Sunday 24 May 2020

“እመቤቴ ቤዛ ብትኾን ምንድር ነው?” (የማያልቀው የዶ/ር ዘበነ ለማ ተረት)

Please read in PDF

   ዶ/ር ዘበነ ለማ፣ በአገረ አሜሪካ የሬዲዮ ፕሮግራም አለው፤ ከጠያቂዎች ለሚመጣለት ጥያቄ ኹሉ መልስ የሚመልስበት። ትኩረቴን ከሳበውና ለዛሬ እንዳካፍላችሁ የፈለግኹት፣ በአንዲት እህት አማካይነት፣ በቤዛነት ዙሪያ የተጠየቀውንና የመለሰውን መልስ በማንሣት ይኾናል፤ የተዘጋጀው “የመናፍቃን ምላሽና የዶ/ር ቀሲስ መምህር ዘበነ ለማ መልስ ክፍል 6” በሚል ርእስ ነው። ለቀረበለት ጥያቄ ዘበነ የመለሰው፣ ጭምቀ ዐሳብ በአጭሩ እንዲህ የሚል ነው፦





  “ … ቤዛ ማለት ስቅለት ማለት አይደለም። ቤዛ ማለት ለአንድ ሰው ዋጋ ከፍሎ ወይም ደግሞ ለአንድ ሰው በአንድ ነገር ላይ ደጋፊ መሆን ማለት ነው፣ ቤዛ መሆን። እከሌ ቤዛ ሆነው ከተባለ፣ ደጋፊ ሆነው ማለት ነው። ሌላ ነገር አይደለም ስቅለት ስቅለት ነው አይገናኝም[የክርስቶስ]።  … ቤዛ ሆነልን ማለት እኛ መሰቀል ሲገባን፣ ለምሳሌ ቤዛ ይስሐቅ ይባላል። ኢየሱስ ክርስቶስ ዘፍጥረት 22 ላይ ይስሐቅ ሊሰቀል ነበር አይደለም፣ ሊሞት ነበረ። መሥዋዕት ሊሆን ነበረ፤ ግን ለአብርሃም ቤዛ ይስሐቅ ሆነ። በጉ ራሱ ይስሐቅ ዳነ፤ ሚስጥሩ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። … እመቤቴ ታዲያ ቤዛ ብትኾን ምንድር ነው በጉ ከኾነ? …”[i] ይላል ዘበነ እያጣደፈ የመለሰው መልስ።
ቤዛነት ምንድር ነው?

ቤዛ” የሚለው ቃል፣ ከግዕዝ ቋንቋ የተወሰደ ሲኾን፣ ሰውን ከባርነት ነጻ ለማውጣት የሚከፈል ዋጋ ወይም አንድን  የተያዘን ወይም የተወሰደን ነገር ለማስመለስ የሚከፈል ዋጋን፣ ካሳን አመልካች ነው። ቤዛን የመክፈል ሥራ ደግሞ፣ ቤዛነት ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ ተጠቅሶአል። ቤዛነት፣ በበደለኛው ሰው የተወሰነውን ትክክለኛ ፍርድ ተመጣጣኙን ዋጋ ከፍሎ ነፃ ማውጣት ነው። ስለዚህም ቤዛ ማለት፣ “በቁሙ ዋጋ፣ ካሳ፣ ለውጥ፣ ምትክ፣ ዋቢ፣ ዋስ፣ መድን፣ ተያዥ … የመሰለው ኹሉ። [በደቂቅ አገባብ] ደግሞ፣ ስለ፣ ፈንታ፣ ምክንያት”[ii] በማለት አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ያብራሩታል። ከዚህ በመነሣት፦

1.      በብሉይ ኪዳን ሰዎች እንሰሳትን ከመታረድ፣ በድኽነት ምክንያት የተሸጠውን ርስት መሬታቸውን ወይም ቤታቸውን ወይም በባርነት የተያዘባቸውን ሰው ለማስለቀቅ ተመጣጣኙን ዋጋ ይከፍሉና ይቤዡ ነበር፤ (ዘጸ. 13፥13፤ ዘሌ. 25፥24-34፤ ሩት 4፥4፤ ኤር. 32፥6)፣ ለዚህም በምሳሌነት፣ እግዚአብሔር ሕዝቡን ከግብጽና ከባቢሎን መቤዠቱን ይናገራል፤ (2ሳሙ. 7፥23፤ ነህ. 1፥10)፣

