Thursday 14 November 2013

በከንፈሩ የሚያከብር ህዝብ(ኢሳ.29÷13)


         ሰሞኑን ከወደምድረ ዓረብ ስለሰማሁትና ስላየሁት ነገር እንዲህ አልኩ…!!!
         በመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ዘንድ "ደረቅ አዲስ ኪዳን" እየተባለ የሚጠራው መጽሐፉ፣ኢሳይያስ የስሙ ትርጓሜ "እግዚአብሔር ያድናል" ማለት ነው፡፡በነቢዩ ዘመን ይሁዳና ህዝቦቿ "የእስራኤልን ቅዱስ" ተወዳጁን ጌታ ንቀውና አቃለው ነበር፡፡ከህዝቡም ኃጢአትና ነውር የተነሳ የእርሻው ቡቃያ ተዘርቶ ሊሰጥ ከሚገባው እጅግ አነስተኛውን የሰጠበት ዘመን ነበር፡፡(ኢሳ.5÷9-10)የእግዚአብሔር ቃል በዘመኑ ለባለራዕዮችና ለነቢያት እንኳ ሳይቀር የተዘጋና የተሰወረ ሆኖም ነበር፡፡(ኢሳ.29÷10)
       መስዋዕቱ፣ቁርባኑ፣የመቅረዙ መብራት፣ዝማሬው ፣ቃሉን መስማት ፣መስገዱ ፣መጾሙ፣መጸለዩ፣…. ያልተጓደለበት ነገር ግን ይህ ሁሉ ሆኖ ህዝብና መሪ በአንድ ያበደበት፣ነቢዩ ከጠንቋይ የተስማማበት፣ አዝማሪ ከዘማሪ የተቋመሩበት፣መሪው በጉቦ አይኑ የታወረበት ፣ሰባኪ ከዘማሪ በዝሙት የረከሰበት፣ህዝቡ "በአስረሽ ምቺው" ኃጢአት የተካነበት፣ካህኑና ዲያቆኑ ተማክረው ሙዳየ ምጽዋት ሰብረው የሚሰርቁበት፣ ህዝቡ ላየው ሁሉ ልቡን የሚከፍትለትን ይህን የእኛን ዘመን ይመስላል የነቢዩ ዘመን፡፡
      ይሁዳ ዕለት ዕለት እግዚአብሔርን የምትፈልግ ፣መንገዱን ለማወቅ የምትጓጓ፣ትዕዛዙን እንዳልተወች፣    እግዚአብሔር ወደእርሷ እንዲቀርብ የምትወድ ፣የምትጾም፣ራስዋን ያዋረደች … ብትመስልም ነገር ግን ሠራተኞችን የምትበዘብዝ፣ጾሟ ከጥልና ከክርክር ያልጸዳ፣ በግፍና በጡጫ የምትደበድብ … ነበረች፡፡(ኢሳ.58÷1-4)፡፡


