Thursday 9 February 2017

ከኢየሱስ ተኮር - ወደ “አገልጋይ[ስጦታ]” ተኮር ሩጫ (ክፍል አራት)

Please read in PDF
2. ራተኛ(አገልጋይ) ባሪያ “ባሪያ ተገዥ፤ አገልጋይ ሰው የተማረከ ወይም የተገዛ ግዝ፤ ውላጅ፡፡ …” [1] በማለት ይተረጉሙታል አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፡፡ “ነጻነትና መብት የሌለው፥ በራሱ ፈቃድ የፈለገውን ማድረግ የማይችል፡፡ በመጀመርያ እግዚአብሔር አንዱን ለሌላው ባሪያ እንዲሆን አድርጎ አልፈጠረም፡፡ ቃሉ ለመጀመርያ ጊዜ በስካር ኃጢአት ከወደቀው ከኖኅ አንደበት ተገኘ፤ ዘፍ.9፥26፡፡” [2]
   ቃሉ በመርገም መልክ ለካም ልጅ ለከነዓን የተነገረ ነው፤ እርግማኑ ከባድ ከመሆኑም ባሻገር እግዚአብሔርን የማይወዱ[ለፈቃዱ የማይታዘዙ] ሁሉ የሚደርስባቸው እርግማን ነው፡፡ የራስን ወላጅ ሆነ የዘመድን ኃፍረተ ሥጋ መመልከት አጸያፊና ነውር ነውና፤ (ዘሌ.18፥4-17) ይህን ያደረገው ከነዓን የባርነቱም እርግማን በትክክል ደርሶበት አይቶታል፤ (ኢያ.16፥10)፡፡ ከዚህ በኋላ በባርነት መያዝና በዚያ መኖር የኃጢአት ውጤት አንዱ መገለጫ ሆኗል፡፡ ለዚህም የእስራኤል ልጆች በመሳፍንት ዘመን በአረማውን እጅ በተደጋጋሚ መውደቃቸውንና በባቢሎንም መማረካቸው በቂ ምስክር ሆኖ በመጽሐፈ መሳፍንት ተጽፎ አለ፡፡

