Friday 8 May 2015

“ … ለደቀ መዛሙርቱ እንደገና ተገለጠላቸው” (ዮሐ.21፥1)

  

  ጌታችን ከሙታን መካከል ከመነሳቱ በፊት ገና በተሰቀለ ጊዜ በደቀ መዛሙርቱ ልብ የቀረው ነገር እጅግ አስደንጋጭ ነገር ነበር፡፡ እንዲያውም ተስፋ እስከመቁረጥም አድርሷቸው ሉቃስና ቀለዮጳ ወደመጡባት ከተማ ወደኤማሁስ(ሉቃ.24፥13) ፥ ብዙዎቹም ጥለው እንደሸሹ ያልተመለሱ ሲሆን (ማቴ.26፥56) ፥ ስምዖን ጴጥሮስ ፣ ዲዲሞስ የተባለው ቶማስ ፣ ናትናኤል ፣ የዘብዴዎስ ሁለቱ ልጆች (ያዕቆብና ዮሐንስ) ደግሞ እጅግ ተስፋ ከመቁረጥ የተነሳ የዕለት ጉርሳቸውንና የዓመት ልብሳቸውን ለመሸፈን ጌታ እነርሱን ከጠራበትና ትተውት ተከትለውት ወደነበረው (ማቴ.4፥18 ፤ ዮሐ.21፥1) ወደቀደመ ህይወታቸው አሳ አስጋሪነት(አጥማጅነት) ተመልሰው ተሰማሩ፡፡

