Wednesday 8 January 2014

የኢየሱስ ደም (ክፍል - አምስት)



3-ደሙ የተዋጀንበት ዋጋችን ነው፡፡

              “በብር ወይም በወርቅ ሳይሆን፥ ነውርና እድፍ እንደሌለው እንደ
               በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ።
                   (1ጴጥ.1÷19)
      “ዋጀየሚለውን መዝገበ ቃላቱገዛ፣ካሳከፈለ (ከሞት፣ ከባርነትለማዳን)፣አዳነብሎ ይፈታዋል፤ (ኣማርኛ መዝገበ ቃላት፡፡(2001)፤ አዲስ አበባ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ማተሚያ ቤት፡፡ገጽ.426) ውጅት ማለት ቀድሞ የራስ የነበረን ንብረት በኋላ ግን ከዋናው ባለቤት ወጥቶ ወደሦስተኛ አካል የገባን ዋጋ ያለውን ሀብት የሚያስፈልገውን ሁሉ ቅጣት በመቀበልና ዕዳውን በመክፈል ነጻ ማውጣትና የራስ ማድረግ ማለት ነው፡፡በዚህ አገባብ ከጥንት የእግዚአብሔር የነበረው ታላቁ ሀብት የሰው ልጅ በገዛ ነጻ ፈቃዱ ወደዲያብሎስ ፈቀቅ በማለቱ ክርስቶስ ኢየሱስ ሰው ከእግዚአብሔር ፈቀቅ በማለቱና ኃጢአት ሠርቶ ሊቀበል የሚገባውን መራራ መከራና ሞት (ቅጣቱን) ተቀብሎ፤ዕዳውን ሁሉ በመክፈል በገዛ ደሙ የሰውን ልጅ ገዛው፡፡
     የተዋጀነው በቀዳሚነትከሕግ እርግማንነው፤ (ገላ.3÷13) እርሱ ስለእኛ የተረገመ ሆኖ እኛን በሕጉ ከመረገምና ሕግን ባለመፈጸም ከሚመጣብን የሞት እርግማን ዋጀን፡፡ እርግማናችን ሁሉ በመስቀሉ ተጠርቆ ከመንገድ ተወግዷልና አሁን እኛ በመስቀሉ ሥራ፤ በክርስቶስ ሞትና በደሙ ተዋጅተን ንጹሐን ሆነናል፡፡ በቀጣይነት የተዋጀነውከአመጽ ሁሉነው፤ (ቲቶ.2÷14) በሐዲስ ኪዳን ጸሐፍት ኃጢአት ሁሉ አመጽ ነው፤ (1ዮሐ.5÷17) ክብር ይግባውና ከእንዲሁ ምህረቱ የተነሳ መድኃኒታችን በመድኃኒት ደሙ አዳነን፡፡
