Wednesday 27 May 2020

ዕርገቱ - የቤዝወታችን ፍጻሜና ተስፋችን!

Please read in PDF
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ማረጉ ባለፈው ሳምንት በምዕራባውያን አብያተ ክርስቲያናት፤ በዚህ ሳምንት ደግሞ በምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ዛሬ ይታሰባል፤ ዕርገቱን አንዱ ወንጌላዊ፣ በመንፈስ ቅዱስ መነዳት ኹለት ጊዜ ዘግቦልናል፤ ሉቃስ ወንጌላዊው፤ (ሉቃ. 2450-52 ሐዋ. 16: 11) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱም ስለ ዕርገቱ አስቀድሞ ተናግሮአል፤ (ዮሐ. 142: 13 2017) ነቢያትም ትንቢት ተናግረውለታል፤ (ዳን. 79-13)




ሞትና ሲዖልን በሞቱ የሻረው ጌታችን ኢየሱስ ሲያርግ ለደቀ መዛሙርቱ፣ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ።” (ማቴ. 2818) በማለቱ፣ በሥልጣኑ ኹሉን ወደሚገዛበት በክብር ዐረገ። ዕርገቱ ባለ ብዙ ምስክር ነው፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሰማያት ከማረጉ በፊት፣ መሰቀሉና ከሙታን መካከል መነሣቱ የታመነ  ነው፤ ክርስቶስ ለእኛ በመሰቀሉ በሥጋው መሥዋዕታችን ኾኖልናል፤ (ቆላ. 121-22 ዕብ.1019-20 1ጴጥ. 224) በብሉይ ኪዳን ሊቀ ካህናቱ የሚያቀርበው ልዩ ሥርዐት አለ፤ ደምን ስለ ራሱና ስለ ሕዝቡ በመያዝ፣ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ ይገባል፤ በታቦቱ ላይ ባለውና የተናተፉ፣ ክንፎቻቸው የተጋጠሙ ኪሩቤል ባሉበት የስርየት መክደኛ ላይ ደምን በመርጨት መሥዋዕትን ለእግዚአብሔር ያቀርባል፤ (ዘሌ. 1611-19 ዕብ. 97) መሥዋዕቱ ስሙርና ውዱድ ከኾነ፣ ሊቀ ካህናቱ በሕይወት ወጥቶ በሕዝቡ ፊት በአደባባዩ ይታያል።

ሊቀ ካህናት ክርስቶስ ግን በተለየ መንገድ፣ “... በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን፥ የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ ... ” (ዕብ. 911-12) እንዲል፣ የተዋጀንበት ነውርና ዕድፍ የሌለበት ደሙን በእግዚአብሔር ፊት በማቅረብ፣ በሰማያዊው ድንኳን ቤዛነቱን ፈጸመ፤ (1ጴጥ. 118-19)

ክርስቶስ ለእኛ የፈጸመው ቤዛነት፣ አብ የረካበት ቤዛነት ነው። ለዚህም የከፈለው ቤዛነት፣ በሰማይም በምድርም አቻ የሌለውና ለአይሁድም ለአሕዛብም የሚበቃ፤ የተትረፈረፈ ቤዛነት ነው። ለመላለሙ ሌላ መሥዋዕት፤ ሌላ ቤዛ እስከማያስፈልግ ድረስ ክርስቶስ ቤዛነታችንን ፈጽሞ፣ ወደ ሰማያት በፍጹም ጌትነትና ክብር ገባ፤ ዐረገ። አብም በፍጹም ደስታ ተቀበለው! ልክ በብሉይ ኪዳን የነበረው ሊቀ ካህናት፣ መሥዋዕቱ በሠመረለትና በእግዚአብሔር በፊት ተቀባይነት ባገኘ ጊዜ ወደ አደባባዩ ወጥቶ እንደሚታየው እንዲሁ፣ ክርስቶስም ቤዛነቱን ፈጽሞ፣ በሰማያዊው ድንኳን አደባባይ ይታይ ዘንድ በክብር ዐረገ።

እኛን ተክቶ ስለ መዳናችን የፈጸመው የቤዝወቱ ሥራ፣ እስከ ኹለተኛ መምጣቱ ድረስ የትኛውም ኀጢአተኛ አምኖ በመጣ ጊዜ ሳይታክት፤ ሳይዝል፤ ሳይሰለች፤ ሳይታዘብ ዘወትር ይቀበላል። ለኃጢአተኛ የክርስቶስ ቤዝወት በቂ ነውና፣ "ዘወትር በድካም ያለን" ኀጢአተኞች እንኳ፣ በዚህ እጅግ ደስ ሊለን ይገባል። ዕርገቱም ደግሞ፣ በሰማያዊው ድንኳን መሥዋዕቱ በእግዚአብሔር ፊት መቅረቡንና ቤዛነት መፈጸሙን ያበሥራልና፣ ለታመኑበት በሰማይም በምድርም የኢየሱስ ቤዛነት ያስመካል (1ቆሮ. 130-31)

የክርስቶስ ዕርገት ቤዛነታችን መፈጸሙን የሚያበስር የምሥራች ብቻ አይደለም፤ ታላቅ ተስፋችንም ነው፤ ያረገው ጌታ ይመለሳል፤ (ሐዋ. 111) ታላቁ ተስፋችን ከክርስቶስ ኹለተኛ መምጣት ጋር የተዛመደ ነው፤ አማኞች ኹላችን ከክርስቶስ ጋር ሞተን፤ ከእርሱ ጋር ተነሥተናል፤ (ኤፌ. 26-7) ደግሞም ዳግመኛ ይመጣል፤ ለዘለዓለም ከእርሱ ጋር እንድንኖር ይወስደናል፤ ያረገው ጌታ ወደ ደስታው እንገባ ዘንድ ወደ ሰማይ ይነጥቀናል፤ በዚያም ደስታችን ፍጹምና ዘላለማዊ ይኾናል።

እርሱ ወደ ሰማይ እንደ ወጣ፣ እኛም ከእርሱ ጋር እንወጣለን ወይም በእርሱ እንነጠቃለን። (ዮሐ.1724 1ቆሮ. 1551-52 1ተሰ. 415-17) ያረገው ጌታ በሰማይና በምድር ሥልጣን አለው፤ ሉዐላዊ እና ኹሉን ተቆጣጣሪም ነው፤ ኮቪድ 19 ኮሮና፣ ለብዙዎቻችን አስጨናቂ ነው፤ ነገር ግን መላለሙን በመግቦቱ የያዘ ባለሥልጣን አለ። ስለዚህም አሁን ያለንበትም፤ ዘላለማችንም የሚገደው ጌታ አለን። ሊቀ ካህናቱ በሰማያት ቤዛነቱን ፈጽሞ ይታይልናልና፣ ደስ ይበለን፤ ሊወስደንም ይመጣል፤ ደስ ይበለን፤ በዚህ ጌታ በደስታ ተጽናኑ፤ ረክታችሁም ቅሩ፤ አሜን።


No comments:

Post a Comment