Wednesday 13 May 2020

የሐሰት መምህራን የማይነኳቸው ርእሶች (ክፍል ፫)

Please read in PDf

2.  ንስሐ፦ የስህተት መምህራን የማይነኩትና የማይደፍሩት ሌላው ርእስ ቢኖር ንስሐ ነው። ከእግዚአብሔር ለተለየው ዓለምም፤ በቤቱ ኖሮ ለሚበድለው አማኝም ንስሐ ዕለታዊ ተግባር ነው። በብሉይ ኪዳን ዐሳብ የአንድን ሰው ከኀጢአት ወደ እግዚአብሔር መመለስን የሚያመለክት ሲኾን (ኢሳ. 9፥13፤ ኤር. 4፥22፤ 5፥3፤ 26፥3፤ ሆሴ. 5፥4፤ 7፥10)፤ የአዲስ ኪዳን ምንባባት ደግሞ ኹለንተናዊ መመለስን የሚያመለክቱ ናቸው፤ ለምሳሌም፦ የነነዌ ሰዎች ኹለንተናዊ በኾነ ዝንባሌአቸው ንስሐ መግባታቸውን፣ “በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና፥” በማለት ጌታ ኢየሱስ ተናገረ (ዮና. 3፥5-9፤ ማቴ. 12፥41)፣ ነነዌ ዮናስን ከተቀበለች፣ አይሁድም ከዮናስ የሚበልጠውን ጌታ አምነው ሊቀበሉ ይገባ ነበርና።




   ሌላው የአዲስ ኪዳን ትርጉም፣ ፍጹም የኾነ ተግባራዊ ምላሽ መስጠት ነው፤ ጌታ ኢየሱስ ላስተማረው ትምህርት፣ አይሁድ ተግባራዊ ምላሽ ባለመስጠት ደነዘዙ፤ ፈዘዙ (ማቴ. 13፥15)፤ አማኙም በተግባራዊ ምላሹ ወደ እውነተኛ የክርስትና ሕይወት ያቀናል፤ የመጀመሪያቱ ቤተ ክርስቲያን አማኞች፣ የቅዱስ ጴጥሮስን ስብከት ሰምተው ተግባራዊ ምላሽ ሰጡ፤ ልባቸው ተነካ፤ ኢየሱስን ባለመቀበላቸው መጸጸታቸውንና አሁን ፍጹም ማመናቸውን አሳዩ፤ (ሐዋ. 2፥37)፤ የጠፋው ልጅም ወደ ልቡ በመመለሱና ተጸጽቶ ተግባራዊ ምላሽ በመስጠቱ ንስሐው እውነተኛ ነበር፤ (ሉቃ. 15፥17-20)።
 የስህተት መምህራን ግን ይህን እውነት አይሰብኩም፤ ለምን ንስሐን አይሰብኩም ወይም ደፍረው ለኀጢአተኞች አያውጁም? ብንል፣ መጽሐፍ ቅዱስ የሚነግረን እውነት አለ፤

·        የሚሰበስቡት ቢጤዎቻቸውን ነው፦ “ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትም የሚወሰዱትን ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ሊደርሱ ከቶ የማይችሉትን ሞኞችን ሴቶች ይማርካሉና” (2ጢሞ. 3፥6-7) እንዲል፣ በሐሰት መምህራን ዙርያ በአብዛኛው የሚያንዣብቡትና የሚከብቡት፣ የኀጢአት ክምራቸው ልክ አልባ የኾኑቱና ተምረው፤ ተምረው ወደ እውነት የማይደርሱ ወይም ተግባራዊ ምላሽ የማይሰጡ ሴቶችና ወንዶች ናቸው። እኒህ ተከታዮቻቸውን ስለ ንስሐ የሚወቅሳቸው የላቸውም፤ መምህራኖቻቸው እንደ እነርሱ እጅግ ኀጢአት የተከመረባቸው ናቸውና።

   የስህተት መምህራን ምናምንቴዎችን ማስከተል እጅግ ይወድዳሉ፤ የስህተት ንግሥት የነበረችው ኤልዛቤል፣ በናቡቴ ላይ ያደረገችውን አስተውሉ! “ሁለቱም ምናምንቴ ሰዎች ገብተው በፊቱ ተቀመጡ፤ ምናምንቴዎቹ ሰዎችም በሕዝቡ ፊት፦ ናቡቴ እግዚአብሔርንና ንጉሡን ሰድቦአል ብለው በናቡቴ ላይ መሰከሩ። የዚያን ጊዜም ከከተማ አውጥተው እስኪሞት ድረስ ወገሩት።” (1ነገ. 20፥13)። ናቡቴ ከመንገድ የተወገደው፣ በኤልዛቤል አጋፋሪ ተከታዮች ነው፤ አዎን! የሐሰተኛ መምህራን ዕድሜ የሚረዝመው በተከታዮቻቸው ድጋፍና አቅም ነው። ገማልያልም የመሰከረባቸው ሐሰተኞቹ ቴዎዳስና ይሁዳም እነርሱን መሳይ አያሌ ተከታዮች ነበራቸው፤ ነገር ግን በፍጻሜያቸው እንደ ምናምን መኾናቸውንም ይነገረናል፤ (ሐዋ. 5፥36-37)።

