Monday 10 July 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አሥራ ሦስት)

Please read in PDf
3.    ይጣን፦ ብዙ ስሞች ያሉት ያሉት ሲሆን፣ ሰይጣን በዕብራይስጡ አሰናካይ፣ ስም አጥፊ፤ (ኢዮ.1፥6 ፤ ዘካ.3፥1 ፤ ማቴ.4፥10 ፤ ራእ.12፥9)፤ ዲያብሎስ ደግሞ ስም አጥፊ፣ ከሳሽ፤ ቤልሆር ማለት ደግሞ የማይረባ ከንቱ (2ቆሮ.6፥15)፤ አብዶንና አጶልዮንም አጥፊ (ራእ.9፥11) ተብሏል፤ በሌላ ሥፍራ ደግሞ የዚህ ዓለም ገዥ(ዮሐ.12፥311)፣ ወይም የዚህ ዓለም አምላክ (2ቆሮ.4፥11) ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በተለይም ደግሞ ስለተንኮለኛነቱና አታላይነቱ የቀደመው እባብ ወይም ታላቁ ዘንዶ(ራእ.12፥9)፣ ዛቻ ወዳጅና የሚያስፈራራ ስለመሆኑ ደግሞ “የሚያገሳ አንበሳ” ተብሏል፤ (1ጴጥ.5፥8)፡፡
     ሰይጣን ዋና ዓላማው ሰዎች ለጌታችን ኢየሱስ ያላቸውን ትኩረት ማስነፈግ ነው፡፡ ትኩረታቸውንና ፊታቸውን ከኢየሱስ ዘወር ባደረጉ ጊዜ ለማን እንደሚያደሉና ወደማን እንደሚያቀኑ በትክክል ያውቀዋል፡፡ ይህንንም ለማድረግ ስውር መረቡን ይዘረጋል፡፡ የክፋት መረቡንም ለመዘርጋት የሚራዱ ብዙ ኃይላትና ሠራዊት፣ ተባባሪዎችም አሉት፤ (ኤፌ.6፥10)፡፡ ከዚህም ባሻገር ልናጣጥልና ልንንቀው የማንችለው የክፋት ጥበብንም የተመላ ነው፡፡

     እንደባለ አእምሮና እንደልበ ሰፊ ስናስብ፣ ከኢየሱስ ጌታችን ላይ ዓይኖቻችንን አንስተን በፍጡር ላይ[እርሱን በሚያገለግሉ አገልጋዮች ላይ ጭምር] የመጣላችንን ምክንያት ሁሉ በሰይጣን ላይ አናላክክም፡፡  ብዙ የክፋት ወጥመድ ያጠመደንና ያገኘን በገዛ ራሳችን ባለመትጋታችን ነውና፡፡ ስንፍናችንን ሁሉ በሰይጣን ላይ ማላከክ ከኃላፊነት እንድናመልጥ አያደርገንም፡፡ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር በሌላ ማናቸውም [በሰማይም በምድርም ባለ ነገር] ላይ ብናሳርፍና በማሳረፋችንም ሁሉ ለሚያገኘን ነገር ተጠያቂዎቹና ኃላፊነቱን ወሳጆቹ እኛ እንጂ ሰይጣን አይደለም፡፡ ሰይጣን ከመጀመርያውም ተፈርዶበታልና፡፡
     እውነተኛ አማኝና ሰይጣን በጉርብትና መልክም ይሁን በማናቸውም መንገድ አንድ ላይ መሆን አይችሉም፡፡ ሔዋን እንደዋዛ ከሰይጣን ጋር የመሠረተችው ወዳጅነት ለከባድ ውድቀት ዳርጓታል፡፡ ምንም እንኳ ላደረገችው ነገር በሰይጣን ብታመካኝም ከመጠየቅም ፈጽሞ አላመለጠችም፡፡ ስለዚህም አማኝ ቃሉን በማጥናት ዘወትር ሊተጋና ከጸሎት ችላ ሳይል በተግባሩ፣ በጠባዩ፣ በስሜቱ በሰይጣን ተጽዕኖ ሥር ከመሆን ወይም ከመውደቅ በእጅጉ መጠበቅ አለበት፡፡
