ቅዱስ እግዚአብሔር በበጎ ፈቃዱና ከታላቅ ባዕለጠግነቱ የተነሳ ሰውን ፍጹምና ቅዱስ አድርጎ ከመፍጠሩ በፊት የተፈጠረው ክቡር ፍጡር በገዛ ፈቃዱ ወድቆ እንደሚረክስ በባሕርይ ዕውቀቱ አወቀ። ስለዚህም የሚፈጥረውን ውድ ፍጥረት አብ በልብ እንዳሰበ በወልድ ሕያው ቃልነት ሲፈጥረው፤ መጥቶ እንደሚያድነውና እንደሚዋጀው ኪዳንን ገባ። ይስሐቅ በአብርሐም ኅሊና ቀድሞ እንደታረደ ወልድም በአብ ኅሊና ቀድሞ የታረደ ሆኖ በበጉ ያመኑትና የዳኑት ቀድሞ ስሞቻቸው በሕይወት መዝገብ ተጻፈ፤መንፈስ ቅዱስ ይህን እውነት ቀድሞ ለተወሰኑ ምርጦች በብሉይ ኪዳን ኋላም ለሐዲስ ኪዳን አማኞች ናኘው።
አቡቀለምሲሱ(ባለ ራእዩ) ዮሐንስ “ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት
መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል” (ራእ.13÷8) ባለው ቃሉ፣ የአብ አንድ ልጁ ለዓለሙ ኀጢአት
የታረደ ሆኖ የታየውና ኪዳኑ የተወሰነው ገና አሮጌው ኪዳን ሳይመጣ እንደሆነ “ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት…”
በማለት ይነግረናል። እግዚአብሔር ከዘመን በፊት ፍጥረት እንዲድን እንጂ እንዲጠፋ አልወደደም፤ ስለዚህም እንደ እግዚአብሔርነቱ
ራሱን፣እንደ እኛም ከእኛ በተለየ አካሉ ኢየሱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም በነሳው ሥጋ እኛን ወክሎ ከፍጥረት በፊት ልዩ ኪዳኑን
ሰጠን(ገባልን)። ቅዱስ ሐዋርያ ጴጥሮስም ከፍጥረት በፊት ሰውን ለማዳን ክርስቶስ ቤዛ እንዲሆን በእግዚአብሔር(አብ) የተመረጠ
መሆኑ የታወቀና የተረዳ መሆኑን በመልዕክቱ ገልጧል፤ (1ጴጥ. 1÷20)።
የዚህ ቁርጥ ውሳኔ ዋና አላማ የሰው ልጅ በኀጢአት መውደቅና መርከስ፣ ያለአድራሻው
በሞት ኩነኔና፣ በዘላለም ፍርድ መያዙ ስለሆነ ከዚህ የሚቤዠውና የሚያድነው አንዳች ሌላ አዳኝ ስላልተገኘና ስለሌለም
ነው።
ኃጢአትና ኃጢአተኝነት
የመስዋዕት ደም ያስፈለገበት ዋናው ምክንያት ስለ ኃጢአት ነው። “ኃጢአት”
የሚለውን ቃል የአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ሲፈታው “በቁሙ በደል፣ዐመጥ፣ግፍ፣ ሕገ ወጥ ሥራ በኃልዮና በነቢብ
በገቢር የሚሠራ፣ ፅድቅን መቃወም … ” ነው ሲል፣ በሌላ ትርጉሙም፦ “ማጣት፣ መቃጣት፣ ዕጦት፣ ችግር፣ ሽሽት፣ኩብለላ።”
በማለት ተርጉመውታል።(ኪዳነ ወልድ ክፍሌ/አለቃ/፤መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ፤1948 ዓ.ም፤አርቲስቲክ ማተሚያ
ቤት፤ገጽ 474።)
የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን ህግ በመተላለፍ ኃጢአትን በኀልዮ(በማሰብ)
በመጎምጀት፣ በነቢብ (በመናገር) ከጠላት ጋር በማሾክሾክ እግዚአብሔር ያለውን “እንዳትነኩትም” በማለት በእግዚአብሔር ቃል ላይ
በመጨመር ህጉን ሲያጣምም፣በገቢር ደግሞ ጌታ እግዚአብሔር ያስቀመጠውን የትዕዛዝ ድንበር በማፍለስ ራሱን ከሕይወት ዛፍ በመለየት
ኃጢአትን አደረገ። በዚህም የሰው ልጅ ሞገስ አልባ ሆኖ በኃጢአቱ ምክንያት የፍቅር ድምጽ እያስደነገጠው ከክትክታ ዛፍ ስር
ተሸሸገ፤ (ዘፍ. 3÷10) ።
ያ ከእግዚአብሔር ጋር የሚጨዋወቱበትና ህብረት የሚያደርጉበት የገነቱ ሥፍራ
አሁን የመሸሸጊያና ፍርሐት የነገሰበት ሥፍራ ሆነ። የእግዚአብሔር ፈቃድ ካልነገሠባት በእርግጥ ገነት የኃጢአተኞች መሸሸጊያ
እንጂ ማረፊያ አትሆንም። ገነት ያለእግዚአብሔር ባድማ ምድረ በዳ ናት። እግዚአብሔር ያላሳረፈው ገነት አያሳርፈውም። በትልቁ
ያልረካ በትንሹ አይረካም።የእግዚአብሔር ሞኝነት ካላስጠበበን የአለሙ ጥበብ ይበልጥ ያደነቁራል። ስለዚህም ትልቁ እግዚአብሔር
የነገረንን ንቀን “መሞት እንኳ አትሞቱም” ያለንን የጠላት ድምጽ ሰምተን ባፈገፈግን ጊዜ ከጸጋ መራቆትን አትርፈን
እግዚአብሔርን ከምንቀርብበት ከልጅነት ድፍረት በመጎስቆል፣ በበደላችንና በኃጢአታችን በፍጥረታችን የቁጣ ልጆች ሆንን፤ (ኤፌ.2÷3)።
ከኖህ በፊት የነበሩት የሚበዙቱ አበው “ሙታን ሆነው” ከዘጠኝ መቶ አመት
በላይ ኖሩ። ስለዚህ መሞት ማለት በድን መሆን ሳይሆን ከእግዚአብሔር የሚገናኘው የመንፈሳችን አካል በገዛ ነውርና ኃጢአታችን
የምኞታችን ባርያ ሆነን ከእግዚአብሔር መለየታችንን ያሳያል። በዚህም ተፈጥሮዐችንን በክፋት በከልነው። አዎ! የተፈጥሮ ብልሽት
ከአጥንት የሚዘልቅ ነው። አዎ! የልጁ የክርስቶስ ኢየሱስን ድምጽ አጥርተው የማይሰሙ እነርሱ በእርግጥም ሙታን ናቸው።የሚሰሙትም
ሕይወት ይሆንላቸው ዘንድ ኢየሱስ መጣ፤ (ዮሐ. 5÷25)።
ብዙ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር ብቻ እንዳለባት ተለባብሶ
ይነገራል።የአስተዳደር ብልሹነት ምንጩ ኃጢአትና ነውረኝነት ነው። ይህ ደግሞ ምንጩ በጌታ ቃል ዳግመኛ አለመወለድ ነው። ዳግመኛ
ያልተወለደ እርሱ ደግሞ ሥጋ ብቻ ነው።ሥጋ ደግሞ የመንፈስን ሥራ ይሰራ ዘንድ አይችልም። ስለዚህ ችግራችን የአስተዳደር ሳይሆን
ለወንጌል ሕይወት ስፍራና ዋጋ አለመስጠታችን ብቻ ነው። ፈረስና ጋሪ እንደማይቀዳደሙ፣ ቢቀዳደሙ መገፋፋት እንጂ ጉዞ እንደሌለ
ሁሉ ወንጌሉ አስተዳደሩን እንጂ አስተዳደሩ ወንጌሉን ሊመራ ፈጽሞ አይችልም። ቢመራ ጉዞ ሳይሆን ፍትጊያ የበዛበት መገፋፋት ብቻ
ነው የሚታየው።
የሐዲስ ኪዳን ጸሐፍትም “ኃጢአትን” ዓመጽ ብለው ተርጉመውታል፤ (1ዮሐ. 3÷4)።
ከመጀመርያ በእግዚአብሔር ላይ ያመጸው የቀደመው እባብ ዲያብሎስ ነው፤ (ዮሐ. 8÷44፤ ራእ. 12÷9)። ከዚያም ሰው ኃጢአትን
በመስራት በእግዚአብሔር ላይ እንዲያምጽ ያደረገው እርሱ ነው። ስለዚህም ኃጢአትን የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር ላይ የሚያምጽ ዓመጸኛ
ነው ማለት ነው።
ሰው በትልቁ ጌታ በእግዚአብሔር ላይ በማመጹ ለትንሹ ጌታ ለገዛ ምኞቱና
ለኃጢአት ተላልፎ ተሰጠ። ሕጉን በመሻር ትርፍ ሲሻ እግዚአብሔርን የሚቀርብባትን ልጅነቱን አጣ።አመጸኝነቱ ለጨካኝ ጌታ አሳልፎ
ሰጠው። እኛም ብዙ ጊዜ ከእግዚአብሔር መንገድ መራቃችን ለማይራራልን ጠላት የገዛ ማንነታችን አሳልፎ ሰጥቶናል።ለህይወት
የተሰጠው ሕግ ለሞት ሆኖ የተገኘው በዚህ መንገድ ነው።አመጸኝነታችን ህግ ተላላፊ ሕገ ወጦች፣ ሕገ ወጥነታችን ደግሞ
በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አልባ አድርጎን ከጸጋው አራቆተን፤ በገዛ ኃጢአታችንም የሞትን ቀለበት አጥልቀን በሥጋችን አተምነው። እንዲለያየንም
የኃጢአትን ግድግዳ በእኛና በእግዚአብሔር መካከል ሠርተን ከኃጢአት በታች በመሆን ሁላችን አስቀድመን ተከሰስን፤ (ሮሜ 3÷9)።
ኃጢአተኝነት በምድር ሁሉ ላይ ተንሰራፋ፤ኃጢአትም መውጊያ ሆኖ ቀዳሚውን
አዳምና ልጆቹን ሁሉ እየወጋ የሚያደማና በመንፈስም ባዶነት የሚገዛ፣የአዳም ገላው ብቻ ሳይሆን ሕይወቱም ስለተራቆተ ፍጥረት ሁሉ
በማቃሰት ተያዘ። ሰው የሚጠጋበት ጥግ አጥቶ በኃጢአት ግዞት ውስጥ በብቸኝነት ተጋዘ። ሞት ድል መንሳቱን፣ ሲዖልም የመስበር
ብርታቱን፣ ሰይጣንም ታላቅነቱን አውጆ የሰው ዘር በኃጢአት ፍርሐት ማቀቀ። ኃጢአተኞች ብቻ ሳንሆን ኃጢአተኝነት ምድርን ገዝቶ
ነዳት። ክብር ይግባውና ገና ኃጢአተኞችና ጠላቶቹ ደካሞችም ሳለን (ሮሜ 5÷6-10) አብ የማይገባንን ታላቅና ኅሊናን የሚያልፍ
ፍቅር በክርስቶስ ኢየሱስ ገለጠልን።
ፍቅሩ ይቆየን፤ አሜን።
ይቀጥላል…
No comments:
Post a Comment