Friday 17 July 2015

ክርስቶስን በሚያባብል ቃል ለምን? (ክፍል ሦስት)

      
                            Please read in PDF

      የሐሰት መምህራን እውነትን ጨክኖ በመናገር ከሚመጣ መከራና ስደት ይልቅ (2ጢሞ.3፥12)፤ እውነትን ከሐሰት ጋር ሸቃቅጦ በመናገር የሚገኘውን ሥጋዊ ጥቅምና የሚከተላቸው የበዛ ቁጥር ሊኖር እንደሚችል በሚገባ ያውቃሉ፡፡ ሙሴ ከላካቸው አሥራ ሁለት ሰላዮች ፥ አሥሩ ይዘው የመጡትን የሐሰት ወሬ ሰምተው ሕዝቡ ሁሉ ተገልብጠዋል፡፡ ለብዙ ዓመታት ከመራቸው እግዚአብሔርና ሙሴ ይልቅ አሥሩን ወዲያው ተቀበሏቸው፡፡ (ዘኁል.14፥2) “የእስራኤልም ልጆች ሁሉ በሙሴና በአሮን ላይ አጕረመረሙ ማኅበሩም ሁሉ፦ በግብፅ ምድር ሳለን ምነው በሞትን ኖሮ! ወይም በዚህ ምድረ በዳ ምነው በሞትን ኖሮ! እግዚአብሔርም በሰይፍ እንሞት ዘንድ ወደዚች ምድር ለምን ያገባናል? ሴቶቻችንና ልጆቻችን ምርኮ ይሆናሉ ወደ ግብፅ መመለስ አይሻለንምን?” ብለው እስከመካድ የደረሱት ከሐሰት መምህራን አባባይ ቃል የተነሳ ነው፡፡

      ሐሰት ለጊዜው ሲያሸንፍ ከተከታዮቿ ብዛት የተነሳ ጉልበቱ ትልቅ ይመስላል፡፡ መሪዎቹም የቁጥሩን ብዛት አይተው በትዕቢት ይነፋሉ፡፡ (ሐዋ.12፥5) በብዛታቸው ተመክተው እውነተኞችን ለማጥፋት ሙሉ ኃይላቸውን ይጠቀማሉ ፤ ነገር ግን እውነት በሁኔታዎች መካከል እንኳ ያው እውነትነቷን ሳትለቅ የኃያላንን ጉልበት ሽራ ጸንታ ትኖራለች፡፡
     የክርስቶስንም ወንጌል የማይሰብኩ ወይም በማባበል ቃል የሚሰብኩ ብዙ አገልጋዮች በሞት ተወራርደው የሚሟገቱላቸው የሚያሳዝኑ ተከታዮች አሏቸው፡፡ እኒህን ተከታዮች የሚያገለግሏቸው ሰዎች እንደሐናና ቀያፋ ዋናዎች ስለሆኑባቸው፥ ወንጌል ጠቅሳችሁ ለመምከር ብታስቡ “አይሳካለላችሁም”፡፡ ያኔ ሐናና ቀያፋን ሲከተሉ የነበሩቱ ኢየሱስን ሊሰሙ ባለመውደድ ይሰቀል እንዳሉ ፤ እኒህም እንኳን እናንተን ፥ ኢየሱስ እንኳ “ድንገት ቢመጣ” ጆሮዋቸውን በማከክ ሊሰሙ ፈጽመው አይወዱም፡፡
  ስለዚህም የሐሰት መምህራን በማባበያ ቃል ከማስተማር ቸል አይሉም፡፡ ለብዙዎቻችን የቁጥር ነገር ያስደነግጠናል፡፡ ከእኛ ወገን ሲበዛ ደስ እንደሚለን ማነሱም ያሰጋናል፡፡ እውነት ግን ሁኔታና የተከተዮቿ ሰዎች መብዛትና ማነስ ምንም አያስጨንቃትም፡፡ የጠላት ሽንገላም የማይለውጣት ፥ እውነት ያው እውነት ናትና!!!

2. የሐሰት ትምህርታቸውን ለማስረጽ እንዲመቻቸው

      ሰይጣን የብርሃን መልአክ የሚመስለውና መስሎም የሚገለጠው (2ቆሮ.11፥14) ዕውቅና የመቀበል ችግር እንዳይገጥመው ነው፡፡ ሰይጣን በሰይጣንነቱ ቢገለጥ የቱም ባዕለአዕምሮ ሊቀበለው እንደማይችል ስለሚያውቅ ራሱን እንደአሳቢ (ዘፍ.3፥5) አድርጎ ሲያቀርብ ፥ ሁሉን ሲያስብ የማይዘነጋውን እግዚአብሔርን ደግሞ ጨካኝና የማያስብ አድርጎ ይስላል፡፡ ስለዚህም በጎነት በሚመስል አመክንዮአዊ የስህተት ድርጊት ውስጥ ራሱን በመሰወር ራሱን ጻድቅ በማስመሰል ይቀርባል፡፡
    የሐሰት መምህራንም ከዚህ የተለየ ነገር የላቸውም፡፡ ለማበባል የሚጠቀሙት ቅዱሱን የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ማባበያውን ሲያቀርቡም “የክርስቶስን ወንጌል የሚመስል” የራሳቸውን ትምህርት በጥበብ ለማስረጽ ነው፡፡ በሚያባብል ቃል የሚያስተምሩት ትምህርት “ለዓለም ከሚመች ከከንቱ መለፍለፍ የማይርቅ፤ ኃጢአተኝነታቸውን ከፊት ይልቅ የሚጨምርና፥ ቃላቸውም እንደ ጭንቁር የሚባል” (2ጢሞ.2፥16) እንደጋንግሪን ተላላፊነቱ አደገኛ እንደሆነ በሽታ ያለ ነው፡፡