     በዓውዳዊው ፍቺው ከመርገም ጋር በቀጥታ የተያያዘ ቢሆንም፣ በኋላ ላይ ትሁታን የጌታ አገልጋዮችም ፍጹም ፈቃዳቸውን ሰጥተው ለጌታ እግዚአብሔር በመታዘዛቸው ምክንያት በስሙ ተጠርተዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን በዚህ ስም የነዌ ልጅ ኢያሱ(ኢያ.24፥29)፣ ነቢዩ ሳሙኤል(1ሳሙ.3፥10)፣ ንጉሥ ዳዊት(2ሳሙ.3፥18)፣ ቴስብያዊው ኤልያስ (2ነገ.9፥36) እንዲሁም አባታችን አብርሃምና ከአዲስ ኪዳን ድንግል ማርያም በዚህ ስም ራሳቸውን ጠርተዋል፤ (ዘፍ.18፥3 ፤ ሉቃ.1፥48)፡፡
   ባርያ መሆን በጌታና በሐዋርያት ዘመን ሰዎች ለባርነት ይሸጡ ነበርና፣ እንግዳ ነገር አልነበረም፤ ማለትም እጅግ የታወቀ ነገር ነበር፡፡ [3] ይህ ማለት ግን ክርስትና ባርነትን ይደግፋል ማለት አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ጌቶች ባሮችን(ሠራተኞችን) እንዳያስጨንቁ፣ ባሮችም ነጻ ከወጡ በኋላ እነርሱም በተራቸው ጌቶች ሲሆኑ፣ የሚያሠሯቸውን ባሮች እንዳያስጨንቁና ባሮችም ለአሠሪዎቻቸው በአገባቡ እንዲታዘዙ እንጂ ፈጽመው እንዳይገዙላቸው መጽሐፍ ቅዱስ በማያሻማ ቃል ይናገራል፤ (1ቆሮ.7፥21-23)፡፡
   በክርስትና ሕይወት ሩጫ አገልጋይም በብዙ መልኩ ለጌታው የሚገዛ ነው፤ ይኸውም፦
1.     አገልጋይ የጌታውን ዓላማ ባያውቅ እንኳ ትእዛዙን ከመፈጸም ፈጽሞ ቸል አይልም፤ ጌታችን፣ “ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና” (ዮሐ.15፥15) እንዳለው፣ ባርያ ጌታው ለምን እንዳዘዘው እንኳ መጠየቅ አያስፈልገውም፤ ጌታው ላዘዘው ቃል በእሺታ ከመታዘዝ በቀር፡፡
     በደሙ ከገዛን ጌታ ኢየሱስ የተነሣ ሁላችን ሎሌዎች ነን(ሮሜ.1፥1 ፤ 1ቆሮ.6፥19 ፤ 7፥23)፤ የሆንነውም በክርስቶስ በመስቀል ላይ ከተደረገልን ትልቅ ዘላለማዊ ቅዱስ ፍቅር የተነሣ ነው፡፡ ለዚህ ውድ አገልጋይነት የበቃን ሆነን እንድንገዛ የተከፈለልን ትልቁ ዋጋ፣ የክርስቶስ ደም ነው፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ አገልግሎትን በተመለከተ ሁላችን ባሮች ነን፤ ምን እንደምንሆን ወደፊት ባይገለጥልን እንኳ (1ዮሐ.3፥2)፤ ለጌታ ኢየሱስ ከመታዘዝ ፈጽሞ ቸል አንልም፡፡ ፈቃዳችንም ሆነ ስሜታችንና ሁለንተናችን ሁሉ ለሞተልንና ለወደደን ጌታ ነውና፣ በፍጹም ልባችንና ኃይላችን ውጤቱ እንኳ ምንም ቢሆን ላዘዘን ቃሉ ፈጽመን መታዘዝ ይገባናል፡፡
     ወደፊት ምን እንደሚገጥመን ባናውቅም፣ ለክርስቶስ ታማኝነታችን ምንም ወደር የለውም፤ ብንሞትም ብንኖርም እርሱን ብቻ እንሰማዋለን፤ እንታዘዘዋለንም፡፡ ለክርስቶስ መታዘዛችንን ልናሳይ የሚገባን በባርነት ይገዛን ለነበረው ኃጢአት፣ ፍጹም በመቃወም ወይም አለመታዘዛችንን በማሳየት ነው፡፡ የኃጢአት ኃይል ልክ “እንደሰው” ባርያ አድርጎ የመግዛት አቅም አለው፤ (ሮሜ.6፥14)፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስ ከኃጢአት ባርነት ነጻ እንዳወጣን እንዲሁ፣ በኃይሉ ሊገዛን ከሚታገለን ከኃጢአት “ኃይለኛም” በሁሉን ቻይነቱ ያድነናል፡፡
