስፍራም አለ፤ “የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ኅብረት” (2ቆሮ. 13፥14) በሚለው ምንባብ ውስጥ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ተጠርቶአል። በኤፌ. 4፥4-6 ባለው ክፍል ደግሞ መንፈስ ቅዱስ አስቀድሞ የተጠቀሰ መኾኑን እረዳለን። በ2ተሰ. 2፥13-14 ላይ ደግሞ አስቀድሞ እግዚአብሔር አብ ተጠቅሶ ቀጥሎ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሲጠራ፣ በመጨረሻም ደግሞ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲጠራ እንመለከታለን።

አስቀድመን እንደ ተናገርነው፣ አንዳንዶች አብ ስለ ቀደመ ብቻ በጊዜና በዘመን ከወልድና ከመንፈስ ቅዱስ የሚበልጥ ይመስላቸዋል፤ ኹለቱ ስለ ተከተሉ ደግሞ ከአብ እንደሚያንሱና በጊዜ በኋላ “እንደ መጡ ወይም እንደ ተገኙ” አድርገው ሲያስተምሩ እንሰማለን። ነገር ግን ሥላሴ ወይም ሦስቱም አካላት፣ እኩልና እንደ ማይቀዳደሙ የቅዱሳት መጻሕፍትን ምስክርነት ማስተዋል እንችላለን።

“የሰው ባሕርዩ በአካል ቢካፈል፣ በየራሱ ልብ በየራሱ ቃል፣ በየራሱ እስትንፋስ ያለው ሆኖ፣ በየራሱ ልዩ ልዩ ሥራውን ይሠራል። ሥላሴ ግን አካላቸው የተለየ ሲኾን፣ ባሕርያቸው ተከፍሎ የሌለበት አንድ ነው።”[1]

ሥላሴ ባላቸው የተግባር ወይም የግብር ልዩነት፣ በመለኮታዊ ማንነታቸው ወይም ባሕርያቸው ላይ አንዳችም የሚያስከትለው መበላለጥ ወይም ልዩነትን አያስከትልም። ለምሳሌ፦ የሰው ልጅን በማዳን ግብር ውስጥ አብ ዓለምን ሲወድድ (ዮሐ. 3፥16)፣ ወልድ ደግሞ በተለየ አካሉ መጥቶ ተሰቅሎ አዳነን (ኤፌ. 1፥5-7)፣ መንፈስ  ቅዱስ ደግሞ ይህን ዘላለማዊ መዳን አተመ ወይም አጸደቀ ወይም መላ ዓለሙ እንዲድን እንዲታወጅ አደረገ (ኤፌ. 1፥13-14)። ሥላሴ ይህን ሲያደርግ በመካከላቸው አንዳችም መበላለጥና መቀዳደም ሳይኖር በፍጹም እኩልነት ነው።

ይቀጥላል …



[1] መሠረት ስብሐት ለአብ (አለቃ)፤ ገጽ 280

3 comments:

  1. አሜን አሜን አሜን ተባረክ

    ReplyDelete
  2. አሜን አሜን ጌታ ኢየሱስ ይክበር::.
    እንደ እግዚአብሔር ያለ ማንም የለም።

    ReplyDelete
  3. a lot stay blessed

    ReplyDelete