    ቀራንዮ ላይ በጌታ ሲሆን ያዩት ነገር ፥ የተነገራቸውን የተስፋ ቃል አስረስቶ አደንዝዟቸዋል፡፡  ከመከራው በፊት መከራውን በጸሎት እንዲያልፉ ቢነግራቸውም ፥ የሚመልሱትን እስከማያውቁ ድረስ በእንቅልፍ ብዛት በጊዜው ማስተዋል ባለመቻላቸው መንፈሳቸው እንደሥጋቸው መድከሙን እናያለን፡፡ (ማር.14፥49-50) በእውነትም መከራን በጸሎት አለመታገስ በደስታ ቀን የሆነውን ሁሉ ያስረሳል፡፡  ሰይጣን ከመከራውም በፊት ፤ በመከራው ጊዜና ከመከራው በኋላ እንዳናይ ከሚያደርገው መንገድ አንዱ የጸሎትን መንገድ ነው፡፡ አለመጸለይ፦
       ህሊናን ያደነዝዛል ፤
       ከእውነት መንገድ ያስታል ፤
       ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያለንን ግንኙነት እንዲቋረጥ ያደርጋል ፤
       መከራውን ብቻ እንድናይ ፤
       በእጅግ ጥቂቱ ነገር ተስፋ እንድንቆርጥ ያደርጋል፤
       ከሁሉ በላይ የተነገረውን የተስፋ ቃል ያስረሳል፡፡
ይህ ሁሉ ነገር በደቀ መዛሙርቱ ህይወት ሲሆን እናያለን፡፡ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ “እንደ ገና አያችኋለሁ ልባችሁም ደስ ይለዋል፥ ደስታችሁንም የሚወስድባችሁ የለም።”(ዮሐ.16፥22) እንዲሁም “… ከተነሣሁ በኋላ ወደ ገሊላ እቀድማችኋለሁ” (ማር.14፥28) በማለት የተስፋ ቃልን ቢሰጣቸውም ደቀ መዛሙርቱ ይህንን አላስተዋሉም፡፡ የጌታ ንግግር እንደምን ድንቅ የሆነ ንግግር ነው!? ከሞት በኋላ እንደሚያገኛቸው በሥልጣን ቃል ጌታችን ተናገረ፡፡ ከሞት በኋላ ለመገናኘት ለመጀመርያም ፤ ሆነ ለመጨረሻ ጊዜ ቀጠሮ የሰጠ ብቸኛ ወዳጅ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡  በአለማችን ላይ እንደክርስቶስ ኢየሱስ ከሞት በኋላ የእንገናኛለን ቀጠሮ ለወዳጆቹ የያዘ ማንም የለም፡፡
    ይህንን ልዩና ድንቅ የማይረሳ ቀጠሮ ደቀ መዛሙርቱ መርሳታቸው የሚደንቅ ነው! ደቀ መዛሙርቱ ብዙ ድውያኖችና ሕሙማን ፤ በተለያየ ነገር የተያዙ ሰዎች በጨነቃቸው ጊዜ ወደጌታ መጥተው ከጌታ ምን አይነት አስደናቂና ተአምራዊ ምላሽ ያገኙ እንደነበር የአይን ምስክሮች ሆነው አይተዋል ፤ ነገር ግን ጌታ መከራን በተቀበለ ማግስት ተስፋ በመቁረጥ መንፈስ ውስጥ ሆነው እጅግ ወደኋላ ሲያፈገፍጉ እናያለን፡፡ ጌታ ያንንሁሉ ያሳያቸው እነርሱም በጭንቀት ጊዜ በስሙ ሥልጣን መከራንና ትካዜን ማለፍ እንዲቻላቸው ነበር፡፡ ግን አላስተዋሉም፡፡
     ወደኋላ የሚመለስ “ክርስቲያን” የጽድቅን መንገድ ባያውቅ በተሻለው (2ጴጥ.2፥21) የተባለለት ነው፡፡ ምክንያቱም እውነተኛውን የክርስትና መንገድ (ሐዋ.9፥2 ፤ 18፥25 ፤ 19፥2) ማወቅ ፤ ማወቅ ብቻ ያይደለ ኃላፊነትንም ያስከትላል ፤ ከምንም በላይ ደግሞ እውነትን ከማስተዋል ተዘናግቶ ፤ ረግጦ ወደኋላ መመለስ ልብን ያደነድናል፡፡ ብዙ ጊዜ ኃጢአትን በመጨከን የምንሠራው የክብሩንና የማዳኑን ወንጌል ብርሃን ዘንግተን በጠላት ሽንገላ በልባችን ስንታለል ነው፡፡
     ሁሉም ደቀ መዛሙርት ፊታቸውን አዙረው ፍጹም ወደኋላ ተመልሰው ሳሉ ጌታችን “በጥብርያዶስ ባሕር አጠገብ ለደቀ መዛሙርቱ እንደ ገና ተገለጠላቸው” (ዮሐ.21፥1)፡፡ ጌታ እንደተስፋ ቃሉ ከሙታን መካከል ተነስቶ በቀጠሮው መሠረት መጣ፡፡ ከመሞቱ በፊት እንደጴጥሮስ “ከአንተ ጋር መሞት እንኳ የሚያስፈልገን ቢሆን፥ ከቶ አንክድህም” (ማቴ.26፥35) እንዳላሉ ቀን ተለውጦ ካዱት፡፡ እርሱ ግን  “በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ነውና የወደደው” (ዮሐ.13፥1) ፤ ባያምኑትም የታመነውና ራሱን የማይክደው ጌታ (1ጢሞ.2፥13) እንደተናገረ እንደገና መጣ፡፡
