Friday 29 May 2020

ለኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን “መከፋፈል” ጊዜው ነውን?

Please read in PDF

  ከወደ ጐጃም የተሰማው ዜና መልካም አይመስልም፤ ቅብዐቶች ከኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አንድነት በመለየት የራሳቸውን አገረ ስብከት በመመስረት፣ ጳጳሳት መሾማቸው እየተሰማ ነው። ነገር ግን ይህ ምሳሌነቱ መልካም አይመስልም። በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደ ፕሮቴስታትንት ወይም ሐድሶአውያን ተብለው የማይወገዙ፣ ቢያንስ አራት ትምህርቶች አሉ፤ ቅብዐት፣ ጸጋ፣ ዘጠኝ መለኮትና ካራ፤ እኒህ ኹለቱ የትምህርት ይትበሃሎች ለዘመናት በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ [ከተወሰኑ ግጭቶች በቀር] በአብሮነት አሉ።

 
አኹን ግን ቅብዐት ልዩነትን በመምረጥ፣ ከካራ ኦርቶዶክሳውያን ልለይ ማለቱን ሰማን። ቅብዐቶች ወጥ ትምህርት የላቸውም፤ የትምህርታቸው ጠንሳሽ በዘመነ አጼ ሱስንዮስ የነበረው ካቶሊካዊ ጳጳስ አልፎንሱ ሜንዴዝ እንደ ነበርና፣ ይህንም ትምህርት ደንቀዝ አሞኛል ብሎ በመቀመጥ፣ ለኤዎስጣቴዎስ ዘሳንኳ የቅብዐትን፣ ለቁረንጭ መናፍቅ ተክለ ሃይማኖት ደግሞ የጸጋን ትምህርት አስተምሮ፣ኹለት እሾኽ ተከልሁብሎ ከኢትዮጵያ መውጣቱን አቡነ ጎርጎርዮስ ጽፈዋል።

   
ቄስ ኮሊን ማንሰል ደግሞ፣ የቅብዓቶች ትምህርት በተለያየ ጊዜ በተለያዩ ሰዎችመጐልበቱንይጽፋሉ፤ ትምህርቶቻቸውም በቤትነት ወይም በአስተማሪዎቻቸው ስያሜ የተቀመጠ ነው፤ ልክ አርዮሳውያን ወይም ንስጥሮሳውያን እንደሚባለው፤ እኒህም ቤተ ዘኢየሱስ፣ ቤተ አካለ ክርስቶስና ቤተ ጐሹ የሚባሉ ናቸው። ትምህርቶቻቸው መስተጋባት የጀመሩት ከአጼ ፋሲል ዘመነ መንግሥት ጀምሮ ነው።

   
ዘኢየሱሳውያን፣ 2ቆሮ. 89 ማዕከል አድርገው፣ ቃል ሥጋን በተዋሐደ ጊዜ የባሕርይ ክብሩን አጣ፣ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ ቅብዐት ወደ ቀደመ ክብሩ ተመልሶ የባሕርይ ልጅ ኾነ ሲሉ፣ አካለ ክርስቶሳውያን ደግሞ፣ ሥጋ በተዋሕዶ አንድ አካል ኾነ እንጂ፣ የአምላክነትን ክብር አላገኘም፤ በማኅፀን በመንፈስ ቅዱስ ሲቀባ ግን ክብርን አገኘ ወይም ክብር ተላለፈለት፤ በዚህም ቅብዐት የባሕርይ ልጅ ወይም የባሕርይ አምላክ ኾነ ሲሉ፣ ጐሹውያን ደግሞ፣ በተዋሕዶም በቅብዐትም ከብሮአል እንጂ፣ በቅብዐት ብቻ አልከበረም፤ ምክንያቱም ያለ ተዋሕዶ ቅብዓት ብቻውን አያከብርም፤ ተዋሕዶም ያለ ቅብዓት ብቻውን አያከብርም፤ ስለዚህም በቅብዐትና በተዋሕዶ በአንድነት የባሕርይ አምላክ ኾነ በማለት ያስተምራሉ።

