Monday 23 December 2013

የኢየሱስ ደም - ክፍል ሦስት

                           Please read in PDF :- yeEyesus dem 3

     ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን ሰርቶ በጨረሰ ጊዜ “ሀያ ሁለት ሺህ በሬዎችና መቶ ሐያ ሺህ በጎች ሠዋ” ይለናል ታላቁ መጽሐፍ፡፡ (2ዜና.7÷5)፡፡በአንድ ቀን እንዲህ ያለ መስዋዕት ከቶውንም በብሉይ ኪዳን ውስጥ ቀርቦ አያውቅም፡፡ሀያ ሁለት ሺህ በሬና መቶ ሐያ ሺህ በጎች በአንድ ቀን!!! አስተውሉ! ከአንድ እስከሀያ ሁለት ሺህ  ቁጠሩና እንደገና ከአንድ እስከመቶ ሐያ ሺህ ጊዜ ቁጠሩ!!! ቁጥር ብቻ ግን አይደለም የሚፈሰውንም የደም ብዛት እዩ! ከዚያ እናንተ በሰሎሞን ቦታ ቁሙ! ምን ያህል ደም በፊታችሁ እንዳለ አስተውሉ!!! የክርስቶስ ደም እንዲህ ነው ከኃጢአት ሁሉ የጋረደንና ለክብሩ የሰወረን!!!
    ሰሎሞንን የመስዋዕቱ ደም ከድኖታል ፤ሰሎሞን የተኛው ሙሉ ለሙሉ በደም እንደተጋረደና በደም እንደተሸፈነ ነው፡፡እንዲህ ሆኖ ተኝቶ ሳለ ጌታ እግዚአብሔር በሌሊት ለሰሎሞን ተገለጠለት፡፡ልዩ ኪዳንም ገባለት፡፡(2ዜና.7÷11-22)፡፡የሚገርመው ግን ይህ ሁሉ መስዋዕት በቀን እየቀረበ እንኳ ፍጽምትና ቅድስት ፣አዲስና ህያው የሆነችውን መንገድ ከኢየሱስ በቀር መርቆ መክፈት የተቻለው አልነበረም፡፡ ምክንያቱም  እነዚህ ሁሉ መስዋዕቶች ፦
የሰውን ዋጋ ስለማይተካከሉ(ማር.8÷37፤ዕብ.÷10÷1)
ጊዜያዊ መፍትሔ እንጂ ኃጢአትን የማያስወግዱና ፍጹም ድህነትን(ድነትን) የማያሰጡ ስለሆኑ(ዕብ.9÷9፤10÷1)
መስዋዕቶቹ በራሳቸው ፍጹማን ስላልሆኑ
እስከመታደስ ዘመን ብቻ በምሳሌነት አገለገሉ፡፡(ዕብ.9÷9)፡፡ስለዚህም ሰው ልዩና ታላቅ ቤዛ ከኃጢአቱም ነጻ የሚያወጣው ሊቀ ካህን የሆነ ቤዛ አስፈለገው፡፡


                        ክህነቱ የማይለወጥ ዐቢይ ሊቀ ካህናት(ዕብ.7÷25)

    የብሉዩ ሊቀ ካህን ዋና አገልግሎቱ ስለህዝቡ ህዝቡን ተገብቶ ስለኃጢአት ይቅርታ ደምን በእግዚአብሔር ፊት ይዞ መቅረብና መማለድ ነው፡፡ነገር ግን ይህ የሊቀ ካህኑ አገልግሎት ምንም እንኳ ህጉ ንጹህ ቢሆንም (ሮሜ.7÷12) እርሱ ራሱ በኃጢአት የተያዘ (ዕብ.5÷3)፣ሞት የሚከለክለውም ስለሆነ (ዕብ.7÷23) የሚያቀርበው የእንሰሳቱም ደም ፍጹም የሆነ የኃጢአትን ሥርየት ሊያስገኝ አልተቻለውም፡፡ ስለዚህም እርሱ ራሱ በኃጢአት ያልተያዘ ፣ቅዱስና ነቀፋ የሌለበት ንጹህና ከኃጢአተኞች የተለየ (ዕብ.6÷26) ሞት የማይይዘውና ለዘለዓለም በህይወት የሚኖር ዐቢይ ሊቀ ካህናት ይገባናል (ያስፈልገናል)፡፡