   የሐሰት መምህራንም ተከታዮቻቸውም ምናምኖች ናቸው፤ ምክንያቱም የዐሳባቸውንና የድርጊታቸውን ምናምንነት በድፍረት የሚናገር፤ የንስሐ ድምጽ የሚያሰማ በመካከላቸው የለምና። ስለዚህም የትኛውም የስህተት መምህር ንስሐን ፈጽሞ አያስተምርም! ነገር ግን እውነተኞቹ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት፣ “በስሙም ንስሐና የኃጢአት ስርየት ከኢየሩሳሌም ጀምሮ በአሕዛብ ሁሉ ይሰበካል” የሚለውን ቃል ከቶውንም በዘመናቸው አይዘነጉትም፤ (ሉቃ. 24፥47)።

·        ግመልን የሚውጡ ናቸውና፦ ጌታችን ኢየሱስ ግብዞቹን ፈሪሳውያንን በጽኑ በወቀሰበት ክፍሉ እንዲህ አለ፦ “እናንተ ዕውሮች መሪዎች፥ ትንኝን የምታጠሩ ግመልንም የምትውጡ።” (ማቴ. 23፥24) የስህተት መምህራን ጥቃቅን ሕጎችን በመጠበቅ የሚተካከላቸው የለም፤ ነገር ግን ዋናውን ነገር ሲሽሩና ሲድሱ እናያቸዋለን፤ ለምሳሌ፦ ኀይሉ ዮሐንስ ትሁትና ገንዘብን በመስጠት ቸር እንደ ኾነ በብዙዎች ይመሰከርለታል፤ ዋናውን የክርስትና ትምህርት በመካድ ኑፋቄ ዘሪ መኾኑን መናገር የሚፈልግ ግን ጥቂቱ ነው። [ሐዋርያ?] ዘላለም ጌታቸውና ሌሎችም ተመሳሳይ ጠባይ አላቸው። ኢየሱስን ፍጹም ይክዳሉ፤ ክደው ያስተምራሉ፤ አንድ ኢአማኒ ሊያደርገው የሚችለውን በጐ ተግባር ደግሞ “አብዝተው” ያደርጋሉ።

   ግመልን ይውጣሉና ትንኝን እንዴት ማጥራት ይቻላቸዋል?! ኹለትና ከዚያ በላይ ያገቡትን ሴቶችና ወንዶችን፣ አንዳችም መናገር የማይሹት፣ እነርሱ ከዚያ በባሰ ነውር ስለተያዙ አልያም ቢቃወሙ ደጋፊና የሚረዳቸውን ስለሚያጡ ነው። ኀጢአት በባሕርይው ራሱን እጅግ መሸሸግ ይወዳል፤ ራሳቸውን ጻድቅ አድርገው ነገር ግን በፍጹም ስህተት ውስጥ የዘፈቁትን ሲያገኝ ደግሞ፣ በሚገባ በእነርሱ በሙሉ ኀይሉ ይሠራል። ወዳጆች ሆይ፤ እንዲህ ካለ ክፉ ወጥመድ መውጣትና ማምለጥ ይኹንላችሁ፤ አሜን።

-       ንስሐ ራስን ለእግዚአብሔር ማሳየት ነው፣
-       ንስሐ በትክክል ወደ እግዚአብሔር መመለስ ነው፣
-       ንስሐ ወደ ትክክለኛ ጌታና እረኛ ፊትን ዘወር ማድረግ ነው፣
-       በንስሐ ኹሉን ትቶ፣ አንዱን ጌታ ብቻ ማየትን ሐሰተኛ መምህራን አይወዱም!

  ለእውነተኛ አገልጋዮች የንስሐ አዋጅ የዘወትርና የማያቋርጥ ነው፤ አዋጁም ራስንም ጭምር የሚያካትት ነውና ለራሳችን ሳናደርገው ለሌላው ብንናገረው ከግብዝነት የዘለለ ትርጉም የለውም፣ ከስህተት መምህራን ጠባይ እንራቅ፤ እንሽሽም!
 ይቀጥላል …

1 comment: