Tuesday 5 March 2024

ነገረ ሥላሴን የምናጠናበት ምክንያት (ክፍል ፱)

Please read in PDF

ካለፈው የቀጠለ …

  • ንፈስ ቅዱስ፦ መንፈስ የኾነ (ዮሐ. 4፥24)፣ ፍጥረትን በመፍጠርና በውበት በማጌጥ (ዘፍ. 1፥2)፣ ከርሱ በመወለድና አዲስ ልደትን ለአማኞች የሚሰጥ (ቲቶ 3፥5)፣ ኃይልን በማልበስና የጸጋ ስጦታን ለቤተ ክርስቲያን በመስጠት ወይም በማከፋፈል (ዘካ. 4፥6፤ የሐ.ሥ. 1፥8፤ 1ቆሮ. 12፥7-11) በጽደቅ ፍሬዎች በመሙላትና በመቀደስ በአማኞች ሕይወት ውስጥ የሚኖር (ዮሐ. 14፥17፤ 1ቆሮ. 3፥16፤ 6፥19፤ ገላ. 5፥22-23፤ ኤፌ. 2፥22)፣ አብሮን በጸሎት የሚቃትት (ሮሜ 8፥26)፣ ቅድስት ድንግል ወልድን በተለየ አካሉ በሥጋ እንድትፀንስ በፈቃዱ ወድዶ የመጣ (ማቴ. 2፥11) የዘላለም እግዚአብሔር ነው፤ (ዕብ. 9፥14)።

ዓለምን ስለ ኃጢአት፣ ስለ ጽድቅ፣ ስለ ፍርድ የሚወቅስ፣ አማኞችን ስለ ክርስቶስ የሚያስታውስና የሚመሰከር (ዮሐ. 14፥26፤ 16፥8-11፤ ሮሜ 8፥14፤ ኤፌ. 1፥13፤ 1ጴጥ. 1፥1-2) ቅዱሳት መጻሕፍትን ቅዱሳን ሰዎች ይጽፉ ዘንድ የመራ ወይም የነዳ (ዮሐ. 1፥16፤ 2ጴጥ. 1፥21)፣ የሚመራና የሚያጽናና (ኢሳ. 48፥16፤ ዮሐ. 14፥26፤ ሮሜ 8፥14)፣ ኀጢአትን የሚከልከል (ዘፍ. 6፥3፤ ኢሳ. 59፥19፤ 2ተሰ. 2፥7) የሚያዝዝ (የሐ.ሥ. 8፥29፤ 13፥2፤ 16፥7፤ 2ተሰ. 2፥7) የጽደቅና የእውነት መንፈስ ነው።

እንዲሁም፣ “አባ” የሚለው ቃል አይሁዶች ከቤተሰባቸው ጋር ያላቸውን ጥልቅ ግንኙነት፣ ቅርርብ፣ ጥገኝነት እና ፍቅር የሚያመለክት ቃል ነው። እግዚአብሔር አምላክም፣ በቅዱስ መንፈሱ በኩል ይህን ከርሱ አጠገብ መገኘት፣ ፍቅር፣ ርኅራኄ፣ ጥበቃ እና አስደናቂ እንክብካቤ ይሰጠናል።

ከዚህም ባሻገር፣ መንፈስ ቅዱስ መዳናችንን የሚያረጋግጥ፣ ፍጹም ማኅተም ወይም የባለቤትነት ምልክት ነው። በጳውሎስ ዘመን፣ ማኅተም አንድ ደብዳቤ ወይም ጥቅልል ​​እንደ ተዘጋ ወይም እንደ ተጠናቀቀ ያመለክታል። አንድ ንጉሥ ወይም ባለ ሥልጣኑ መለያ ምልክት በደብዳቤ ለማሳየት ሲፈልግ፣ ቀለበቱን በሚሸፍነው ሙጫ ያትማል። መንፈስ ቅዱስ በአማኞች ላይ የእግዚአብሔር ምልክት ነው እና የእርሱን መኾናችንን ያትማል ወይም ያረጋግጣል ወይም ያጸድቃል፤ (2ቆሮ. 1፥22)።

ስለዚህም ቅድስት ሥላሴ ርስ በርስ ባላቸው ግንኙነት፣ ግንኙነታቸው አምላካዊና ፍጹም በኾነ አንድነት እንደ ኾነ፣ እንዲሁም ከፍጥረት ጋር ባላቸው ግንኙነት ግን ሦስቱም በተለያየና አንድ በኾነ መንገድ እንደ ኾነ አንስተናል። መዘንጋት የሌለብን እውነት፣ ሥላሴ ርስ በርስ ባላቸው ግንኙነት ዓይነት፣ ከፍጥረት ጋር ፈጽሞ እንደማያደርጉ ማስተዋል ይገባል። ርስ በርስ የሚያደርጉት ግንኙነት በመለኮታዊ ምልአት ብቻ ሲኾን፣ ከፍጥረት ጋር በሚያደርጉት ግንኙነት ግን አምላክና ፍጡር በሚያደርገው ዓይነት ግንኙነት ብቻ ነው።

ይቀጥላል …


1 comment: