Friday 8 August 2014

ድንግል ማርያምና የአይሁድ አሽሙር(ክፍል አንድ)




    
እመቤታችን ድንግል ማርያም በጌታ ያመነች ብጽዕት ናት፡፡(ሉቃ.1፥45) ከዳዊት ቤት ወገን የምትሆን ድንግል ብላቴና(ኢሳ.7፥13) ዕድሜዋ ወጣት፣ የገሊላ ናዝሬት ወደምትሆን … “ብዙ ገሊላ አለና ከዚያ ሲለይ እንተ ስማ ናዝሬት፤ ብዙ ደናግል አሉና እንተ ተፍኀረት ለብእሲ ዘስሙ ዮሴፍ፤ ብዙ ዮሴፍ አለና ከዚያ ሲለይ ዘእምቤተ ዳዊት አለ፡፡”(ወንጌል ቅዱስ ከቀድሞ አባቶች ጀምሮ ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው ንባብና ትርጓሜው፤1997፤ ትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት፤ አዲስ አበባ፡፡) ኑሮዋም ባላመኑና በክፉዎች መካከል ቢሆንም(ሉቃ.1፥26) በእግዚአብሔር የምታምን፤ የእስራኤልን አምላክ ብቻ በመፍራት የምታመልክ ነበረች፡፡ ድንግል ማርያም ምንም መልካምነት በሌለባት ናዝሬት(ዮሐ.1፥47) የሚደነቅ መልካም ነገር ተገኝቶባታል፡፡
የመልአኩ ገብርኤል ብሥራት አጭር ቅኝት
    ወደገሊላ ናዝሬት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ተልኮ ሲወርድ፤ የሄደው ወደአንዲት፤ ማርያም ወደምትባል ድንግል ሴት ነው፡፡(ሉቃ.1፥27) ይህ ቃል እግዚአብሔር በየትኛውም ክፉ ዘመንና ሁኔታ ውስጥ የራሱ የሆኑትን ፍጹም ጠብቆ እንደሚያኖር ያሳየናል፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ጥበብ ከሰው ህሊናና ማስተዋል በላይ የሚደንቅ ነው፡፡ ቅዱስ ኤልያስ በእርሱ ዘመን ጣዖት ተስፋፍቶ ሰው ሁሉ በዓልን ይከተል ነበር፡፡ ከእርሱ በቀር ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ያለ አልመሰለውም፡፡ ነገር ግን ነቢዩ ቅዱስ ኤልያስ በማያስተውለውና በማያውቀው መንገድ እንደኤልያስ “ከእስራኤል ጕልበታቸውን ለበኣል ያላንበረከኩትን ሁሉ፥ በአፋቸውም ያልሳሙትን ሁሉ፥ ሰባት ሺህ ሰዎች ለእኔ አስቀርቼአለሁ።”(1ነገ.19፥9፤18)፤ሮሜ.11፥5) ያለ እግዚአብሔር፤ በናዝሬትም በጸጋው የመረጣትን ቅሬታ፤ ድንግል ማርያምን እናገኛለን፡፡