     ሰው ከኃጢአት ሁሉ በራሱ ፈጽሞ መዳን አይቻለውም፤ የክርስቶስ ደም ግን ብቃት ያለው አዳኝና ዋጋችን ስለሆነን ከኃጢአተ ሁሉ በእርሱ የተዋጀን ሆነናል፡፡ ኢየሱስ በሞቱ እኛን ዋጅቶናል፡፡ ሞቱ የህይወት ዋጋ፣ ውርደቱ የክብር ሰገነት፣ ሥቃዩ የደስታችን እልልታ፣ የሾሁ ጉንጉኑ የጽድቅ አክሊልሆኖልናል፡፡ የተገዛነው በውድ ዋጋ ነው! በክርስቶስ ኢየሱስ ደም! (ኤፌ.1÷7) በደሙ በመዋጀታችን የኃጢአትን ይቅርታም አጊኝተናል፤ (ቆላ.1÷13-14)
      የተገዛንበት ዋጋ ፍጹም መተካከያ የለውም፤ (1ቆሮ.6÷207÷23) የክርስቶስ ኢየሱስን ደም ምንም ምን የሚወዳደረው የለም፡፡ የገዛን በራሱ ደም ነው፤ በዋጋ ተገዝታችኋልናየሚለው ቃል የተገዛንበት ዋጋ የክርስቶስ ደሙ መሆኑን ያገናዝባል፡፡ የተገዛነው ዋጋ በማይተመንለት ዋጋ ነው፡፡ በክርስቶስ ሁሉን እንወርሳለን የምንለው ዋጋችንን የከፈለልንና ዋጋችንም የሆነው እርሱ ስለሆነ ነው፡፡ ዋጋችን ነውና በእርሱ እርሱንና መንግስቱን እንወርሳለን፡፡ አንዲት በክርስቶስ ደምና ሞት ያመነች ነፍስ ዋጋ ሰማያውያን መላዕክትና ምድራውያን ቅዱሳን ከቶውንም ሊያውቁት አይቻላቸውም፤ የዚያች ነፍስ ዋጋዋ ራሱ ክርስቶስ ነውና እርሱ ከግምት፣ ከሕሊናና ከዕውቀት ያልፋል፡፡ በእውነት ይህን ጌታ ማን ይስተካከለዋል?! በእውነት ይህን ጌታንጉሠ ጽድቅ ፣ንጉሠ ሰላም በደሙ ላስታረቀን በትሩፋቱ ላጸደቀን ለክርስቶስ መባል ይገባል፤” (ድርሳን ዘዮሐንስ አፈወርቅ 12 ድርሳን .29)፡፡
       በክርስቶስ ተወደህ ዋጋህ የበዛልህ ወዳጄና ወገኔ ሆይ! እባክህን ዋጋህን በኃጢአት አመጽ አታርክሰው፡፡ እርሱ በትልቅ ፍቅር ወዶሀልና አንተ በትንሹ ኃጢአት መልሰህ ራስህን አትርገመው፡፡ በደሙ በቤቱና በደጁ ያገነነህን ጌታህን፣ እንዳትሞትበት የሞተልህን አገልጋዩና ትሁቱ፤ አምላክ ዘመድህን እባክህን አታስቀይመው፡፡ በብዙ ዋጋ ያከበረህን ትተህ በትንሹ ኃጢአት ሊያረከረስህ ሞትን ቀጥሮ ከሚማጸንህ ክፉ ባልንጀርነትና ዲያብሎስ ርቀህ ወዳጅህን ቀና ብለህ እየው!! ዛሬም ገና ልታድን እጁ ተዘርግታ አንተን ትጠብቃለች፡፡