የቤተ ዘኢየሱሳውያን ትምህርት ውላጤና ሚጠት ገንኖ እንመለከታለን፤ ነገር ግን ክርስቶስ ፍጹም ሰውና ፍጹም አምላክ ነው እንጂ መለወጥና መመለስ የለበትም፤ ክብሩንና ጥቅሙን በፈቃዱ እኛን ለማዳን ሲል ተወ እንላለን እንጂ፣ አጣ ወይም ለቀቀ አንልም፤ አካለ ክርስቶሳውያን ደግሞ፣ የክርስቶስን መሲሐዊ ክብርና ሥልጣን፣ ለሥጋ ብቻ ይሰጣሉ፤ በዚህም ፍጹም አምላክነቱን ይጥላሉ፤ ሦስተኛዎቹም በተመሳሳይ መንገድ ውላጤን ወይም መለወጥን ይሰብካሉ፤ በሦስቱም አስተምህሮ ውስጥ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን ገንዘብ ያደረገው በቅብዐት እንጂ በባሕርይው አምላክ እንደ ኾነ አያስተምሩም።

 
ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ያሉ አስተምኅሮዎችን፣ በጉያዋ ይዛ ለዘመናት አብራ ቆይታለች፤ እንደ ቅዱስ ቃሉ የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነትና ፍጹም ቤዛነት የሚቀበሉትን አሳድዳ፣ እኒህን በጉያዋ መያዝዋ ይደንቃል፤ ነገር ግን እንደ ቀደመው አኹንም፣ ተሐድሶ እያለች ብዙዎችን እንዳሳደደችውና በውግዘት (በርግጥም አንዳንዶች መወገዝ እንደ ነበረባቸው በግሌ ባምንም) እንደ ለየችው ብትደግም ኪሳራና ጥፋትዋ ሊያመዝን ይችላል።

ስለዚህም ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ሆይ!

1.      በስክነት፣ በልበ ሰፊነት በመወያየት ማድመጥ እንድትጀምሪ፣
2.     ከዚህ ቀደም ወንጌል የጨበጡትን ፈጥነሽ እንዳወግዝሽ አኹንም ፈጥኖ ከማውገዝ ብትዘገዪ፣ ብትመክሪ፣ ብታቀርቢ፣ ዝቅ ብለሽ መነጋገርን ብትወድጂ፣
3.     ለመጽሐፍ ቅዱሳዊ ተሐድሶም በሮችሽን ጠርቅመሽ ከመዝጋት፣ በሮችሽን ብትከፍቺና ውስጥሽን ብትፈትሺ መልካም ነው፤ ምክንያቱም በብሔር የተደራጁ አካላት ጥያቄ ማቅረባቸው ትኩሳቱ ሳይግል ይህ መነሣቱ፣ በተደጋጋሚ የልጆችሽ ፍልሰት መብዛቱ፣ በውስጥ ብዙ ያልተስተካከሉ እንከኖች ለመኖራቸው ምልክት ነው፣
4.     አኹንም ዙርያሽን የከበቡትና እየመሩ ያሉ ካራውያን ወይም የአውጣኪን ትምህርት ተከታይ ልጆችሽ፣ ራሳቸውን ቢመረምሩና በቃለ እግዚአብሔር ራሳቸውን ለመፈተሽ ቢዘጋጁ፣ በረከትና ሕይወት ይኾንላቸዋል፤ ይኾንልሻልም፡፡ አልያ ግን ልጆችሽን ከመበላላት፤ ከመጠፋፋት፤ ከመረጋገም ከቶ መከልከል አትችይም፡፡

   ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ሆይ በመስቀሉ ርኅራኄ እንለምንሻለን፤  በእውነት ላይ አንዳች ሳትጨምሪ፣ ለቅዱስ ቃሉ በትክክል መታዘዝና መሸነፍ እንድትችል ጸጋው ይብዛልሽ፤ አሜን።


No comments:

Post a Comment