Monday 21 October 2013

ለምን ከደካማው ጋር?



   የሰማዩን አለም ቅዱስና ፍጹም ያደረገው በዚያ ያሉ ሁሉም ለስሙና ለፈቃዱ ብቻ ስለሚገዙ ነው፡፡ በቀንና በሌሊት ሳያርፉ የሰማዩን ዓለም በምስጋና ችቦ የሚያፈኩት በፊታቸው የተገለጠች በጎ ፈቃዱን መቀደስ ምግባቸው ፣ማመስገን እረፍት ሆኖላቸው ነው፡፡በእርግጥም የእግዚአብሔር ፈቃዱ በሰማይ የተገለጠች ናት፡፡"ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነችእንዲል ታላቁ የህይወት መዝገብ፡፡(ማቴ.6÷10)
          ምድር ግን መልካምነትና በጎነት የበዛበት ይህን ፈቃዱን ፣ከማለዳ እስከማለዳ የተዘረጋ ቅዱስ ምሪቱን በኃጢአትዋ ከመካከልዋ አሰደደችው፡፡ስለዚህም በክፉዎችና በአስጨናቂዎች ተያዘች፡፡ህይወት የደገሰላትን ትልቁን ጌታ ትታ ሞት የሠረገላትን ተራ ባርያ ዲያብሎስን ሰምታ እንዲያስጨንቃት በላይዋ ሾመችው፡፡ስለዚህም ሲቻለው በግልጥ አልያ ደግሞ የተለያዩ መንገዶችን በመጠቀም ለክፉ ሐሳቡና ምኞቱ ያጠምደናል፡፡
       እኛ ክርስቲያኖች የጌታ ፈቃድ ብቻ የነገሰባትን ያቺን የጽዮን ተራራ ለመውረስ የምንጓዝ የዘወትር መንገደኞች ነን፡፡በተሰፈረ እድሜ የማይሰፈርና መጠኑና ይዘቱ ሊለካ የማይቻለውን በረከትና ህይወት ለመውረስ በቀንና ማታ የምንቃትት ነን፡፡ክፉ ገዢ ካለባት ከዚህች ምድር ወደሚያሰማራን ጌታ ለመጓዝ  የምንፋጠን ፣በተስፋ የምንናፍቅ ደጅም የምንጠና ነን፡፡
     ከሁሉ ይልቅ ደግሞ አንድ ትልቅ እውነት ተረድተናል፡፡ጠላታችን መናፍስት መሆናቸውንና ተግዳሮታቸውም ውስብስብ መሆኑን፡፡ደግሞ አለሙ ሁሉ በክፋት እንደተያዘም በሚገባ እናውቃለን፡፡ (1ዮሐ.5÷19) ስለዚህም ሰልፋችንና ውጊያችን ከአጋንንትና ከጨለማው አለም ገዢዎችና አለቆች ጋር ነው፡፡ ከሥጋና ከደም ጋር ሳይሆን ከነዚህ በዓይን ከማይታዩ አዕላፍና ልምድ ካላቸው መናፍስት ጋር ነው፡፡(ኤፌ.6÷12)

       ይህን የምለው ግን ገና በደካማው በደልና ኃጢአት ላይ ለሚያሽሟጥጡ፣ኃጢአተኛው ላይ ደቦ ጠርተው እንውገረው ፣ኃጢአቱ ትልቅ ነውና በፌስቡክናበሌላም መንገድ እንግለጠው የሚሉትን የአምልኮ መልክ ያላቸውን "ክርስቲያኖች" አይደለም፡፡ ኃይሉን ሳይክዱ፣ዝቅ ዝቅ ብለው ከዋናው ጠላታቸው ጋር የሚዋጉትን ብርቱ አማኞችን ነው፡፡
     አዎ! አብዛዎቻችን ኃጢአትን ከራሱ ከሚያመነጨው፣ሐሰትን ከራሱ ከሚናገረው ጋር እንደምንዋጋ ገና በውል ያልተረዳን ነን፡፡ ጠላታችን ምድርን ሊገዛና ሊያረክስ እኛንም የክፋቱ ፍሬዎች ሊያደርገን ከጥልቁ ተማምሎ የወጣ ነው፡፡ በዚህም የብዙ ዓመታትን የጥበብ ልምድ ያካበተ ነው፡፡ከወደቀውና ኃጢአትን ሰርቶ ከረከሰው ሰው ጀርባ ያለውን ዋና ጠላት ማየት ካልቻልን የውጊያውን አድራሻ ስተናል፡፡
      ውጊያችን ከሥጋና ከደም ጋር አይደለም ማለት ኃጢአትን ከሚሰራው ከሸክላው ጋር ሳይሆን ከአሰሪው ጋር ነው ማለት ነው፡፡ያ ደግሞ ጠላት ዲያብሎስ ነው፡፡ እርሱ ደግሞ በፈንጂ፣በመትረየስ ፣በተጨበጠ ቦክስ፣በማውገዝ፣ በዕውቀት …  የሚርቅና የሚሸነፍ አይደለም፡፡ ጠላታችን ሳይታክት የሚዋጋን እኛ ደግሞ በመታከትና በድካም የተከበብን ፣እርሱ አልቦ ሥጋ የማይታይ እኛ ግን ሥጋ ለባሽና የምንጨበጥ ነን፡፡ ያልተመጣጠነ ፍልሚያ!!!
       እንኪያስ አንድ ነገር ይገለጥ፡፡ ውጊያው በእኛ አድራሻ ሳይሆን በጠላታችን አድራሻ ፤ስፍራውም በሰማያዊ ስፍራ ነው ማለት ነው፡፡ጠላታችን አይታይም ስለዚህ የማይታይ ጦር ያስፈልገናል፣ጥበበኛና የማይታክትም ስለሆነ የጥበብ ቃልና የማይታክት መንፈስ ያስፈልገናል ማለት ነው፡፡መናፈቁንና እረፍቱን በእግዚአብሔር ገነት ከክርስቶስ ጋር ያደረገና እንደሆነም የተገለጠለት አማኝ እውነቱን እንዲህ ነው የሚረዳው፡፡ የማይታይ ጦር የእግዚአብሔር ቃል፣የማይጠፋ ቀንዲል የመንፈስ ቅዱስ ብርሐን፣ የማያስደፍር ቅጥር ድንቁ የመስቀል ሥራና ደሙ ያስፈልገናል ማለት ነው፡፡ ከሁሉ በላይ ሳያቋርጡ፣ ሳይታክቱ፣ዘወትርና ተግቶ መጸለይን ባለመርሳት፡፡
      ኃጢአተኛን ወደእግዚአብሔር መማረክ የሚቻለው ኃጢአቱን በመንቀስ ሳይሆን የኃጢአቱን አመንጪ ከኋላው ያለውን ያን ክፉ ቀድሞ በማስደድና በማሰር ነው፡፡ የሰውን ድካም አይተን በድካሙ  መፍረድና መናቅ ከጀመርን ወደንስሐ የምትመራዋን የጌታን የትዕግስቱን መጠን እየናቅን በጠላት አሰራር ሰው እንዲሞት እየሻትን ነው ማለት ነው፡፡ይህ ታዲያ ከእግዚአብሔር ነውን?እና በምህረቱ ከተያዝን በምረቱ የተያዘውን ስለምን እንንቃለን?ስለምንስ ፍርድን እንለምናልን?ከዚህ ይልቅ ስለምን በኃጢአቱ የጣለውን የሁላችንን ጠላት በክርስቶስ ጽድቅ በመቃወም አንማልድለትም?
       አብያተ ክርስቲያናት ይህ ጥበብ የተሰውረባቸው ይመስላል፡፡ ዜመኞችና የዜማ መሳሪያዎች፣ ማስታወቂያና ሞንታርቦዎች ፣አስገምጋሚ ድምጽና የታወቁ ሰባኪዎችን መጋበዝና ጉባኤ ማዘጋጀት የኋላ ሥራ እንጂ ፊተኛው ሥራ "ክፉውን ማሰር" እስከክብራችን ዙፋን እየተከተለ የሚከሰንን ከሳሽ ጠላት ድል መንሳት ነው፡፡
       ነብሳትና ለመማረክ ቀድሞ የታሰሩበትን እስራት መፍታት ፣ትብታቡን መበጣጠስ ያስፈልጋል፡፡ያ ደግሞ ከልምድና መንፈስን ከማይነካ የጸሎት ህይወት በመውጣት ጠላታችንን ለዘወትር ከእግራችን በታች ከሚያስገዛልን ጌታ ፊት በመዋረድና በእምነት በምልጃና በልመና ስንቃትት ነው፡፡የዚያኔ እኛ በእምነት ስንበረከክ ጌታ በድል ይቀድመናል እኛ ደግሞ ምርኮ ለመሰብሰብ እንነሳለን፡፡ቀድሞ ግን ጌታ እንዳስተማረን አሳሪውን እንሰር፡፡
    " … ወይስ ሰው አስቀድሞ ኃይለኛውን ሳያስር ወደ ኃይለኛው ቤት ገብቶ እቃውን ሊነጥቀው እንዴት ይችላል? ከዚያም ወዲያ ቤቱን ይበዘብዛል።"(ማቴ.12÷29)
    መድኃኒታችን ሆይ በሰማይ ያለች ፍጽምት ፈቃድህ ለአንተ መገዛትን ታስተምረን፡፡ በደካማው ከሚፈርድም ክፉ ሐሳብ መከልከልን ጥበብህ ትምራን፡፡አሜን፡፡

   


No comments:

Post a Comment