2.    በአዲስ ኪዳን ግን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያምኑበት ኹሉ፣ ቤዛና መድኀኒት ኾነላቸው፤ (ማር. 10፥45፤ ኤፌ. 1፥7፤ 1ጢሞ. 2፥5፤ ዕብ. 9፥12)፤ ይህንም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነትን ከሙታን ትንሣኤ በኋላ አረጋገጠው፤ (ሮሜ 8፥23፤ ኤፌ. 4፥30)።[iii]
ጌታችን ኢየሱስ ለምን ቤዛ ኾነን?
1.      ሰው በደለኛ ስለኾነ፦ ሰው በደለኛና ኀጢአተኛ ስለኾነ፣ ለራሱ ቤዛ መኾን አይችልም። ቤዛ ለመኾን ከሚቤዥበት ነገር፣ ተቤዢው ነጻ መኾን መቻል አለበት። ከዚህ አንጻር በደል አልባ የኾነ ሰው፤ ለሰው እጅግ ያስፈልግ ነበር፤ ምክንያቱም ኹሉም የአዳም ዘር፣ ከኀጢአትና ከበደል በታች ተከስሶ ተዘግቶበት ነበር፤ (ሮሜ 3፥9)። ስለዚህም ክርስቶስ ኢየሱስ፣ “ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።” (ቈላ. 1፥13-14)።

    በኀጢአት ምክንያት የሕግ እርግማን ያገኘንን፣ እርሱ የሞትን መውጊያ ሰብሮ፣ የሲዖልን ኃይል ድል ነሥቶ ተቤዠን፤ ዋጀን፤ ዐርነትን ሰጠን። የሕጉንም እርግማን ከእኛ ላይ አስወገደው፤ (1ቆሮ. 15፥56፤ ገላ. 3፥10)። ስለዚህም ከእርሱ ተነሣ ቅዱሳንና አለነውር ኾንን።

2.    ክርስቶስ አንዳች በደል ስለሌለበት ስለ በደላችን ብቸኛ ቤዛ ኾነልን። ራሱም ሲናገር፣ “የሰው ልጅ ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ” እንደ መጣ ተናገረ፤ (ማቴ. 20፥28፤ ማር. 10፥45)፤ እኛም በክርስቶስ በኩል በኾነው ቤዛነት፣ የበደላችንን ስርየት አገኘን፤ ከሕግ እርግማንም ዋጀን፤ (ሮሜ 3፥24፤ ኤፌ. 1፥7፤ ገላ. 3፥13)።

3.    ከዚህም የተነሳ ለዋጀን ጌታ ብቻ እንኖርለታለን፤ ቤዛና ዋጆ በዐሳብ ደረጃ ተዛማጅ ትርጉም አላቸው፤ በቤዛነት ክርስቶስ የራሱ ገንዘቦች እንዳደረገን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ በማለት ይመሰክራል፤ “በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።”፣ “በዋጋ ተገዝታችኋል፤ የሰው ባሪያዎች አትሁኑ።” (1ቆሮ. 6፥16፤ 7፥23)።

  የዳንነውና ክርስቲያን የተባልነው ወይም የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን የተጠራነው፣ ክርስቶስ ያለ አንዳች በደልና ነውር ቤዛ ኾኖ በደሙ፣ የኀጢአታችንን ዕዳ ኹሉ ስለ ከፈለልን ነው። በዋጋ የገዛን እርሱ ነውና የእርሱ ብቻ ነን! ወደፊት የምንኖረውና የምንኖርለት በክርስቶስ ለክርስቶስ ብቻ ነው። ዐርነት የወጣንበት እውነት (ዮሐ. 8፥32)፣ ጸድቀን ጻድቃን የተባልንበት ጽድቃችን ክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው፤ (1ቆሮ. 1፥30-31)።