      ሰይጣን ሌላው ባሕርይው አስመሳይና ተለዋዋጭ ጠባይ ያለው መሆኑ ነው፡፡ “እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ፥ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች ናቸውና፡፡ ይህም ድንቅ አይደለም፤ ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና፡፡ እንግዲህ አገልጋዮቹ ደግሞ የጽድቅን አገልጋዮች እንዲመስሉ ራሳቸውን ቢለውጡ ታላቅ ነገር አይደለም፤ ፍጻሜአቸውም እንደ ሥራቸው ይሆናል” (1ቆሮ.11፥11-15)፡፡ ከዚህ ምንባብ የምነስተውለው ሰይጣን ብቻ ሳይሆን፣ አገልጋዮቹም ጭምር ልክ እንደእርሱ በማስመሰል የተካኑ መሆናቸውን ነው፡፡
    የእግዚአብሔርን ሥራ ለመቃወም በማስመሰል የሚቀርብ ወይም አሳቻ ሰዓት የሚጠብቅ ነው፡፡ ሌባና ወንበዴ ስለሆነ ሥራውን በብርሃን ሁሉ እያየው አይሠራም፡፡ እግዚአብሔር ልጆቹን በብርሃን እንዲመላለሱ ሲፈቅድና ሲያጸና ሰይጣን ግን በተንኮሉ የክፋትን ሥራ ሊሠራ፣ አሳቻ ሰዓት ጠብቆ እንክርዳድን ይዘራል፤ (ማቴ.13፥24)፡፡ ስለዚህም በቅዱስ ቃሉ ውስጥ እንኳ የራሱን ሃሳብ ለመናገር ይጥራል፡፡ የቃሉንም ኃይልና ዓውድ ለራሱ ክብር ሊጠቀምበት እጅጉን ይደክማል፡፡
     ይህ ተለዋዋጭ ባሕርይው አደገኛነቱንና አይናቅነቴውን ያስገዝበናል፡፡ ሥራዎቹን በጽድቅ እርሻ መካከል እንኳ የእንክርዳድን መዝገብ መሰወር እስከመሻት ስለሆነ ፍጹም የቃሉ ብርሃንና የመንፈስ ቅዱስ አስተውሎት ያስፈልገናል ማለት ነው፡፡ ያለእግዚአብሔር አቅምና ችሎታ ስውሩን የጠላት ዲያብሎስን አሠራር ልናውቀው አንችልም፡፡ ምክንያቱም የዘወትር ጥረቱና ዋና ዓላማውም ሰዎች ትኩረታቸውን ከጌታችን ኢየሱስ ላይ እንዲያነሱና በራሳቸው ወይም መምህራኖቻችን ወይም ዋኖቻችን ባሏቸው ሥጋ ለባሾች ላይ ልባቸውን እንዲጥሉ ማድረግ ነውና፡፡ 
      አማንያን ትኩረታቸውን ከኢየሱስ ላይ ሲያነሱ፣ ውጤቱ ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ ሰይጣን በሚገባ ያውቀዋል፡፡ ይህንን ለማድረግም ኀይሉን ሁሉ ይጠቀማል፡፡ ከጌታችን ኢየሱስ ላይ ዓይኖቻቸውን አንስተው ወደሌላ[ወደሰይጣን] የተመለከቱ ሁሉ በመንፈሳዊ አምልኮዓቸው ፍጹም አመንዝረዋል፤ ከማይወጡበትም ፍጹም ዓለማዊነትና ክህደት ውስጥ ተዘፍቀው ቀርተዋል፡፡ አስተውሉ! የክህደትን ቁልቁለት የምንጀምረው ትኩረታችንን ከጌታችን ኢየሱስ ከቤዛነቱና ከሊቀ ካህናትነቱ ባነሳን በዚያው ቅጽበት ነው፡፡
      በዚህ ዘመን በአስባበ “የጌታ አገልጋይን” ማክበር፣ መውደድ፣ መቅረብ … በግልጥ ጌታችን ኢየሱስ ሲገፋ እያየን ነው፡፡ ሎሌው እየገነነ ጌታውና የቅዱስ ቃሉ ብርሐናዊ ፍቺ ሥፍራ እያጣ ነው፤ አገልጋይን በኢየሱስ ሥፍራ የመተካት ሥራ በአደባባይ ሳይታፈርበት እያየን ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ ጉድ ጀርባ ማን እንዳለ ብናስተውል ከብዙ ጥፋት በዳንን ነበር፡፡ ሰዎች መልካም በሚመስለው መንፈሳዊ ነገር እንኳ “ሰይጣንን በማክበር” ወደጌታችን ኢየሱስ ዘንድ እንዳይደርሱ ሰይጣን ከመቼውም ጊዜ በላይ እየሠራ ነው፤ ደግሞም “መንገዱ ብዙም የሚቸግር አይመስልም”፡፡ አማኙ ሁሉ ከመመርመርና ቅዱስ ቃሉን በትክክል በልበ ሰፊነት ከማጥናት ተዘልሏልና፡፡
እንኪያስ ምን እናድርግ?
     በዋናነት ለክርስቶስ ታማኝና ፍጹም ቅዱሳን የሆንን ሯጮች፣ ባርያዎች፣ ወታደሮች እንዳንኾን የሚያደርጉንን አይተናል፡፡ ዓለም፣ ኀጢአትና ዲያብሎስ፡፡ እኒህ “አካላት” አሮጌውን ሰው ተገን አድርገው ዛሬም ድረስ ይዋጉናል፤ ያጠቁናል፤ እጅጉንም ይፈትኑናል፡፡ የእግዚአብሔር ቃልም በእነዚህ እኩያን ላይ መውሰድ ያለብንን እርምጃ ሁሉ ይነግረናል፡፡ ይኸውም፦
1.     ቃወሙ፦ የቀደመው ሰው ለኃጢአት በመሸነፉና ከእግዚአብሔር ጋር ተባብሮ ክፉውን መቃወም ባለመቻሉ ምክንያት፣ ፍጹም ለጠላት ዲያብሎስ የተገዛ ሆነ፡፡ ከዚህም የተነሣ ዲያብሎስ ዓለሙን ሁሉ በክፋቱ መላው፤ (1ዮሐ.5፥19)፣ ደግሞም የዚህ ዓለም ገዥ ተባለ፤ (ዮሐ.12፥31 ፤ 14፥30)፡፡ ስለዚህም በማናቸውም መንገድ ቢሆን የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ በመቃወም ሥልጣኑን ማቆምና “ታላቅነቱን” መግለጥ ይፈልጋል፡፡
     “በመጠን ኑሩ ንቁም፥ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና፤ በዓለም ያሉት ወንድሞቻችሁ ያን መከራ በሙሉ እንዲቀበሉ እያወቃችሁ በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት” (1ጴጥ.5፥8-9) እንዲል፣ ቅዱስ ጴጥሮስ ጌታ በተያዘባት ሐሙስ ማታ የሆነበትን በትክክል ያስተዋለና ያሰላሰለ ይመስላል፡፡ የዚያን ማታ ጌታችን ኢየሱስ ለሦስት ዓመታት ያስተማረውንና በመጨረሻዎቹ ቀናት የተናገራቸውን ብርቱ የመከራ ቃላት በቸልተኝነት ዘንግቷቸው ነበር፤ ንቁ ባለመሆንና በፍርሃት ውስጥ የከተተውን ባላጋራ ባለመቃወም ምክንያት፣ በቀረበለት ፈተና ሁሉ ወድቆ ነበር፡፡ ክፉውን መቃወም አለመቻሉ የወደደውንና ለክብር የለየውን ጌታ ሽምጥጥ አድርጎ ለመካድ አበቃው፡፡
   ሰይጣንን መቃወም፣ በእግዚአብሔር ቃል ላይ ፍጹም መቆምን፤ በዚያ በቆምንበት የቅዱስ ቃሉ መሠረትነት ላይም ፈጽሞ አለመናወጥን፣ መጽናትን፣ ፈቀቅ ላለማለትም መወሰንና መጨከንን ያመለክታል፡፡ ለዚህ ደግሞ በእግዚአብሔር ፍጹም መታመንና በእርሱ ብቻ መመካት ያስፈልጋል፡፡ ሰይጣን እንደጴጥሮስ ሰይፍ ገዝተን የማልኮስን ጆሮ በመቁረጥ(ማቴ.26፥51) በራሳችን እንድንመካና እንድንቆም ይፈልጋል፤ ጌታችን ግን፣ “በእኔ ማለት በሥጋዬ በጎ ነገር እንዳይኖር አውቃለሁና፤ ፈቃድ አለኝና መልካሙን ግን ማድረግ የለኝም” እንዲል፣ ከራሳችን የሆነ ብቃትና የበጎነት አቅም ስለሌለን፣  በራሳችን አንዳች እንዳናደርግና በእርሱ ብቻ እንድንታመን ይነግረናል፡፡
      በራስ መመካት፣ ራስን ማየት፣ ራስን ከፍ ከፍ ማድረግ አቅም ይነሳል፤ እግዚአብሔርን ማየትና በእርሱ መመካት ግን አቅምና ጉልበት፤ ዲያብሎስንም ድል መንሻ ታላቅ መንገድ ነው፡፡ ዛሬ ብዙ አገልጋዮች ራሳቸውን እንጂ ጌታ ኢየሱስ ማሳየት ስላልቻሉ አማኞች የረኩ እየመሰላቸው ከአገልጋይ አገልጋይ ሲንከራተቱ ይስተዋላል፡፡ ዲያብሎስንም ለመቃወም አቅም አጥተው ያገኘ ሁሉ ሲማርካቸውም፤ እረኛ እንደሌላቸው በጎችም ሲሰብራቸው እናያለን፡፡
     ቃሉ ግን፣ “እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል፤ ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ወደ እናንተም ይቀርባል፤” (ያዕ.4፥8-9) እንዲል፣ ዳዊት በእግዚአብሔር ታምኖ ጎልያድን በመቃወም እንደጣለው፣ እኛም በእግዚአብሔር ላይ ባለን እምነት በመጽናት ፍጹም ዲያብሎስን በመቃወም ልንሸሸው ይገባናል፡፡ ለእርሱ አለመገዛታችንንም ፍጹም በመቃወም ልንገልጠው ይገባል፡፡ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ማስተዋልና ጥበብን፤ ቅዱስ የሆነ ጉልበትንም ይስጠን፤ አሜን፡፡

ይቀጥላል …

2 comments: