Monday 11 November 2013

የሕጻኑን ነፍስ የሚፈልጉት (ማቴ.2÷20)

     በሥጋ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው ኢየሱስ፥ ዓለምን ብቻውን ሊያድን ብቃት ያለው አዳኝ፣ መሲህ ክርስቶስ ሆኖ የሰውን ልጅ ሊያድን ተገልጧል፡፡ ነቢዩ "ሕጻን ተወልዶልናልና …"(ኢሳ.9÷6) ያለውን ያንን ሕጻን፥ ማቴዎስም ሕጻን ብሎ ይጠራዋል፡፡ ይህ ሕጻን ገና ሳያድግና አንደበቱን ከፍቶ ሳይናገር የንጉሥ ፍርሐት፤ የዲያብሎስ ጭንቀት ሆነ፡፡ ኢየሱስ ገና የሁለት ዓመት ሕጻን ቢሆንም፥ ጎልማሳው ሄሮድስ ግን የመግደል ሴራን በስውር ጠነሰሰ፡፡ ጠላት ዓላማ ቢስ ከሆነ ሽማግሌና ጎልማሳ ይልቅ ዓላማ ያለውን ሕጻን በአላማ አጽንቶ ይዋጋል፡፡ ጉዳዩ አላማ እንጂ ዕድሜ አይደለምና፡፡
      የሁለት አመት ሕጻን በሰው ፊት ትርጉም ላይሰጥ ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ግን እጅ በአፍ እስክንጭን  በድንቅ ቃል ምስጢር ያወራዋል፡፡ በነቢዩ ሳሙኤልም የሆነው እንዲህ ነው፡፡ እግዚአብሔር ታላላቅ ነን ከሚሉት ጋር ሳይሆን ስለእስራኤል ጉዳይ ከሁለት አመቱ ብላቴና ጋር ያወራ ነበር፡፡ ዓለማውያንና የመቅደሱ አገልጋዮች በእግዚአብሔር ላይ በኃጢአት ሲያምጹ እግዚአብሔር ሳሙኤልን በትሑት ቃል ተናገረው፡፡

       አገልግሎት በዕድሜ፣ በዕውቀት፣ በንግግር ጥበብ፣ በሰው ብልሐት … እየመሰላቸው ስንቶች ናቸው ዛሬም ሕጻናትን የሚያሳድዱ? ቀሚስ ስላልለበሱ፣ መስቀል ስላልጨበጡ፣ ጎምለል እያሉ መድረክ ስላልሞሉ፣ ሰው ጎንበስ ቀና እያለ "ስላልሰገደላቸው" … የተረሱና የተጣሉ ስንት አገልጋዮች አሉ? እግዚአብሔር የሁለት ዓመት ሳሙኤልን መርጦ ካህናቱን አፍኒን፣ ፊንሐስንና ዔሊን የናቀው ለምን ይመስላችኋል?  አገልግሎት የእግዚአብሔር መገለጥ እንጂ ሹመትና እድሜ፣ ሰዋዊ ብልሐትና ሜዳዊ ሥርአትን ማሟላት ስላልሆነ ነው፡፡ ሰላሳ፣ አርባ አመት "በእግዚአብሔር ቤት" ተቀምጠውና አገልግለው ኖረናል እያሉ እግዚአብሔርን የማያውቁ ሰዎች ብታገኙ ምን ይሰማችኋል? አዎ! አገልጋይነትና አማኝነት በመገለጥ የመኖር ጉዳይ እንጂ ዕድሜ የመቁጠር ጉዳይ አይደለም፡፡
       ጠላት ዓላማን እንጂ ዕድሜን አይፈራም፡፡ ስለዚህ ሄሮድስ ኢየሱስን ለማግኘት ኢየሱስን የማያውቁትን የቤተልሄምና የአውራጃዋን የሁለት አመት ህጻናት በሙሉ አስገደለ፡፡ የቤተ ልሔም ሕጻናት ኢየሱስን አያውቁትም ግን በእርሱ ስም ተገደሉ፡፡ ኢየሱስን የማያውቁ በስሙ ግን መከራን የሚቀበሉ ዛሬም ቁጥራቸው ትንሽ እናዳይመስላችሁ፡፡ "ኢየሱስ ያድናል"፣ "ኢየሱስ ፈራጅ ነው"፣ "ኢየሱስ ጌታ ነው" … የሚሉ ግና እንዴት እንደሚያድን፣ እንዴት እንደሚፈርድ፣ ለምን ጌታ እንደተባለ የማያውቁ አብርሆተ መንፈስ ቅዱስ የሌላቸው ጯሂ ደቀ መዛሙርት ዛሬም በጭፍኑ እይታቸው ክብር የሌለውን መከራ ሲቀበሉ ማየት ያሳዝናል፡፡
       ብዙዎቻችን በወንድና በሴት ፍቅር ታምተን የምንደሰተውን ያህል በክርስቶስ ኢየሱስ ስም መታማትን አንፈልግም፡፡ ግና መነቀፋችን፣ መጠላታችን፣ መታማታችን፣ ከሰው መካከል መወገዳችን … በስሙና በስሙ በማመን ካልሆነ በቀር ከንቱ ድካም ከንቱ ትምክህት ነው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ያለኢየሱስ በሌላ በማንም ስም አልተነቀፉም፣ አልተሰደቡም፣ መከራንም አልተቀበሉም፡፡ (ሐዋ.4÷2 ፤ 5÷40 ፤ 7÷52 ፤ 17÷3)፡፡ ጌታም ለሚያምኑቱ በስሙ ብቻ መከራን ቢቀበሉ፣ ስሙን እያገለገሉ ውሸት ሲናገሩባቸው ቢታገሱ የሚጠብቃቸውን ክብር ገልጦላቸዋል፤ (ማቴ.5÷11)፡፡ እኛም የኪዳኑ ተካፋዮች ነንና ከስሙ በቀር በሌላ በማንምና በምንም ስም መከራ ልንቀበል አይገባንም፡፡
      ሄሮድስ በዋናነት የፈለገው አንዱን የናዝሬቱን ሕጻን ኢየሱስን ነው፡፡ ነገር ግን በመልአኩ አንደበት እንደተነገረ "የሕጻኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋል"፤ (ማቴ.2÷20) ተባለ፡፡ የሚገርመው እውነት ይህ ነው! ሕጻኑ ሀያላን ነገስታትን፣ ጽኑአን ገዳዮችን …ያስረጀና ያደከመ ነው፡፡ ሁልጊዜ ብርቱ የሚመስል የባላጋራ እጅ ከገለባ ይልቅ ቀሎ፣ እንደተወዘወዘ መስዋዕት ሲዝል አይተናል፡፡ የይሁዳው አንበሳ የናዝሬቱ ሕጻን ግን ሸሽቶ ያሸነፈ በብርታቱም ኃይለኞችን ያዋረደ ነው፡፡
      ልጁን የሚያሳድዱ በእርጅና ሞት ተይዘው በመቃብር ይወሰናሉ፡፡ የልጁ መንግስት ግን በሰማይና በምድር የጸናች ናት፡፡ የእውነትን ወንጌል የሚቃወምና የሚያሳድድ ጉልበት እስኪገርመን ድረስ ይዝላል፡፡ ወንጌላችን ግን ገና የጠላትን ግዛት ምርኮ ያለድካም ይሰበስባል፡፡ በአሰቃቂነቱ ወደር ያልተገኘለትን የማርቆስ አውሬሊያኖስን(161-180 ዓ.ም)የክርስቲያኖችን የስደት ዘመን ያየን እንደሆን ስለት የጨበጡት የገዳይ ወታደሮች እጅ ዛለ እንጂ የስሙን ምስክርነት የተሸከሙና የሚሸከሙ ዕለት ዕለት ይጨመሩ ይበዙም ነበር፡፡
      አዎ! በሄሮድስ የተገፋውና የተጠቃውን ሕጻን "እግዚአብሔር ያለልክ ከፍ ከፍ አደረገው ከስም ሁሉ በላይ ያለውን ስም ሰጠው…"(ፊሊ.2÷9)፡፡ እንኪያስ የምታምኑ ሁሉ ደስ ይበላችሁ፡፡ የሚያሳድዷችሁ በገዛ እጃቸው መቃብራቸውን አዘጋጅተው ለሞት ሲቸኩሉ፥ ለእናንተ ግን የክብርን ሰገነት እያዘጋጁላችሁ ነው፡፡
   "የሕጻኑን ነፍስ የሚፈልጉት የሞቱ" ቢሆኑም ዛሬ የሌሉ ግን አይደሉም፡፡ ዛሬም ወንጌልን የተሸከሙ እውነተኛ አገልጋዮችን ነፍስ ፈልገው የሚያሳድዱ፣ ስም የሚያጠፉ፣ የሚወግሩ … አሉ ግና ሁሉ የሚዝሉ የሚያረጁ፣ በሞትም የተገደቡ ናቸው፡፡በስሙ የተጠቃችሁና የተናቃችሁ ግን ደግሜ  እላለሁ ደስ ይበላችሁ የናዝሬቱ ሕጻን ቀን አውጥቶላችሁ በአሳዳጆቻችሁ ፊት በሞገስ ያራምዳችኋል!!!
    የሕጻኑን ነፍስ የሚፈልጉ ይሞታሉና ሕጻኑን የምትሰብኩ ያለፍርሐት አሁኑኑ ተነሱ ኃይል የህጻኑ ማዳንም የክርስቶስ ብቻ ነውና፡፡ ጌታ ማስተዋልን ያብዛልን፡፡ አሜን፡፡


4 comments:

  1. አሜን አሜን አሜን ቃለ ህይወትን ያሰማልን !!!

    ReplyDelete
  2. የድንግል ማርያም ስደትና የዋልድባ ገዳም ጉብኝት

    አንዳንድ ሰዎች ድንግል ማርያም በስደቷ ጊዜ ወደ ኢትዮጲያ መጥታ እንደነበር ጎንደር ክፍለሀገር ዋልድባ በሚባለው ገዳም እንደተገኘችና ኢየሱስም ለእናቱ ለማርያም ኢትዮጲያን እንድትጠብቃት በአስራትነት እንደሰጣት ይናገራሉ፡፡ የእነዚህ ሰዎች ምኞትና ሀሳብ መልካምና የሚያስጎመጅ ቢመስልም ምንም አይነት መፅሀፍ ቅዱሳዊ መረጃ የሌለውና ከአጠቃላይ የመፅሀፍ ቅዱስ አስተምህሮ ጋር የሚጋጭ በመሆኑ ከብዙ ሺህ ተረቶችና አፈታሪኮች እንደ አንዱ የሚቆጠር በቁም ነገርም ሊወሰድ የማይችል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
    ብዙሀኑ ህብረተሰብ የሚሰማውን ሀይማኖታዊ ነገር እንደወረደ በሚቀበልበት እንደ ኢትዮጲያ ባለ ሀገር እጅግ ጥቂቶች ብቻ የሰሙትንና የሚባለውን ነገር በስነ አመክንዮም አቅጣጫ በማገናዘብ ይህ ነገር እውነት ይሆንን በማለት የታሪኩ ምንጭ የሆነውን መፅሀፍ ቅዱስ ራሳቸው ለማንበብ ይነሳሳሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ግን ይህ ሲነገር የሰሙትን ነገር ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ አባባልና ብዙዎች አምነውበት የሀይማኖታቸው መሰረት ያደረጉትን ነገር ከቅዱስ መፅሀፉ ሳያገኙት ሲቀሩ ስለጉዳዩ ያውቃሉ ብለው የሚያስቧቸውን የሀይማኖት አባቶች ወደ መጠየቅ ሊሄዱ ይችላሉ፡፡
    በዚህ ጊዜ ነው የጥርጣሬ የግጭትና የአለመግባባት ነገሮች የሚመጡት፡፡ የሀይማኖት አባቶች የሚባሉት በእርግጥም መፅሀፉን ራሱን ከፍተው እነዚያን ሲወርድ ሲዋረድ የመጡ አባባሎችንና ታሪኮችን ማሳየት ስለሚቸገሩ በሌሎች መፅሀፍቶች የተፃፉና ከጥንት ጀምሮ የታወቀ ስለሆነ ብቻ የሚባለውን ነገር አምኖ መቀበል የተሻለ እንደሆን ምክር በመስጠት እንደዋዛ ያልፉታል፡፡ ይህን የሚያደርጉት ደጋግና አስተዋይ አባቶች የሆኑ እንደሆን ነው፡፡ አንዳንድ አባቶች ግን ብዙም ማብራሪያና መልስ የማይሰጡበት ጥያቄ ሲመጣባቸው ” እንደው ለእግዚአብሄር ምን ይሳነዋል?” የምትል የተለመደች ድፍን መልስ በመስጠት ከጥያቄዎች ለመገላገል የሚሞክሩ ሲሆን የሚበዙት አባቶች ግን ይህን መሰሉን ጥያቄ በበጎ መልኩ ስለማይመለከቱት ሀይማኖትን እንደመጠርጠር ወይም አባቶችን እንደመፈታተን አለያም ደግሞ በሰይጣን ተልኮ እንደመምጣት ይቆጥሩና ጠያቂዎችን መቆጣት ወይም መገሰፅ አለያም ከዚህ በከፋ መልኩ የማስፈራሪያ ቃላትን በመጠቀም ከጥያቄው መሸሽን እንደ አመራጭ ይወስዱታል፡፡
    የሆኖ ሆኖ ግን

    ReplyDelete
  3. ጥያቄው የተጫረባቸውና እውነትን የሚሹ ሰዎች መቼም ቢሆን እውነትን እስከሚያገኙ ድረስ አእምሮአቸው አያርፍምና መልስ ወደሚያገኙበት ከመሄድ የሚያግዳቸው አይኖርም፡፡
    የድንግል ማርያም ወደኢትዮጲያ መምጣት ነገር በመፅሀፍ ቅዱስ አለመፃፉ ብቻ አፈታሪክ ነው ለማለት ባያስችልም ከመፅሀፍ ቅዱስ ጋራ መጋጨቱ ግን በእርግጥም የፈጠራ አፈታሪክ መሆኑን ከማጋለጡም በላይ ክርስቲያን የሆነ ማንም ሰው ይህንን አይን ያወጣና የመፅሀፍ ቅዱስን ትምህርት የሚያዛባ አፈታሪክ አምኖ በመቀበል እንደ እውነት ሊወስደው ፈፅሞውኑ አይችልም፡፡ ስለዚህም የጌታችን እናት ድንግል ማርያምና ኢትዮጲያ የምትባል ሀገር በምንም ሊገናኙ ሊተዋወቁና ሊዛመዱ እንደማይችሉ ይረዳል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በምድር ላይ ካሉ ሀገሮች ሁሉ ኢትዮጲያን በተለየ መልኩ አይቶ ለእናቱ በአስራትነትም ሆነ በጠባቂነት እንደማይሰጣት በቀላሉ ሊገነዘብ ይችላል፡፡
    እርግጥ ነው አፈታሪኩ በጣም ደስ የሚልና ኢትዮጲያዊ መሆን የሚያስደስት ነገር እንደሆነ እንዲታሰብ ያደርጋል፡፡ ነገር ግን እውነታውን ለመመርመር እንሞክር ከተባለ በውስጣቸው በርካታ ጥያቄዎችን የሚያመነጩ ሁለት አንኳር ነገሮችን በማንሳት መልስ መፈለጋችን አይቀርም፡፡
    ይኸውም አንደኛ የማርያም እጮኛ የሆነው ዮሴፍ በህልም በተነገረው መሰረት ህፃኑን ኢየሱስንና እናቱ ማርያምን ይዞ ወደ ግብፅ መሸሹና ከተወሰነ ጊዜ ቆይታ በሁዋላም እንደገና ወደ እስራኤም ምድር መመለሳቸውን መፅሀፉ ይነግረናል፡፡ ስለዚህ በዚህ የቆይታ ጊዜአቸው ውስጥ ከግብፅ ሀገር ወጥተው ወደሌላ ሀገር ሄደው ነበርን? ብለን መጠየቃችንና ይህም ሆኖ ከነበረ የት ነው የተፃፈው? ታሪኩስ ከየት የመነጨ መነሻና ማመሳከሪያውስ ምንድነው? ማለታችን አይቀርም፡፡
    ሁለተኛው ኢትዮጲያ የምትባል ሀገር ከሌሎች ሀገሮች ሁሉ ተለይታ ለማርያም በአስራትነት የምትሰጥበት ምክንያት በእግዚአብሄር ዘንድ ምንድንው? ይህን የሚያክል የአምላክ የቃል ኪዳን ነገር ካለስ በየትኛው የመፅሀፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ ተፅፏል? እውን ድንግል ማርያም በእግዚአብሄር ከሴቶች ተለይታ የተመረጠችበት አገልግሎቷ አምላክን በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት እንድትፀንስ እንጂ ሀገሮችን እንድትጠብቅና እንድታስተዳድር ነውን? የመጠበቅ ነገር ከተነሳስ በእግዚአብሄር ትእዛዝ ጥበቃና ከለላ የማድረግ ስራ የተሰጠው ለመላእክት ነው ወይስ ስጋ ለባሽ ለሆኑ እንደ ድንግል ማርያም ላሉ ፍጡራን ነው ? የሚሉ ማለቂያ የሌላቸው ጥያቄዎች መልስ ይፈልጋሉ፡፡ መልስ ካለም የዋናው ታሪክ ምንጭ መፅሀፍ ቅዱስ እንደሆነ ሁሉ ለእነዚህም ጥያቄዎች መልስ የሚጠበቀው ከዚሁ ቅዱስ መፅሀፍ ብቻ ይሆናል፡፡
    ለመሆኑ የታሪኩ ምንጭ የሆነው መፅሀፍ ቅዱስ ስለ ማርያም ስደት ምን ይላል?፡፡ የማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 2 ሙሉውን ማንብብ አስፈላጊ ነው፡፡
    በአጭሩ ግን

    ReplyDelete
  4. ኢየሱስ በተወለደ ጊዜ ይሁዳ እስራኤልን በቅኝ ግዛትነት ያስተዳድር የነበረው ሄሮድስ የተባለው የሮም ንጉስ ወደፊት ተቀናቃኝና አይሁዳዊ ንጉስ የሚሆን ወንድ ልጅ እንደተወለደና ከሩቅ ሀገር ተነስተው ኮከብ ቆጣሪ የሆኑ ሰዎች ሊሰግዱለት እንደመጡ ሲሰማ በመቆጣት ህፃኑ ከተወለደበትና ካለበት አስፈልጎ ለመግደል አሰበ፡፡ ይህንን የሄሮድስን የውስጥ ሀሳብ ደግሞ ያወቀ ማንም ሳይሆን እግዚአብሄር ብቻ ነበር፡፡ ስለዚህም እግዚአብሄር በመልአኩ አማካይነት ለማርያም እጮኛ ለዮሴፍ በህልም ታይቶ “ ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ፥ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ፥ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው።” ስለዚህም ዮሴፍ እንደታዘዘው ፈፀመ፡፡ ይህ የዮሴፍና የቤተሰቡ ስደት በአጋጣሚ የሆነ ሳይሆን አስቀድሞም በነቢያት የተነገረው ይፈፀም ዘንድ እንደሆነም ለማሳየት “ ልጄን ከግብፅ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብፅ ሄደ፥ ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ።” ይለናል ቅዱስ ማቴዎስ፡፡ በመቀጠልም ሄሮድስ ብዙ ወንድ ህፃናትን ቢፈጅም ኢየሱስን ሊያገኝ አልቻለም፡፡ ይህ ንጉስ ሄሮድስም ሞቶ በፈንታው ልጁ ሲተካ ኢየሱስን ለመግደል የመፈለጉ ጉዳይ ስላበቃ እንደገና የእግዚአብሄር መላእክ ዮሴፍ ካለበት በህልም ተገልፆ ወደ ሀገሩ እንዲመለስ አዘዘው፡፡ “ሄሮድስም ከሞተ በኋላ፥ እነሆ፥ የጌታ መልአክ በግብፅ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሣ፥ ሕፃኑን እናቱንም ይዘህ ወደ እስራኤል አገር ሂድ አለ፡፡እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን ያዘና ወደ እስራኤል አገር ገባ፡፡” የሚል ቃል በቃል እናነባለን፡፡
    እንግዲህ ይህ ታሪክ በግልፅ የሚያሳየው ዮሴፍ ከእስራኤል የመሸሹንም ሆነ የመመለሱን ትእዛዝ የተቀበለው ከጌታ መልአክ በህልም ነው፡፡ ለዮሴፍ የተሰጠው ትእዛዝም በግልፅ እንደሚያሳየው ወደ ግብፅ እንዲሸሽ ሌላ ተለዋጭ ትእዛዝ እስከሚመጣም በዚያው በግብፅ እንዲቀመጥ ነው፡፡ እንግዲህ ወደ ኢትዮጲያ ጉዳይ ስንመጣ ዮሴፍ ይህንን የእግዚአብሄር ትእዛዝ ጥሶ ነው ወደ ኢትዮጲያ እጮኛውን ማርያምንና ልጇን ኢየሱስን ይዞ ወደ ጎንደር ዋልድባ ገዳም የመጣው? እንደታዘዘው በግብፅ እንዳይቀመጥ የከለከለው ነገርስ ነበር? በማን ትእዛዝስ ነው ወደ ኢትዮጲያ የሄደው? በህልም የስደቱን ትእዛዝ የሰጠው መልአክ ወደ ዋልድባ እንዲሄድ ሌላ ያሳየው ህልም ነበር? በወቅቱ በነበረው የመጓጓዣ ዘዴ በፈረስና በአህያ በጋሪ ወይም በእግር ከእስራኤል ወደ ግብፅ ለመሄድና እንደገና ለመመለስ ስንት ጊዜ ፈጀባቸው? ኢትዮጲያ ለመምጣትና ለመመለስስ ስንት ጊዜ ይፈጃል? ለመሆኑ በግብፅ ለምን ያህል ጊዜ ተቀመጡ ንጉሱ ሄሮድስስ የሞተው ከስንት ጊዜ በሁዋላ ነው? ቅዱስ ማቴዎስ ይህንን ሁሉ የስደት ታሪክ በዝርዝር ሲፅፍ በመሀከል የገባውን የኢትዮጲያን ጉዞ በአንድ አረፍተ ነገር እንኳ ያልፃፈልን ሳያውቀው ቀርቶ ወይስ ወረቀትና ቀለም አንሶት ወይስ ዮሴፍ የመልአኩን ትእዛዝ ጥሶ ሌላ ሶስተኛ ሀገር መሄዱ እንዳይታወቅ ለመደበቅ ሲል ነውን ሄሮድስ እስኪሞት ድረስ በዚያ (በግብፅ) ኖረ ብሎ የፃፈልን ? የሚሉና ሌሎች በርካታ ጥያቄዎችን ማንሳት የሚቻል ሲሆን በዋናነት ግን “ --- እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው።” እንደገናም “ --- ወደ ግብፅ ሄደ፥ ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ።” የሚሉትን ቃለ እግዚአብሄርን በሚሽርና ከመፅሀፍ ቅዱስ ጋር በሚጋጭ መልኩ ድንግል ማርያም በስደቷ ጊዜ ወደ ኢትዮጲያ መጥታ ነበር የሚለውን በመፅሀፍ ቅዱስ ውስጥ ያልተፃፈውን ታሪክ የፈለሰፉና ይህንንም አፈታሪክ ተቀብለው ለዘመናት በየመድረኩ ያስተማሩና የሚያስተምሩ ሰዎች ግልፅ የሆነ ምላሽ መስጠት ወይም የሀሰት ትምህርታቸውን ማቆም ይጠበቅባቸዋል፡፡
    ወደ ማጠቃለያው ስንመጣ ይህ የድንግል ማርያም በስደቷ ጊዜ የዋልድባ ጉዞና ጉብኝት ፈፅሞውኑ አፈታሪክ እንጂ ቅንጣት ታህል እውነታ የሌለው በታሪክ የጊዜ ቀመርም ሆነ በመፅሀፍ ቅዱስ ሊመሰከሩ ከማይችሉ በርካታ ተረቶች አንዱ ሲሆን ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሚነገረውን “ኢትዮጲያ በአስራትነት ለማርያም የተሰጠች የአደራ አገር ነች” የሚለው ሞቅ ያለ ጣፋጭ ታሪክ ሀሰት አለመሆኑን ቃለእግዚአብሄርን በመጥቀስ የሚያስተምሩ አባቶችንና የሀይማኖት አዋቂዎችን ለመስማት እንጓጓለን፡፡
    ለመሆኑ በአለም ላይ የርስ በርስ ጦርነት የማያውቃቸው፣ ረሀብና እርዛት የማያውቃቸው፣ የተፈጥሮ አደጋና የጠላት ወረራ ያልነካቸው ክርስትና ሀይማኖታቸውን ጠብቀው በላምና በደስታ የሚኖሩ በርካታ ሀገሮች እንዳሉ ያውቃሉ? ስለዚህ የድንግል ማርያም የኢትዮጲያ ጠባቂነት ያመጣው ነገር ምን ይሆን ኢትዮጲያ ከጥንት ጀምሮ ታሪኳ የጦርነት የረሀብና የእርዛት የእርስ በርስ አለመከባበርና መተላለቅ፣ በየዘመኑ የድንበር መጥበብ የሚያጋጥማት፣ መንግስትና ህዝብ እንደ አይጥና ድመት የሚተያይበት አይደለምን? እስኪ ከሌላው የአለም ሀገር የተለየና ሌላው ህዝብ የሌለው እኛ ግን የተትረፈረፍንበትና የምንኮራበት ምን መልካም የሆነ ነገር አለን? የምንቆጥረው ነገር ካለ ይነገረንና ይህ ከድንግል ማርያም ጥበቃ የተነሳ ያገኘነው ነው እንበል እስኪ፡
    ኢትዮጲያ የክርስቲያን ደሴት በመሆኗ ክርስትናዋ እንዳይደፈር ነው የድንግል ማርያም ጠባቂነት ያስፈለጋት ከተባለ ለመሆኑ የጠባቂነት አደራ የተሰጣት መቼ ነበር የክርስትና ሀይማኖት ስጋት የሆነው እስልምና ሀይማኖትስ የተፈጠረው መቼ ነበር የሚለውን ማየት ያስፈልጋል፡፡

    ReplyDelete