    ዘበነ፣ ቤዛነትን ደጋፊነት ብሎ መተርጎሙ ፍጹም ስህተት ነው፤ ፍጹም በኾነ መንገድ፣ አንድን ነገር የራስ ገንዘብ ማድረግ ነው እንጂ። ልክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ ዋጅቶ፣ ገዝቶ፣ ተቤዥቶ የራሱ ገንዘቦችና ውድ ዕቃዎቹ እንዳደረገን እንዲህ ነው። እርሱ የደገፈን ብቻ አይደለም፣ “ሁሉን በሥልጣኑ ቃል የደገፈው ክርስቶስ ኢየሱስ፥ ኃጢአታችንን ደግሞ በራሱ አንጽቶአል” (ዕብ. 1፥3)። 

   ቤዛነት፣ አምላክነትን ብቻ ያይደለ፣ ፍጹም አምላክና ፍጹም ሰው መኾንን ይሻል። በፍጹም አምላክነቱ ዓለማትን የደገፈው ያው ጌታ፣ ከቅድስት ድንግል ተወልዶ በፍጹም ሰውነቱ አድኖናል፤ ለኀጢአታችን በደሙ ስርየት ኾኖአል፤ “መንግሥትም ለአምላኩና ለአባቱም ካህናት እንድንሆን አድርጎአልና፥ ለእርሱ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ክብርና ኃይል ይሁን፤ አሜን።” (ራእ. 1፥6)።

   ቅድስት ማርያም፣ ኀጢአትን በተመለከተ ለሰው ልጆች ኹሉ ቤዛ መባል ወይም መኾን አትችልም፤ ምክንያቱም ቅድስት ማርያም ቤዛዋን ወለደች እንጂ፣ በራስዋ ቤዛ ለመኾን ፍጹም አምላክነትና ፍጹም ሰውነት ያሻታል፤ ዘበነ፣ ቅድስት ማርያም እንዲህ ናት እያለ ከኾነ፣ ቅድስት ማርያም ለእርሱ አራተኛ “ሥላሴ” ናት ማለት ነው። ነገር ግን ለኀጢአታችን ቤዛችን ናት ማለትም፤ “እርሷ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ናት” የማለት ያህል፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ የወጣ የተገለጠ ኑፋቄ ነው። 

   ዘበነ፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ በተቃራኒ ቆሞ፣ ቤዛነት ከስቅለት ጋር አይገናኝም ቢልም፣ መጽሐፍ ቅዱስ ግን በቀጥታ ከስቅለቱና ከደሙ ጋር በማያያዝ እንዲህ ይላል፦ “በእርሱም እንደ እግዚአብሔር ጸጋ ባለጠግነት መጠን፣ በደሙ በተደረገ ቤዛነት፣ የኀጢአትን ይቅርታ አገኘን” (ኤፌ. 1፥7) ይላል። ዘበነ ሆይ! “በደሙ የተደረገ ቤዛነት” የተባለው የመስቀሉ ሥራ አይደለምን?!

    ቤዛነት፣ ክርስቶስ በሰውነቱ ወይም በሥጋ ሞቱ የከፈለልን ፍጹም የመስቀሉ ሥራ ነው፤ ይህም ብቃት ያለውና አንዳች ተጨማሪ ነገር የማያሻው ነው፤ የትኛውም ኀጢአተኛ ይህን በማመን ይድናል። ይህ መንገድ ኹለተኛ ሌላ አማራጭ የለውም፤ የዳንበትና የምንድንበት የቤዛነት ሥራ አንድና አንድ ብቻ ነው። ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ እንዲህ ብለዋል፤ 