      ከባርነት ነጻ የወጣነውና ነጻ የሆንነው ለኃጢአት ሳይሆን እግዚአብሔርን እናገለግል ዘንድ ነው፤ (ገላ.5፥13)፡፡ ስለዚህም ለኃጢአት ባሪያ ሆነን እንዳንገኝ እንጠንቀቅ፤ ኃጢአትን የሚሠራ ሁሉ ለዚያ ለሚሠራው ነገር ባርያ ነው፤ “ኢየሱስ መለሰ፣ እንዲህ ሲል፦ እውነት እውነት እላችኋለሁ፣ ኃጢአት የሚያደርግ ሁሉ የኃጢአት ባርያ ነው፤”(ዮሐ.8፥34)፡፡ ከእንዲህ አይነት ባርነት ማንም በራሱ መዳን አይችልም፡፡ እውነት የሆነ ኢየሱስ ብቻ አርነት ያወጣል፡፡
   በቃና ዘገሊላ ሠርግ ቤት የነበሩ አገልጋዮች፣ ለዚህ ሃሳባችን እጅግ ቅርብ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ” ባለቻቸው ጊዜ፣ አገልጋዮቹ ከትእዛዙ አንድም ሳያጐድሉ እንደነገራቸው አደረጉት፡፡ ውኃው ምን እንደሚሆን ባያውቁም ከቃሎቹ አንድስ እንኳ አላጐደሉም፡፡ አገልጋዮቹ በእያንዳንዱ እርምጃ ፍጹም ታዛዦች ነበሩ፤ ለምን? የሚል ሙግት ፈጽሞ እንዳልነበር ከአገልጋዮቹ ተግባራዊ ምላሽ እናስተውላለን፡፡ ጌታ አድርጉ ባለን በየትኛውም ትዕዛዞቹ እንታዘዘዋለን፤ ውኃውን ወደጋኖች መጨመር ቀላል ሊመስል ይችላል፤ የሠርጉን ወይን ጉድለት ይመላል ብሎ መጨመር ግን የሚታዘዝና የእምነት ልብን ይጠይቃል፡፡
      ለሚያዛችሁ ጌታ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለመታዘዝ ዝግጁ ናችሁ? ታማኝና እውነተኛ ባርያዎች መሆናችሁ አንዱ መለኪያው ላዘዛችሁ የትኛውም ቃሎቹ የምታሳዩት ፈቃደኝነታችሁ ነው፤ ብዙዎቻችን በግልጥ ለታዘዝነው ቃሎቹ ታማኞች አይደለንም፡፡ እንዲያውም በግልጥ ለታዘዝነው ካለመታመናችን አልፈን፣ ከክርስትና ጠባይ ለማይገጥሙ ድርጊቶች ራሳችንን ስናዘጋጅ እንስተዋላለን፤ ብዙ ጊዜም መጠጣት ይፈቀዳል ወይስ አይፈቀድም? “እንትን” ማድረግ ፍቅድ ነው ወይስ ክልክል? የሚሉ ሙግቶችን የምናሰማው ትክክለኛ ባሮች ሆነን የጌታችንን ጠባይ በትክክል ካለመረዳት ጭምር ነው፡፡ እናውቀዋለን የምንለውን ጌታ ድርጊታችን ግን ፈጽሞ የማያውቀው መሆኑን ያሳብቅብናል፡፡ እንዲያውም ብዙዎቻችን ከኢየሱስ ቃሎች ይልቅ ትዝ የሚለንና የምንታዘዘው “ዋና የምንላቸውን መምህራኖቻችን ቃልና ትእዛዝ” ነው፡፡  
2.    አገልጋይ በነገር ሁሉ ተግቶ ጌታውን እንደሚያገለግል (ኤፌ.6፥7 ፤ ቈላ.3፥23)፣ ክርስቲያን አገልጋይም በሥራ ሳይታክት እንደሚደክም ገበሬ ነው፤ (2ጢሞ.2፥6)፡፡ ለፍሬ መትጋት ይገባል፤ መከርን እጅ ዘርግቶ ለመቀበል አስቸጋሪውን የክረምት ወቅት በትዕግስት ማለፍ ይገባናል፡፡
   ገበሬ በእርሻ፣ በጉልጓሎ፣ በዘር፣ በአረም ማረም፣ በኩትኳቶና በሽልሻሎ፣ በአጨዳና በክማሮ … ዘመኑ እጅግ ትጉህ ነው፡፡ ይህን ሁሉ በዘመኑ ሁሉ ሳይታክት ያደርገዋል፡፡ እኒህን ሁሉ ሳያደርጋቸው ቢቀር መልሶ ማስተካከል እጅግ አደገኛ ነገር ነው፡፡ አረም ማረም ባለበት ዘመን ዝም ብሎ፣ ለአጨዳ ቢመጣ ምናልባት የዘራውን ዘር ሳይሆን በአረም የተወረሰ ዳዋ ሆኖ ሊጠብቀው ይችላል፡፡ አገልጋይም ስለልፋቱ ምንም ሳይቆጥር የታዘዘውን ደግሞ ደጋግሞ ያደርገዋል፡፡ ሳይታክቱና ሳይሰለቹ ማድረግ ትጋትን የሚጠይቅ ጉዳይ ነው፡፡
    አለመትጋት ለስልቹነትና ለታካችነት፤ ለዝንጉነትም ራስን ማጋለጥ ነው፤ ለዚህም ነው የእግዚአብሔር ቃል፣ “የታካች ሰው ነፍስ ትመኛለች፤ አንዳችም አታገኝም፤ የትጉ ነፍስ ግን ትጠግባለች” (ምሳ.13፥4)፤ “ታካች ሰው በብርድ ምክንያት አያርስም፤ ስለዚህ በመከር ይለምናል፥ ምንም አያገኝም”(ምሳ.20፥4) በማለት በግልጥ የሚናገረን፡፡ በአለመትጋት ስንፍናችን የገዛ ስሜታችን ባሮችና አገልጋዮች እንዳንሆን፣ በእግዚአብሔር ሥራ የበረታን ትጉሃን ልንሆን ይገባናል፡፡
     ስለዚህም ለእግዚአብሔር ሥራ ትጉሃን መሆን ይገባናል፤ ትጉህ አገልጋይ፣ “በምድርም በሕይወት በሚኖርበት ዘመን ሁሉ እግዚአብሔርን መፍራት ይማር ዘንድ፥ … ሕጉንና ትዕዛዙን እንዳይረሳ፥ በሕይወቱም ዘመን ሁሉ ከልቡ እንዳይወድቅ ይጠነቀቃል፣ ነፍሱንም በትጋት ይጠብቃል፤ ለልጆቹም ለልጅ ልጆቹም ያስታውቃል፤” (ዘዳግ.4፥9)፤ በአምልኮና በመልካም ሥራ እጅግ ይተጋል (ሐዋ.26፥7 ፤ 2ቆሮ.8፥16)፤ እንዲያውም አንድ አገልጋይም ይሁን አማኝ መዳኑን ማወቅና ማስተዋል የሚቻለው በዚያው መዳኑ ጸንቶና ተግቶ ሲገኝ ነው (ዕብ.6፥11)፤ “ … ትጋትን ሁሉ እያሳየ በእምነቱም በጎነትን ሊጨምር … እግዚአብሔርንም በመምሰል የወንድማማችን መዋደድ፥ በወንድማማችም መዋደድ ፍቅርን ሊጨምር ይገባዋል” (2ጴጥ.1፥6)፡፡
   ስንቶቻችን ለቅዱስ ወንጌሉ ሥራ ባለመታከት የምንሠራ ነን? ከወንጌሉ ይልቅ የምንተጋለት “ሌላ ሥራ” የለን ይሆን? እንዲያውም በኑሯችን ካሰማራን ጌታ የተሻለ ኑሮ ለመኖር የምናስብ ባሮች አልሆንን ይሆን? ዓለም ጌታችንን ሰቅላ ሳለ፣ እኛ ግን ከጌታ ይልቅ የተሻለ ሥፍራ ለማግኘት የምንከራተት ምስኪን አገልጋዮች ሳንበዛ አንቀርም፡፡ አገልጋይ ሆይ! ፊትህን ወደጌታህ አቅና!
ጌታ ማስተዋሉን ያብዛልን፤ አሜን፡፡
ይቀጥላል …




  [1]  ኪዳነ ወልድ ክፍሌ/አለቃ/፤ መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ፡፡ 1948 ዓ.ም፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት፡፡ገጽ.297
   [2] የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 6ኛ እትም፤ የኢትዮጲያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር [ቄስ ኮሊን ማንሰል]፤ 1992 ዓ.ም፤አዲስ አበባ፤ ባናዊ ማተሚያ ቤት፤ ገጽ.108
    [3] እንዲያውም በዚያ ዘመን ሰዎች እንደዕቃ ወይም እንደከብት በገበያ ቆመው ይሸጡ፤ ይለወጡ ነበር፡፡ እኛም ያለጥርጥር በክርስቶስ በከበረው ደም ተገዝተናል፡፡

4 comments:

  1. መልካም ደስ የሚል እይታ ነው በርታ ወንድማችን

    ReplyDelete
  2. werke sehuf new.

    ReplyDelete
  3. ይህ ሰው በጣም አስተዋይ ጸሀፊ ነው። ጌታ ይባርክህ አቦ

    ReplyDelete
  4. ልክ ብለሃል ፀሐፊው ጌታ ይባርክህ

    ReplyDelete