    ገና አገልግሎቱን ሲጀምር ከጠራቸው ሥፍራ ዳግመኛ ቢያገኛቸውም አላዘነባቸውም፡፡ ጌታችን እንደገና መገለጡ መቼም በእኛ ተስፋ አለመቁረጡን ፍጹም ከማሳየቱም ባሻገር ፥ ጥልቅ ፍቅሩንም የሚያሳይ ነው፡፡ በእርግጥም አባታችን ብዙ እንደገናዎችን የሚገልጠው ልጆቹ ስለሆንንና በእኛ መጨከን የሚችል ባህርይ ስለሌለው ነው፡፡ ብዙ ቅዱሳን የተባሉ አባቶችና እናቶች ብዙ መውደቃቸው ሳይሆን ብዙ እንደገናዎችን ከአባታቸው በማግኘታቸው ፍጹማን ሆነዋል፡፡ አዳም የእንደገና ዕድል ስላገኘ ከሞት የመዳን ተስፋን አገኘ (ዘፍ.310 ፤ 15) ፣ ሳምሶን በጌታ እግዚአብሔር ፊት ዳግመኛ ዕድል በማግኘቱ ፤ ጸጉሩ ዳግመኛ በቅሎለት  “በሞቱም የገደላቸው ሙታን በሕይወት ሳለ ከገደላቸው በዙ።” ተብሎ የጌታ ኢየሱስ ምሳሌ ሆነ (መሳ.16፥22 ፤ 30-31) ፣ ዳዊት በጌታ ፊት እንደልቤ ከመባልም በላይ “በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ካገለገለ በኋላ አንቀላፋ” የተባለው የበዛ ዕድልን አጊኝቶ ነው (2ሳሙ.12፥13-14 ፤ ሐዋ.13፥36) ፣ ቅዱስ ጴጥሮስም በእርግጥ እንደካደ ቢቀር በአንድ ቀን ስብከት ያን ሁሉ አይሁዳዊ መማረኩ ፣፤ በአንድ ተአምራቱም ያን ያህል አማኝ መሰብሰብ እንዴት ይታሰብ ይሆን?! (ጌታችን ግን አዋቂና  ጻድቅ ነው!!!) ሦስቴ የካደው ሐዋርያ ግን ዕድል ስለተሰጠው ቁልቁል በመሰቀል ለጌታው ታማኝነቱን ገለጠ፡፡
 ብዙዎቻችን ሰው ሆነን ዛሬ የመቆማችን ትልቁ ነገር በጌታ እግዚአብሔር የሆነልን የተደጋገመ የእንደገና ዕድል ነው፡፡ ጌታ ደቀ መዛሙርቱን እንደወጡ ይቅሩ አላለም ፤ ያሉበት ወይም የጠፉበት ድረስ ሄዶ በስስት አይኑ ፈለጋቸው፡፡ ሁላችን ከመጥፋት አለም በፍለጋ የተገኘን ነን፡፡ አንዳንዶቻችን ከቤቱ ርቀን ነው የጠፋነው ፤ አንዳንዶቻችን በቤቱ እያለን እየዘመርን ፣ እያስቀደስን ፣ እየሰበክን … ባለመታዘዝና ፍሬ ባለማፍራት የጠፋን ነን፡፡ ሁላችንንም ግን ጌታ “የእግዚአብሔር ቸርነት ወደ ንስሐ እንዲመራህ ሳታውቅ የቸርነቱንና የመቻሉን የትዕግሥቱንም ባለጠግነት ትንቃለህን?” (ሮሜ.2፥4) በማለት በመደጋገም የሚጠራንን የእግዚአብሔር የቸርነቱን ባዕለጠግነት እንዳንንቅ መንፈስ ቅዱስ በወቀሳ ቃል ይነግረናል፡፡ ጌታ ምህረቱን አብዝቶ እንደገናን የሰጠን ለሌላ የኃጢአት ቀጠሮ አይደለምና!!!
   እርሱ ለአንድ ጊዜ ብቻ በደጅ ቆሞ በር አያንኳኳም ፤ ደጋግሞ ያንኳኳል እንጂ(ራዕ.3፥20) ፤ አንድ ጊዜ መጥቶ ፍሬ ስላጣብንም ተስፋ ቆርጦ አይቀርም ፤ እጅግ ደጋግሞ ከብዙ እንክብካቤ ጋር ወደእኛ ይመጣል እንጂ፡፡ (ኢሳ.5፥2 ፤ ሉቃ.13፥7) እንኪያስ እኛ ባለብዙ እንደገናዎች ሆነን ምህረት ካገኘን ፥ እኛም ለበደሉን ፣ ለሚበድሉን ፣ እየበደሉን ላሉ እንደገና አሁንም ይቅር ልንላቸው ይገባናል፡፡ የክርስቶስ የጽድቅ ሕይወቱ ይህን ያስተምረናልና፡፡
    የተወደዳችሁ ሆይ! ጌታ በብዙ ይቅር ያለንና ብዙ የእንደገና ዕድሜን የሰጠን እንዲያው አይደለም ፤ ይልቁን “አሁንስ ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጦአልና” (ማቴ.3፥10) በዚህ በከፋ ዘመን “ጸንተን በመቆም እንደ ገናም በባርነት ቀንበር ባለመያዝ” (ገላ.5፥1) ፤ “የልቡናችንን ወገብ ታጥቀንና በመጠን ኖረን፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ የምናገኘውን ጸጋ ፈጽመን ተስፋ ልናደርግ ይገባናል፡፡” (1ጴጥ.1፥13)

ጌታ እግዚአብሔር ሆይ! በጌታችን ኢየሱስ እንደገና ዕድልን ስለሰጠኸን እናመሰግንሃለን፡፡ አሜን፡፡

1 comment:

  1. Do you want to get the complete Mortal Kombat 9 Deadlands list.
    ini file and change b - Use - Max - Quality - Mode=False to b - Use - Max - Quality - Mode=True.
    TBH, my storm cant freakin move and spell properly.


    my web blog: download pes 2015 for android

    ReplyDelete