  “አዳም መለኮታዊ ሕግን በመተላለፉ፣ በደል በመፈጸሙ የሞት ቅጣት ተፈርዶበታል፤ አዳም ከዚህ ዘላለማዊ ቅጣት ለመዳን የሚችለው በፍርድ መንገድ እንጂ በሌላ ሁኔታ መዳን አይችልም። ቅጣቱ በፍርድ እንደ ሆነ መዳኑም በፍርድ ይፈጸማል። ስለዚህ ነው ጌታ ሥጋ ለብሶ ማለት ሰው ሆኖ የአዳምን የሞት ፍርድ በራሱ ሰውነት ተቀብሎ ያዳነው፤ “ወአድኃነነ በፍትሕ ጽድቅ ወርትዕ” ተብሎ እንደ ተጻፈው መዳናችን በፍርድ እንደሆነ እናስተውል (መቅድመ ወንጌል)። ፍርድም የተፈጸመው በመስቀል ላይ ነው። እንግዲህ በመስቀል የመዳናችን ነገር አማራጭ የሌለው በእግዚአብሔር የተመረጠ ብቸኛ የጽድቅና የፍትሕ የርትዕ መንገድ እንደሆነ እናምናለን።
ከመስቀል ሌላ የመዳን አማራጭ አለ ብሎ ማሰብ ከእውነትና ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ መሆንን ያመለክታል። መስቀል አያስፈልገንም ከነ ኃጢአታችን ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ እንችላለን ማለት ዘበት ነው፤ ሐሰት ነው፤ ከእግዚአብሔር ተለይቶ መቅረት ካልሆነ በስተቀር የእግዚአብሔር የቅድስና መለኮታዊ ባህርዩ የሚያቃጥል እሳት ስለሆነ በክርስቶስ መስቀል በኩል ካልሆነ ማንም ሊድንና ወደ እግዚአብሔር ሊቀርብ አይችልም። … ደም ካልፈሰሰ የኀጢአት ሥርየት የለም (ዕብ. 9፥22)። የኀጢአት ሥርየት ከሌለ ሰው ከእግዚአብሔር አይታረቅም።[iv]
ማጠቃለያ

   ዘበነ፣ “የመናፍቃን ምላሽና የዶ/ር ቀሲስ መምህር ዘበነ ለማ መልስ ክፍል 6” ተብሎ የመለሳቸው መልሶች ብዙዎቹ፣ እጅግ የሚያሳፍሩ ናቸው፤ ከመጽሐፍ ቅዱስ በተቃራኒም የተመለሱ ናቸው፤ እንዲያውም በግልጥ ቃልም፣ የያዝነው መጽሐፍ ቅዱስ እንኳ ሙሉ አለመኾኑን ጭምር፣ በድፍረት ሲናገር ይሰማል። ነገር ግን እርሱ እንዳለውም አይደለም። ከዚያ መዝነን ያየነው የቤዛነት ትምህርት እንኳ፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ በተቃራኒ ያስተማረ ለመኾኑ፣ ቅዱሳት መጻሕፍን የመረመረ አስተዋይ ደቀ መዝሙር ይረዳዋል። እናም ቤዛነት በክርስቶስ ብቻ የተከናወነ፣ የሰው ልጆች ኹሉ የዳኑበት ታላቅ፣ ዘላለማዊና ሕያው ሥራ ነው። ኀጢአተኞች ኹሉ በዚህ ጽድቅና ቤዛነት በመታመን ቢመጡ፣ “ከአባቶቻቸው ከወረሱት ከከንቱ ኑሮአቸው” (1ጴጥ. 1፥18-19)፣ ከኀጢአት ባርነት (ዮሐ. 8፥34)፣ ከጨለማ ሥልጣን (ቈላ. 1፥13)፣ ከሞት ፍርሃት (ዕብ. 2፥14) ነጻ በመውጣት ይድናሉ፤ ቤዛነቱ ለመላለሙ፤ መዳኑ ደግሞ ለሚያምኑበት ነውና። እንዲህ ያዳነን ጌታ ይባረክ፤ አሜን።

   ዘበነ ሆይ፤ ከስህተትህ ትመለስ ዘንድ በክርስቶስ ፍቅር እንመክርሃለን፤ የመንፈስ ቅዱስ ወቀሳም እንዲያገኝህ እንማልዳለን፤ አሜን። “እግዚአብሔር ሙላቱ ሁሉ በእርሱ እንዲኖር፥ በእርሱም በኩል በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ሁሉ ለራሱ እንዲያስታርቅ ፈቅዶአልና።” (ቈላ. 1፥19-20) አሜን።
ጸጋና ሰላም በክርስቶስ ኢየሱስ ይብዛላችሁ፤ አሜን።