                                4-ደሙ የተሻለውን ጮኾ የሚናገርልን ነው፡፡

ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል።”(ዕብ.12÷24)

ስለእኔ በቀራንዮ የፈሰሰ ንጹህ የሚሆን የመሢህም ደም እነሆ ስለእኔ ይጮኻል፡፡” (የሐዋርያት ቅዳሴ) (መጽሐፈ ቅዳሴ ጕልህ፡፡ (1994)፡፡አዲስ አበባ፣ትንሳኤ ማተሚያ ድርጅት፡፡ገጽ 107)
      እግዚአብሔር የቀረበውን መሥዋዕት ሳይሆን መስዋዕቱ የቀረበበትን ልብና መንፈስ አስቀድሞ ያያል፡፡ ቃየል መስዋዕትን ቢያቀርብም መሥዋዕቱን ያቀረበበት ልብ ግን የጠቆረ ነበረ፡፡ አቤል ደግሞ መስዋዕቱን በእምነት እግዚአብሔር ከሰጠው ርቢ መካከል ለእግዚአብሔር የተወደደውን መስዋዕት አቀረበ፡፡(ዕብ.11÷4) ስለዚህም እግዚአብሔር ቀድሞ ወደአቤል ልብ ከዚያም ወደመሥዋዕቱ ተመለከተ፡፡ መጽሐፍእግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ”(ዘፍ.4÷4) እንዲል፡፡ የአቤል የልቡ እምነት በመስዋዕቱ ንጽዕና ተገለጠ፡፡ ይህ ግን ቃየልን ደስ አላሰኘውም፡፡ እጅግ በሚያሳፍር መልኩም የወንድሙን  የአቤልን ደም በማፍሰስ ገደለው፡፡
    ቃየል በማን አለብኝነት ወንድሙን ቢገድልም የወንድሙ ደም ግን ወደእግዚአብሔር ይጮህ ነበር፡፡በግፍ ተገድሏልና፡፡ በእርግጥ የአቤል ደም የጮኸው በመክሰስ ስለፍርድ ነውና፤ የሚሻለውን አልተናገረም፡፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ ግን በደሙ የተሻለውን ቃል ጮኾ ይናገራል፤ (ዕብ.12÷24) እርሱምአባት ሆይ፥ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው”(ሉቃ.23÷34) ያለው ቃሉ ዛሬም ህያው ነውና ስለይቅርታ ስለእርቅ ይጮኻል፡፡
     የክርስቶስ ደም ዛሬም ህያው ነውና ይናገራል፡፡ የሚናገረው እንደቀደመው በየቀኑ መስዋዕትን በማቅረብ አይደለም፤የእርሱ መስዋዕትነት ፍጹም ነውና ዘላለማዊ ቤዛነትን ተቀዳጅቶ አሁን በሰማያዊቷ መቅደስ አለ፡፡ አንድ ጊዜ ያቀረበው መስዋዕት የማንኛውንም ሰውና በየትኛውም ዘመን የተፈጸመን ኃጢአት ማሥተስረይ ይችላል፡፡አዎ! ዛሬም ደሙ ኃጢአተኞችን ይቅር ሊል ትኩስና ሕያው፤ የሚጮህና የተሻለውንም ቃል የሚናገር ነው፡፡
     ስለኃጢአተኞች መፍሰሱን፣ ኃጢአተኞችም ሁሉ መጥተው እንዲሁ እንዲቀደሱ፣ አምነው የመጡትም በየትኛውም የጠላት ክስ እንዳይፈሩና ወደኋላ እንዳይመለሱ፣ ልብሳችሁ አድፏል፤ ኃጢአታችሁ በዝቷል፤ ማንም ይቅር አይላችሁምብሎ ጠላት የሚከሳቸውን በሚያጽናና አንደበት የሚናገር ቃል አለው፤ የኢየሱስ ክርስቶስ ህያው ደም!!! እንኪያስ ኃጢአት የበዛባችሁ፣ የሰው ክስ ያደከማችሁ፣ መዳናችሁን እንድትጠራጠሩ ጠላት ብዙ ያንሾካሸከባችሁ ቅዱስና ህያው ወደሆነው፤ የተሻለውንና መልካሙን ስለእናንተ ወደሚናገረው ወደዚህ ቅዱስና ህያው ደም !!!
          5- ደሙ ለዘላለም አሁንም መታያችን ነው፡፡

                    “በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን የሚታይ … ” (ዕብ.9÷24)

                    “… እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ
                     ከተሰዋ በኋላ፥ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት
                     ይታይላቸዋል” (ዕብ.9÷28)