     ስለዚህም "ህዝቤ" የሚላትን ይሁዳን "ይህ ህዝብ" ብሎ ጠራት፡፡እንደሚስት በወቀሳና በምክር ቃል የሚናገራትን የይሁዳን ቤት አሁን ከፈቃዱ ፈቀቅ ብላ እንደአህዛብ ወግና እንደአለማውያን ልማድ በኃጢአትና በሚበዛ ግፍ ስለተያዘች "ይህ ህዝብ" አላት፡፡እግዚአብሔር እውነተኛ ዳኛ ነው፡፡ፍርዱ ባላመኑት ህዝብ ላይ ብቻ ሳይሆን ያመኑት ወገኖቹም ወደውና ፈቅደው በግብዝነት ኃጢአት ሲወድቁ ፊት አይቶ ሳያዳላ ይፈርዳል፡፡እኛ የኃጢአትን መንገድ መርጠን ከእግዚአብሔር  ፊት  እንሸሻለን እንጂ እግዚአብሔር ለሚጠሩት ሁሉ ቅርብና የሚሰማም ነው፡፡በእግዚአብሔር የፍቅር ጉያ መኖር ሰልችቶን ኃጢአትን ናፍቀን ስንሔድ በሰይጣን የቅጣት ግዞት ውስጥ እንገባለን፡፡
     ይሁዳ ከላይ ላያት የአምልኮ ሥርዐቷ የሚማርክ ውብ ነው፡፡ነገር ግን ሁሉ ነገር እንደሰው ሥርዐትና ትምህርት ከከንፈር እንጂ ከልብ አይደለም፡፡እግዚአብሔር የምትሸነግልን ምላስ አብዝቶ ይጠየፋል፡፡ በግብዝነትና በልማድ  ለስምንትና ለዘጠኝ ሰዐት ከሚፈጸም ቅዳሴና ማህሌት ይልቅ መዳን ባለው ንስሐ የሚፈጸም የሦስት ደቂቃ የንስሐ ጸሎት ይበልጣል፡፡እግዚአብሔር በከንፈር ረዝሞ ሳይሆን በልብ ከመንፈስ የሆነውን ያጠረውን መስዋዕት ያሸተዋል፡፡ጌታም ፈሪሳውያንን ስለአባቶች ወግ ምክንያት የእግዚአብሔርን ፈቃድና ህግ በመሻራቸው በግልጽ ነቅፏቸዋል፡፡(ማቴ.15÷6)፡፡
        ሽንገላ የከንፈር አምልኮ ነው፡፡ዛሬ ትውልዳችን የተያዘው በዚህ ከባድ ነውር ነው፡፡ሙሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ በሽምደዳ ከንፈሩ ላይ አለ ግና የጠነዛ ያህል ቃሉና ህይወቱ ምኑም አይጣፍጥም፡፡ስለሌላው ቃል አዋቅሮ "በጥበብ" የሚናገረውን ያህል ስለራሱ በእግዚአብሔር ፊት በሞኝነት ማውራትን እንዳልመሰልጠን ቆጥሮታል፡፡
        በዓረብ ምድር ሰሞኑን በአፍሪካውያን ወገኖቼ ላይ እየሆነ ያለውን ከሰማሁት ቀን ጀምሮ በመገናኛ ብዙሀን የሚለቀቀውን ምስልና ጽሁፍ፣ተቃውሞና አቤቱታ … ሳይ ሁለት ነገር ወደልቤ መጣ፡፡ እንዳለመታደል በደስታ ዘመናችን አንስማማም፡፡በሰላም ዘመን ለጎረቤታችን የምላስና የስለት ካራ እንስላለን እንጂ ወደእግዚአብሔር መመለስና ንስሐ ትዝ አይለንም፡፡ዮሴፍ በጥጋብ ዘመን ያከማቸው እህል ነው የረሐቡን ዘመን ያሻገረው፡፡በደስታ ዘመን እየጨፈርን በሀዘኑና በመከራው መጯጯህ የለየለትና አይን ያወጣ ሽንገላና ማስመሰል ነው፡፡የእኛ ህዝብ ጎበዝ ነው¡¡¡ በሰርግ ደግሶ ያጋባል ደግሶም ያፋታል፣የእኛ ህዝብ ጃንሆይ ንጉሳችን እያለ ለጥ ጸጥ ብሎ ይገዛል ይኸው ህዝብ ጃንሆይ ሌባ ሌባ!!! እያለ ያወግዛል፣የእኛ ህዝብ እንደእርሱስ ያለ ዘማሪ፣ሰባኪ፣ዲያቆን፣ቄስ፣መጋቢ፣ሽማግሌ … የለም ባለ አንደበቱ መልሶ ያሳድዳል፣ስም ጥላሸት ይቀባል፡፡እንደእኛ ህዝብ የታደለ ማን አለ¡¡?? ጾሙም አይቀርበት ዘፈን ዝሙቱም አይጎድልበት!!! ሸንጋይ!!!    
        ሌላው መገናኛ ብዙሐኑን ስመለከት እንደመቃኞ በሬ በአንድነት ተነድቶ የእኛን "መሪዎችና" የዓረቡን ባለሥልጣናት የሚራገም እንጂ "የእኔ ነውር የለበትም ይሆን?" ያለ ሰው ለማግኘት ተቸግሬያለሁ፡፡ በህይወቴ የማይረሱኝ እናት አሉ፡፡ሦስት ሴቶች ልጆቻቸው የሚኖሩት በውጪው አለም ነው፡፡እኔና የተወሰን ሰዎች ቤታቸውን ተከራይተን የምንኖርበት ቤት ውብና እጅግም ርካሽ ነው፡፡በዙሪያችን ባሉ የኪራይ ቤቶች ሁለት ጊዜ ጭማሪ ተደርጎባቸው ተከራዮች ሲማረሩ እኛ ሁለቱንም ጊዜ ጭማሪው አላገኘንም፡፡አንድ ቀን ጠጋ ብዬ ጠየቋቸው፡፡መለሱልኝ፡- "ልጆቼ በውጪ ሐገር በስደት ነው ተከራይተው የሚኖሩት፤እኔ እዚህ እናንተን ባስጨንቅ እዚያ ልጆቼን የሚያስጨንቅ የሚነሳ ይመስለኛል" ሲሉኝ የጉንጬን ስርጉድ ትኩስ እንባ አጠበው፡፡
       አዎ! ያ ሁሉ በባዕድ ምድር በወገኖቻችን የሆነውና ባዕዳን ጠላት የሆኑባቸው ከእኛ ነውርና ኃጢአት የተነሳ ነው፡፡እኛ የቤቶቻችንን ሠራተኞች እንዴት ነው የምናስጨንቀው? ጉልበታቸውን በዝብዘን ሲታመሙ ከቤተ ክርስቲያን ደጅ በማታ ጨለማ የምንጥል እኛ አይደለንም? አሰርተን ደመወዝ ከልክለን የምናባርር እኛ አይደለንም? በየቢሮው በሚሆነውና በማይሆነው ደመወዝ የምንከለክልና የምንቆርጥ ስንቱን ድሀ ደም የምናስነባ እኛ አይደለንም? ምጽዋተ ሙዳዩን ሰብረን የምናመነዝርበትና ጠጥተን የምንሰክርበት እኛ አይደለንም? ይህን እያደረግን ጠዋት ለአምልኮ ቀድመን ቅዳሴ ላይ የምንቆመው፣ህያው ህንጻ እያፈረስን የድንጋይና የጭቃ ህንጻ የምናሰራው፣በስጦታ ኃጢአታችንን ማለቃለቅ የምንሻ የሽንገላ አምልኮ የምናቀርብ እኛ አይደለንም???
    ሀገር በተቃውሞና በጩኸት ፖለቲካ አይለማም፡፡የሚቀድመው የሌላውን ነውር ማውራት ሳይሆን የራሳችንን ኃጢአት በንስሐ ስንሸፍን ነው፡፡ጌታ ስለእኛ የሚዋጋው እኛ በፊቱ በመዋረድ ስንበረከክ እንጂ ራሳችንን ንጹህ አድርገን በሌላው ላይ ጣታችንን ስንቀስር አይደለም፡፡አዎ! ጆሮ ጭው የሚያደርገው ነገር ያገኘን በነውራችን በገዛ ኃጢአታችን ነውና ሳንሸነጋገል ብንመለስና ፊታችንን ወደእግዚአብሔር ብናቀና ይሻለናል፡፡አልያ ግን መከራና ሐዘኑ ገና የማያባራ ገና የማያቆምም ነው!!!
  አቤቱ መድሐኒታችን ሆይ! ስደተኛ ህዝብህን አስብ፣ርስትህን ወገንህን ባርክ ፣እኛንም ወደልባችን መልሰን፡፡አሜን፡፡      

5 comments:

  1. I agree u touch the focal point be
    blessed,instead of blaming some body
    else we need to point our fingers on us.
    every body need's to now what does it
    means Christianity we are the most
    cruel &selfish people in this planet we
    don't deserve this name Christian.i don't get it what kind of blood we have.
    education can't change us,country can't change us it's really horrible all this mess is our fault but no one believe his
    or her fault whether religious leaders or
    Political parties its disgusting.

    ReplyDelete
  2. wendme tsegawun yabzalh berta.betam des yemil new iyitah.ayzoh bertana tsaf

    ReplyDelete
  3. What a lovely article. May God bless you my brother.
    I 100% agree.

    ReplyDelete
  4. Amen amen amen Egziabher bechernetu wede lbachin ymelsen Kale hywetn yasemaln tsegawn yabbzalh tebarek!

    ReplyDelete