3. ለኃጢአት ዕውቅና ለመስጠት

   በሚያባብል ቃል የሚናገሩ “መምህራንና አማኞች” የመጨረሻ ግባቸው ኃጢአተኞች ሆነው ክርስቶስን ለማስካድ ሾልከው የሚገቡ ናቸው፡፡ “እያለሙ ሥጋቸውን እያረከሱ …”(ይሁ.8) “የዋጃቸውን ጌታ እንኳ ክደው የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየሳቡ የሚያጠፋ ኑፋቄን አሹልከው ያገባሉ” (2ጴጥ.2፥1) ይህ ማለት እንግዲህ የሐሰት ትምህርታቸው እንዲሠርጽና ዕውቅና እንዲያገኝ የተቻላቸውን ሁሉ ያደርጋሉ ማለት ነው፡፡
     በአንድ ወቅት ፥ የአገልጋዮችን የተገለጠ ኃጢአት በተመለከተ መሆን ስላለበት በርዕስ መልክ ይዘን ከተወሰኑ ወንድሞችና እህቶች ጋር እየተወያየን ሳለ ድንገት በቁጥር የሚያንሱ ወንድሞችና እህቶች “አገልጋይ በገዛ አካሉና ብልቱ ላይ የፈለገውን የማድረግ መብት አለው ፤ እኛ መውቀስም ፣ መቆጣትም ፣ ምንም ምን አንችልም ፤ በጠንካራ ዘመኑ ያገለገለውን ልናይ ይገባል እንጂ፥ የድካም ዘመኑን በፍጹም ልናስብ አይገባም” የሚል ሙግት አቅርበው ነበር፡፡ እኔም የዚህ ጽሁፍ ጸሐፊ በስልክና በአካል የተወሰኑ “አማኞችን” በዚህ ርዕስ ዙርያ ለማወያየት ሞክሬያለሁ፡፡ በዚህ ውይይት ውስጥ የእኒህን ልጆች ሃሳብ የሚደግፉትን ጥቂት ሰዎችንም አጊኝቻለሁ፡፡ እነዚህ ማሳያዎች ሰዎች በማባበያ ቃል የሚሰሙት ወንጌል ለኃጢአት ዕውቅና እስከመስጠት እንደሚችል አለማስተዋላቸውን ነው፡፡ 
     የሐሰት መምህራን ስብከታቸውን ለማስረጽ ይህን ያህል “ስውርና የጥበብ መንገድ” ይከተላሉ፡፡ ዛሬ ላይ የምዕራብ አብያተ ክርስቲያናት በአብዛኛው “አመንዝራነትን ፣ ቀላጭነትን ፣ ግብረ ሰዶማዊነትን ፣ ሴሰኝነትን ፣ ራስ ወዳድነትን ፣ የብልጽግና ወንጌልን … ” በመብት ሰበብ በግልጥ በየ“አውደ ምህረታቸው” መለፈፍ የደረሱት ሕገ መንግሥታቸውን ከመፍራትና ከማክበር አንጻር ብቻ ሳይሆን “ወንጌልን በጨበጡ” የሐሰት መምህራን የኃጢአት ስውር ስብከትንም ቀላቅለው በመሰበካቸውና እኒህን የሐሰት መምህራን ከመካከላቸው ማራቅ ባለመቻላቸው ጭምር እንደሆነ የዚህ ጽሁፍ ጸሐፊ ያምናል፡፡ ምክንያቱም ለመቃወምና ኃጢአት ኃጢአት ነው! ለማለት ብሎ ወደንስሐ መመለስ አለመቻል ፤ ይህን አልፎ በመጣ ጊዜ በግልጥ ተቃውመው ከዚያ ህብረትና አንድነት መለየት እየቻሉ ፥ ራሳቸውም የነውሩ ተካፋይ ሆነው በየአብያተ ክርስቲያናቸው ግብረ ሰዶማውያን አገልጋዮችን ሲሾሙና ሲያጋቡ እያየን ነውና፡፡
   አቤቱ ጌታ ሆ ይ! ዘመናችንን እንደንስር አድስልን፡፡ አሜን፡፡

    ይቀጥላል …

1 comment:

  1. Hello thgis is somewhat of off topic but I was wondering if blogs use
    WYSIWYG ediotors or if you have to manually code with HTML.
    I'm starting a blog soon but have no coding know-how so I wanted to get advice
    from someone with experience. Any hrlp would be greaqtly appreciated!


    Here is my website; Click here

    ReplyDelete