    ክብር ይግባውና ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የሆነበትን ዓቢይ ምክንያት ዮሐንስ አፈወርቅ ሲተረጉም “ሰው የሆነው ዘመድ ሊሆነን ብቻ አይደለም ፈጽሞ ይቅር ይለን ኃጢአታችንን ለማሥተስረይ ፣ከአብ ጋር ለማስታረቅ ፤ሊቀ ካህናትም ይሆነን ዘንድ ወደደ እንጂ፤ስለዚህም ሰዎችን ሊመስላቸው ይገባል ባለው ነገሩ ላይ ጨምሮ በሁሉ አዛኝ፣የህዝቡንም ኃጢአት ለማሥተስረይ በእግዚአብሔር ዘንድ የታመነ አስታራቂ ይሆናቸው ዘንድ ነው አለ” ይለናል፡፡(ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ፡፡(1982)አዲስ አበባ፣ተስፋ ማተሚያ ቤት፡፡ምዕ.62 ቁ.13 ገጽ.204)
    ክርስቶስ እንደሌዋውያን ባለች ፍጽምናና ቅድስና በሚጎድላትና ብዙዎች ባገለገሉባት ፣በምትደጋገመው ደካማ ክህነታዊ ምሳሌ ሳይሆን እንደመልከ ጼዴቅ ባለች አንድ ጊዜ ተገልግላ ለዘለዓለም ህያው ሆና በህይወት በምትሰራው ክህነታዊ አገልግሎት ሊቀ ካህናት ሆነ፡፡ ክርስቶስ ሊቀ ካህናት የሆነው ራሱን ሰውቶ ነው፤ራሱን የሠዋው ደግሞ አንድ ጊዜ ለዘለዓለም ነው፡፡ሊቀ ካህንነቱም አንድ ጊዜ በሠዋውና ለዘለዓለም በሚኖረው፤ በማይለወጠውም ህያው ክህነቱ ነው፡፡(ዕብ.7÷20)፡፡ክርስቶስ ያገለገላት የክህነት አገልግሎት እንደሌዋውያን ወደሌላ የምትተላለፍ አይደለችም፡፡አንድ ጊዜ ያቀረበው ይህ አገልግሎት ሳይከለከል ዛሬም ህያው ሆኖ በእርሱ ሊቀ ካህንነት አምነው ወደእግዚአብሔር የሚመጡትን ፈጽሞ፣ ያለመሰናክል ለዘላለም ሊያድናቸው ይችላል፡፡
    ክህነቱ ለዘለዓለም የምትኖር ናትና እንደሌዋውያን ታልፋለች አትባልም፡፡እርሱ በዚህ አገልግሎቱ አባቱንና እኛን ደስ ያሰኘ መዓዛው ያማረ መስዋዕት ነው፡፡አዎ! አባቱን ደስ ያሰኘ መስዋዕት ስለሆነ በአባቱ ዘንድ ስለሚታየው ችንካርና ደሙ ጸሎታችን ይሰማልናል፡፡ብሉይ ኪዳን ያለደም ገና ቅድስተ ቅዱሳኑ እንዳልተከፈተ ሐዲስ ኪዳንም በክርስቶስ በሆነች ህያው ክህነት በተሠዋ ደሙ ካልሆነ ገና መዳን ገና ምንም ህይወት የለም፡፡
    አዎ! እርሱ ሰው ካልሆነና መጥቶ በዐቢይ ሊቀ ካህንነቱ፣በማይለወጥም ክህነቱ ካላገለገለን በቀር አንድንምና ሊያድነን መጣልን!!!
                    “ቀድሞ ሊቀ ካህናት ይለምን እንደነበረ ዛሬ ስለለመነ አምላክ
                     ይለምናል ብለህ አታድንቅ፡፡ሊቀ ካህናት እንደመሆኑ ስለለመነ
                     አታድንቅ፡፡ … ስለምን ሰው ሆነ ሰው ካልሆነ አያድንምን የሚል
                     ሰው ቢኖር አዎን ሰው ካልሆነ አያድንም ብለን እንመልስለታለን፡፡”
                   (ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፡፡17ኛ ድርሳን ቁ.31-37 ገጽ.302)
በእርግጥም እውነቱ ይህ ነው!!! እርሱ በደሙ ባገለገላት የክህነት አገልግሎት በኩል እንጂ ለሰው መዳን ፈጽሞ አይታሰብም፡፡ምናልባት ከዚህ ከደሙ መንገድ ውጪ ለመዳን ማሰብ ምዕራብን ከምስራቅ ለማዋሀድ የመጣር ያህል እጅግ መታከት ብቻ ነው፡፡ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ይህን አውነት ያጸኑታል፦
        “ከመስቀል ሌላ የመዳን አማራጭ አለ ብሎ ማሰብ ከእውነትና ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጪ
         መሆንን ያመለክታል፡፡መስቀል አያስፈልገንም ከነኃጢአታችን ወደእግዚአብሔር
         ለመቅረብ እንችላለን ማለት ዘበት ነው፤ሐሰትነው፤ከእግዚአብሔር ተለይቶ መቅረት
         ካልሆነ በስተቀር የእግዚአብሔር የቅድስና መለኮታዊ ባህርዩ የሚያቃጥል እሳት ስለሆነ
        በክርስቶስ መስቀል በኩል ካልሆነ ማንም ሊድንና ወደእግዚአብሔር ሊቀርብ አይችልም፡፡”
       (አበራ በቀለ(ሊቀ ጉባኤ አባ)፡፡(1996)፡፡ትምህርተ ሃይማኖት እና ክርስቲያናዊ ህይወት፡፡
        አዲስ አበባ፡፡ንግድ ማተሚያ ድርጅት(ማህበረ ቅዱሳን)፡፡ገጽ.116)
እንግዲህ ዐቢይ ሊቀ ካህናት ክርስቶስ በሊቀ ካህንነቱ በሠራልንና በህያው ክህነቱ ባገለገለልን የመስቀል ሥራ የምናምን ልጆቹ መንግስቱን እንወርስ ፤ክብሩን እንለብስ ዘንድ ይገባናል፡፡ በእውነት ሞቱ የሚያኖር እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት ያስፈልገናል፤ይገባናልም!!! ከዚህም የተነሳ …


                          መስዋዕቱም አቅራቢውም ፍጹም ነው!!!


        የብሉይ ኪዳን መስዋዕት ከመስዋዕቱ ደካማነትና ከኃጢአት የተነሳ ፍጽምና አልነበረውም፤አቅራቢውም ካህንና ሊቀ ካህን በኃጢአት የተከሰሱ ስለሆነ አገልግሎቱ የሞትና የኩነኔ አገልግሎት ተብሏል፡፡ (2ቆሮ.3÷9)የብሉዩ መስዋዕት አቅራቢው ሊቀ ካህን “እርሱ ራሱም ደግሞ ድካምን የሚለብስ … ”(ዕብ.5÷2) ስለሆነ በአገልጋዩና በሚቀርበውም መስዋዕት መካከል ነቀፋ ስለተገኘበት አዲስ መስዋዕትና ንጹህ አቅራቢ አስፈለገ፡፡(ዕብ.8÷8፤ኤር.31÷31)
   አምላክ ወልድ በተለየ አካሉ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በነሳው ሥጋ የእግዚአብሔር በግ ሆኖ በንጹህ መስዋዕትነቱ ህዝቡን ከኃጢአታቸው ሊቤዣቸውና ሊያድን ይህንንም መስዋዕት ያቀርብ ዘንድ መጣ፡፡ (ዮሐ.1÷29፤ማቴ.1÷21) ክርስቶስ ኢየሱስ የመጣው በሊቀ ካህንነቱ መስዋዕትን ሊያቀርብና በመስዋዕትነቱም አለምን ሊቤዥና ሊያድን አላማ አድርጎ ነው፤ ክርስቶስ ኢየሱስ በፍጹም ቅድስናና ንጽዕና መስዋዕት መሆኑ በብሉዩ የቀረቡትን መስዋዕቶች ሁሉ የሻረና ያስረጀ፤ እንዲነቀፍም ያደረገ ነው፡፡(ዕብ.8÷7) ውራጅም ሆኖ ሊጠፋ የቀረበ ሆነ፡፡(ዕብ.8÷13)፡፡
    በእውነት ይህ ነገር ይደንቃል!!! በመስዋዕትነቱ ሥላሴ ለእኛ ያለውን ፍቅር በመስቀል ላይ አየን፡፡ “ … ክርስቶስ ሥጋውን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ፣ሊቀ ካህናታችን ነውና ወደእርሱ ስለቀረበው በሥልጣኑ ሥለዐሳረገው ስለሥጋው ስለደሙ ወደእርሱ መቅረብ ከተቻለው ከዚህ መስዋዕት የተነሳ አብ አደነቀ፡፡”(ሃይማኖተ አበው፡፡ምዕ.68 ክ.23 ቁ.23 ገጽ.231) ራሱን መስዋዕት አድርጎ በማቅረብ ለሚሻለው ተስፋና ለሚሻለው አዲሱ ኪዳን ዋስ ሆኖ የዘላለምን ቤዛነት አጊኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ በእጅ  ወዳልተሰራችው ወደሰማያዊቷ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ፡፡(ዕብ.7÷19፤8÷6፤7÷22፤9÷12) ስለዚህም መስዋዕት አቅራቢው ይዞት የገባው የደም መስዋዕት ፍጹም ስለሆነ፦
ሊያድንና ሊቤዥ ብቻውን በቂ ነው
ሌላ መስዋዕት ፈጽሞ አያስፈልገንም (ዕብ.10÷18፤26)
በዚህ በማመን እንድን ዘንድ በሰማያዊ ጥሪ ተጠርተናል፡፡
እንደመልከጼዴቅ ባለች በዘላለም ክህነት በሊቀ ካህንነቱ በኃጢአትና በሞት ፈርዶ እኛን በጸጋው አጽድቆ ፤በእንዲሁ ፍቅር መንግስቱን እንወርስ ዘንድ የጠራን ጌታ ልዩና ድንቅ ነው!!! በዚህ ደም የዳንን ክርስቶሳውያን ቤተሰቦች ጮኸንና አሰምተን ልንናገርለት የሚገባን አንድና ትልቅ እውነት መንፈሳዊ ታላቅ ሥራ ይህ ብቻ ነው፡፡ሙሽሪት ቤተ ክርስቲያን ሆይ ያጌጥሽበት የክብር ልብስሽ ፤ወደበጉ ሠርግ መግቢያም ካባና ላንቃሽ ደሙ ነውና ዘወትር ትናገሪው ዘንድ አትርሺ፡፡
       የካህናት አለቃ አምላካችን መድኃኚታችን  ኢየሱስ ክርስቶስ በጽድቅ የጌጥ ልብሱ፤በደሙ ኃጢአታችንን ይቅር ይበለን፡፡ከነውርም ሁሉ ያንጻን ፡፡አሜን፡፡

    ይቀጥላል…
               

4 comments:

  1. egezibeher betsega endasadegeh degemo betsega yalemelemeh

    ReplyDelete
  2. egzibeher betsega endasadegeh degemo betsegaw yalemelemeh

    ReplyDelete
  3. kidus yohanis afeworki yetenagerewun ante yemitifeligatin bicha korteh awutiteh yeraasihin nufaqe chemereh litachiberebire atimokire

    ReplyDelete