            “ዛሬም ስለእና በእግዚአብሔር ፊት ተገለጠ፤ ሰው ከመሆኑ በፊት ለምን አልተገለጠም? እርሱማ በሕልውና ያለ፤ ያለድካም ሁሉን የፈጠረ ሁሉ የተፈጠረበት የአብ ጥበቡ ነው እንጂ፡፡ ዛሬስ በምን ሥራ፤ በምን ነገር በእግዚአብሔር ፊት ተገለጠ፤ አምላክ ቃል እንደእና ሰው ሆኖ በአዲስ ሥራ ተገለጠ፡፡ አለም ሳይፈጠር ሥጋንም ሳይዋሐድ በመለኮቱ በአብ ዘንድ ሕልው ሲሆን ስለእኛ በእግዚአብሔር ፊት በእኛ ባሕርይ በአስታራቂነት ተገለጠ፡፡ ዛሬ ስለእኛ  በእግዚአብሔር ፊት እንደተገለጠ የምንናገረው ነገር ይህ ነው፤ … ” (ሃይማኖተ አበው ዘቄርሎስ፤  ምዕ.79 ክ.50 ቁ.71-73)
      ሊቀ ካህናት በየዓመቱ ስለህዝቡ በእግዚአብሔር ፊት እንዲታይ ደሙን በሥርየት መክደኛው ላይ ይረጨዋል፡፡ እግዚአብሔር የህዝቡን ኃጢአት ይቅር ሊል፤ ስለህዝቡ የእንሰሳው ደም በእግዚአብሔር ፊት ይታያል፡፡ ያለደም መፍሰስ ስርየት የለምና፤ (ዕብ.9÷22) እግዚአብሔር በምህረት ሊገለጥና ሊታይ ደሙ ቀድሞ በእግዚአብሔር ፊት መታየት አለበት፡፡ እግዚአብሔርስለብቃታችንይቅር አይለንም፤ በእኛ ምትክ ሆኖ ስለፈሰሰው ደም እንጂ፡፡
    ያለክርስቶስ ደም ምድር ሁሉ ወንጀሉን በእጁ ጨብጦ በጨካኝ ዳኛ ፊት የሚቆም ሰውን ትመስላለች፡፡ እግዚአብሔር ያለክርስቶስ ደም ይህችን ምድር ቢያይጽድቁ የመርገም ጨርቅ የሆነበትን ፣መልካምነቱ ያረረበትን ፣ቅድስናው የረከሰበትን፣ጥበቡ የደነቆረበትን … ” ፍጡር ብቻ ነው የሚያየው፡፡ እግዚአብሔር ከምድር መልካም መዓዛን ያሸተተውና ከእኛ የመንፈስ ፍሬን የፈለገው በክርስቶስ ኢየሱስ ደም በኩል ባየን ጊዜ ነው፡፡ አብ አይቶ የረካበትና ደስ የተሰኘበት እርሱ ልጁ ክርስቶስ ብቻ ነው፤ እርሱም እኛን ሁሉ ወክሎ በመስቀል ላይ ታየ፡፡ አብ የአዳምን ልጆች ቅጣት ሁሉ ወይም አዳም ሊቀጣ የሚገባውን ሁሉ ክርስቶስ የተቀጣ ሆኖ በፍርድ ተወሰደ፤ (ኢሳ.53÷8) ስለዚህ ስለእኛ ኃጢአት በእግዚአብሔር ፊት የተቀጣው ክርስቶስ ዛሬም የተገባ ሆኖ ይታይልናል፡፡

     ኢየሱስ ክርስቶስ ፤አብ የረካበት ህያው መስዋዕት ዛሬም እንደታረደ በግ ሆኖ በሰማያት ስለእኛ ይታያል፤ (ራእ.5÷6) በሞቱ ሞታችንን ድል ነስቶ በሰማይና በምድር ሥልጣን የጨበጠው ቅዱሱ በግ የታረደበት ምልክቱ ዛሬም በሰማያት ስለእኛ ይታያሉ፡፡ ደሙ ለአለምና ለዘላለም የሚበቃ ሆኖአልና ለእኛ መገለጡ ወይም በሰማያት መታየቱ ብቻ ይበቃናል!!! “በእግዚአብሔር ፊት በእኛ ባሕርይሆኖ ሊቀ ካህናታችን ባለበት በዚያ እኛም ደግሞ በሚታይልን  በደሙ ብቃት እንገባለን፡፡
      እሱ ስለእኛ የሚታይልን ባህርያችንን ስለነሳና ሰው ስለሆነ ነው፡፡ አሁን ስለኃጢአት ስለእኛ በእግዚአብሔር ፊት ይታያል፤ በኋላ ግን በዳግም ምጽአት ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት በሞገስና በፍቅር እጆቹን ዘርግቶ ይታይላቸዋል፡፡ በዚህም ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁቱ ወደታላቁ የበጉ ሠርግ ታድመዋልና ልዩ የክብርና የሐሴት ቀናቸው ነው፡፡ አዎ! ይህ ሁሉ ዛሬ ደሙ መታየቱን ለሚያምኑና ለሚቀበሉ ብቻ ነው፡፡
ይቀጥላል


No comments:

Post a Comment