   መልአኩ ወደ ድንግል ማርያም ገብቶ በደስታ ሠላምታ፥ ብስራትን አሠማት፡፡ “ደስ ይበልሽ፥ ጸጋ የሞላብሽ ሆይ፥ ጌታ ከአንቺ ጋር ነው፤ አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ” አላት፡፡(ሉቃ.1፥28) ድንግል ማርያም የሠማችውን “እንዴት ያለ ሠላምታ ነው?” ብላ በልቧ ታሰላስል የነበረው በእውነተኛ ትህትና ሆና ነበር፡፡ በልብ የማሰብን ትህትና ከድንግል ማርያም በብዙ ቦታ ላይ እናገኛለን፡፡(ሉቃ.2፥19፤51) እንደሰከረ ሰው ብዙ ከመለፍለፍ ነገርን በጌታ ልብ ማሰብ የተትረፈረፈ እረፍትና ሠላም አለበት፡፡
  መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ድንግሊቱ በልቧ የምታስበውን ከመንፈስ ቅዱስ የተነሳ ያወቀ ይመስላል፡፡ ስለዚህም የብስራት ዜናውን ቀጠለ፡፡ ነቢያት በትንቢታቸው፣ አባቶች በምሳሌና በራዕይ ከሩቅ አይተው፣ እናቶች በእምነት ታግሰው የጠበቁትን ጌታ ልትወልድ እንዳላት፤ የምትወልደውንም ኢየሱስ ብላ እንደምትሰይመው፤ ልጁም ታላቅና ለመንግስቱ መጨረሻ የሌለው ንጉስ እንደሆነ” ነገራት፡፡(ሉቃ.1፥29-34) በመልአኩ አንደበት የተገለጠው የልጁ ታላቅነት፤ የሚገርምና ልብ የሚገዛ ነው፡፡ መልአኩ የረጅሙን ዘመን የትንቢትና የነቢያቱን ቃል በአንድ ጠቅልሎ በውብ አገላለጥ በአጭሩ ነበር የተናገረው፡፡ ለመንግስቱ መጨረሻ የሌለው ኢየሱስ የልዑል ልጅ ይወለዳል!!!
ካህኑ ዘካርያስና ገሊላዊት ድንግል ማርያም
     ካህኑ ዘካርያስ በቅዱሱ መቅደስ ሥፍራ ዕጣን የማጠን ሥራ ዕጣ ደረሰው፡፡ ከመቅደስ ገብቶ ዕጣን ሲያጥን፣ እግዚአብሔርንም ሲያገለግል በዕጣኑ መሠዊያ ቀኝ ቆሞ የጌታ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ታየው፡፡ የታየው መልአክ ሊወልድ እንዳለውና ልጁም “የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች የማይታዘዙትንም ወደ ጻድቃን ጥበብ ይመልስ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኃይል በፊቱ እንደሚሄድ” ነገረው፡፡(ሉቃ.1፥17) ካህኑ ከሚሰማውና ከሚያየው ነገር ይልቅ በዙርያው ያለውን እርጅናና ያለመውለድን ነገር አይቶ በልቡ ደከመ፤ እምነቱ ተፈታ፤ በአለማመንም ተከበበ፡፡
   ትልቁ ካህን የአብርሃምንና የሣራን ነገር ዘንግቶ መውለድ እንደማይችል፤ እርሱም ሚስቱም ያረጁ መሆናቸውን ለመልአኩ ለማስረዳት ጀመረ፡፡ ብዙዎቻችን እንዲህ ነን፤ በአገልግሎታችን ሁሉ የምንነቀፍበት ነገር አይኖርብን ይሆናል፤ ነገር ግን የአገልግሎታችን ያህል ሳይሆን ቅንጣት ታህል እምነት ታጥቶብን ብዙ ጊዜ የምንስት፣ የምንዝል፣ የምንወድቅ ነን፡፡ ካህኑ ማመን በሚገባው ነገር ደከመ፤ የአለማመን ድካም ደግሞ ሁሌም ቅጣት አለበት፡፡ ካህኑ ነገሩ እስኪሆን ዲዳ ወይም ደንቆሮ ትሆናለህ ተባለ፡፡(ሉቃ.1፥20፤62)
    ድንግል ማርያም “ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል?” ያለችው (ሉቃ.1፥34) እንደዘካርያስ ባለማመን አይደለም፡፡ ንግግሯ ፍጹም እምነቷን የሚገልጥ ነውና፡፡ ምክንያቱም በህሊናዋ ለእግዚአብሔር የመሰጠት ቁርጥ አላማ ነበራት፤ በዘመኗ ላይ እግዚአብሔርን ለመሾም ወስናለች፡፡ ከወንድ የመገናኘት ፍጹም ፍላጎት የላትም፡፡ የልዑልን ልጅ ለመውለድ መሻቷን ብትገልጥም አፈጻጸሙን ግን አላወቀችውምና “ይህ እንዴት ይሆናል?” አለች፡፡ ይህ ትልቅ እምነትን ያጠይቃል፡፡ የቀደመችው እናት እውነተኛውን ቃል መለየት ባለመቻሏ ለአመጻ ቃል ተሸንፋ፤ በእግዚአብሔር ቃል ላይ አመጸች፡፡ ድንግል ማርያም ግን የእግዚአብሔርን ቃልና መናፍስትን እንኳ በመመርመር ለእግዚአብሔር መታዘዝን ተማረች፡፡ እምነት አለመጠየቅ አለመመርመር አይደለም፡፡ የዳንበትን እውነት በአመክንዮ ማስረዳትና መረዳት፤ መጠየቅና መመርመር በእውነት የሚገባ ነው፡፡ መዳን ለሚገኝበት እውቀት መጠንቀቅ(1ጢሞ.4፥15) ዕለት ዕለት መጻህፍትን እየመረመሩ(ሐዋ.17፥10) መናፍስት ከወዴት እንደሆኑ መመርመር(1ዮሐ.4፥1)  ጥልቅ እምነት ያለው ሰው መገለጫ ነው፡፡ ስለዚህ ነገሩን በእምነት ልብ መረመረችው፡፡
    የአፈጻጸሙን መንገድ መልአኩ በጥንቃቄ አስረዳ፡፡ ከማህጸንዋ የሚወለደው ህጻን እርሷን መንፈስ ቅዱስ ከጸለላት በኋላ እንደሆነ፤ ህጻኑም አዳማዊውን ኃጢአተኛና ሥጋዊ ተፈጥሮ እንደማይጋራ፤ ቅዱሱ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሚባልም ነገራት፡፡ ኤልሳቤጥንና ዘካርያስን በምስክርነት ጠቅሶ እነርሱ እንኳ መጽነሳቸውን አስረግጦ፥ እግዚአብሔር የሚሳነውና የሚያቅተው ነገር እንደሌለ ተናገራት፡፡(ኤር.32፥17፤ሉቃ.1፥36) በክፉዎች መካከል በናዝሬት ያለችው ድንግል ማርያም፤ ህጉን ከሚያውቁ በኢየሩሳሌም ካለው ዘካርያስ፣ በገሊላ ናዝሬት መንደር ነዋሪዋ ድንግል ማርያም፤ በመቅደስ ከሚያገለግለው ዘካርያስ፣ በዕድሜዋ ገና ብላቴና ድንግል ማርያም፤ በዕድሜ ከሸመገለው ዘካርያስ፣ “ምንም ክህነት” የሌላት ድንግል ማርያም፤ ክህነት ከነበረው ዘካርያስ የተሻለና የሚበልጥ እምነት ይዛ ተገኘች፡፡ ከሚጠበቀው ሳይገኝ ከማይጠበቀው ሲትረፈረፍ ይህ ጌታ አሠራሩ እንዴት ይደንቃል?! ብዙ ዘመን በቤቱ ኖረን ፍሬ አልባ ሆነን፤ ከገረገራው ያሉ ግን “እግዚአብሔርን የሚያስደንቅ እምነት” ሲይዙ ማየት ፍርድ በደጅ መቅረቡንም ያመለክታልና፤ ወደራስ መመልከት፣ ዓይኖቻችንን በራሳችን ላይ ማድረጉ ይረባናል፡፡
   የድንግል ማርያም ምላሽ የሚደንቅና ፍጹም ታዛዥነቷን የሚያስረግጥ ነበር፡፡ “እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ” አለች፡፡(ሉቃ.1፥38) ይህ ፍጹም  የተሰጠ ማንነትን ያሳያል፡፡ ለእግዚአብሔር ከሥጦታዎች ሁሉ የሚበልጠው ትልቁ ሥጦታ ራስንና ማንነትን “የጌታ ባርያ” ብሎ ለፈቃዱ ማስረከብ ነው፡፡ ከራሳችን ያነሰ ሥጦታ ዕጣን፣ ጧፍ፣ ዝማሬ፣ ስብከት፣ አስራት፣ መጽሐፍ፣ መጋረጃ … ይዞ ወደ እግዚአብሔር ፊት መቅረብ፤ በዚህም ራሳቸውን እንደትልቅ አገልጋይና የእግዚአብሔር ሠራተኛ ቆጥረው የተቀመጡትን ሳይ ብዙ ጊዜ ውስጤ ይደማል፡፡ ትልቁ ሥጦታ ራስን ለእግዚብሔር “አንተ እዘዝበት፤ ፈቃድህ ይፈጸምበት” ብሎ መስጠት ነው፡፡ በእርግጥ እንዲህ ያሉትን እግዚአብሔር ይመለከታል፡፡ “የባርያይቱን ውርደት ተመልክቷልና” አለችም አይደል ድንግል እመቤታችን?!!!
  አይሁድ ይህን ነገር ለመቀበል ልባቸው ዘግይቷል፡፡ እግዚአብሔርን እየሰሙ አለመታዘዝ፤ ቃሉንም እያደመጡ መደንዘዝ እንዴት ያለ አስጨናቂ ነገር ነው? ከእግዚአብሔር ሐሳብ የዘገየ ልብ ከበጎ ነገር ሁሉ የጎደለ እንደሆነ ማን በነገረው? አይሁድ ልባቸው ከማመን ቢዘገይም ጌታ ግን ድንግል ማርያምን በዘመን መጨረሻ በመንፈስ ቅዱስ አሠራር ኢየሱስን ትጸንስ ዘንድ መረጣት፡፡
አሜን፡፡ የሚመርጠን እንጂ የማንመርጠው ጌታ ውርደታችንን ተመልክቷልና ይወደስ፡፡
ይቀጥላል …



No comments:

Post a Comment