[i] የሬዲዮ ቃለ ምልልስ።
[ii] ኪዳነ ወልድ ክፍሌ(አለቃ)፤ ገጽ 266
[iii] የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት፤ ገጽ 116
[iv] ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ፤ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት፤ 1996 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ አሳታሚ ማኅበረ ቅዱሳን፤ ገጽ 116





10 comments:

  1. ደረጃህን ጠብቅ

    ReplyDelete
  2. ዘበነ፣ ቅድስት ማርያም እንዲህ ናት እያለ ከኾነ፣ ቅድስት ማርያም ለእርሱ አራተኛ “ሥላሴ” ናት ማለት ነው። ነገር ግን ለኀጢአታችን ቤዛችን ናት ማለትም፤ “እርሷ ፍጹም ሰው፤ ፍጹም አምላክ ናት” የማለት ያህል፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ የወጣ የተገለጠ ኑፋቄ ነው። ewnetihn new

    ReplyDelete
  3. አንተ የገማህ አርፈህ አትቀመጥም የሉተር ዲቃላ ዝም ብለህ ስለ ምንፍቅናህ ለመን አፅም በማያገባህ ከምትገባ ከብት

    ReplyDelete
  4. ያንተን መናፍቅነት አንሰማም

    ReplyDelete
  5. አሁን አቤነዘር ሰነፍ ሰባኪ መሆኑን እየተረዳሁ ጹሐፋም ፋይዳ ያለው በአመክንዩ የዳበረ አለመሆኑን እየተረዳሁ ነው :: የሚያነሳው ክርክር ጀማሪዎችን ለማወናበድ ለእውነት ሳይሆን አጃቢና አድናቂ ለመሰብሰብ የሚደረግ ከንቱ ልፊያ እንጂ ከአቻዎቹ ጋር የሚደረግ የንጽጽር ክርክር አይደለም ይህን ያልኩት አቤነዘር የሚነሳቸው ምጉቶች ጀማሪዎችን የሚስደነግጥ ቤተክርስቲያኒቱን የሚያውቁትን የዚህ ልጅ እውቀቱ እንዲህ ነው መሰረታዊ ኮርሶችን እንካን አልተማረም እንዴ አንድም ቀን በሰንበት ትምህርት ቤት ደጅ አላለፈም የሚስብል ነው ፡፡

    ReplyDelete
  6. የአፄ ዘራያእቆብ ተንኮልና ተከታዮች ሃሳብ ዉጤት ነዉ :: አንተ ግን ተባረክ !!!

    ReplyDelete
  7. አቶ..A/T...ወዳጄ ምነው ከኦርቶዶክስ ላይ አልወርድ አልክ አይምሮህ አላርፍ አለህ መሰለኝ እንዲህ እኮ ነው የበሉበት ወጪት መርገጥ መጨረሻው ይሄው ነው ለማንኛው ዝም ብለህ እንደ እርጎ ዝብ ጥልቅ አትበል በማያገባህ አትግባ ጸጥ ብለህ የራስህን ኑሮ ኑር...... ምንም ግዜ በራሱ መቆም የማይችል በማያገባው ሚገባ "ጥገኛ ትል"ብቻ ነው..!!!

    ReplyDelete
  8. ዘበነ እከ ደፋር ነው ምንም አይሸምመውም

    ReplyDelete
  9. ነገረ ተዋህዶን እስቲ ረጋ ብለህ ተማር የቤዛነት ትርጉም ይገባህ ነበር ክርስቶስ ቤዛ የሆነበት ስጋው ከሰማይ የመጣ ነው እንዴ?

    ReplyDelete
  10. ጩጬው ዶክተር ዘበነን ለመተቸት መጀመሪያ ት/ቤት ግባ ከዚያ ጓደኞችህን ተች አትንጠልጠል።

    ReplyDelete