Friday 6 June 2014

መንፈስ ቅዱስ ግን ለምን ነው የተረሳው?

   Please read in PDF:- Menfes kidus gn lemn teresa? 
 የኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በብዙ ሺህዎች የሚቆጠሩ በጻድቃን በሰማዕታት፣በመላዕክት፣ በሥላሴ፣ በኢየሱስ፣ በአብ … ሥም “በመታሰቢያነት” የተሰሩ የገጠር አጥቢያ፣ አድባራት፣ ገዳማትና ካቴደራሎች አሏት፡፡ ከእነዚህ እልፍ ሺህ “አብያተ ክርስቲያናት” መካከል የመንፈስ ቅዱስን “መታሰቢያ ህንጻ” ማግኘት በምድረ በዳ መልካም ጥላ የመፈለግ ያህል እጅግ ይከብዳል፡፡ለምን ይሆን? … (በእርግጥ የመንፈስ ቅዱስ አማናዊ ማደርያ ቅዱሱ በጌታ ቤዛነት ያመነ አማኝ ሰውነት ቢሆንም! (1ቆሮ.3፥16፤ሮሜ.8፥9) የንጽጽሩም አላማ ስለመንፈስ ቅዱስ ያለንን ግንዛቤ አናሳነት ለመታዘብ እንጂ ድካምን ለማጉላት ከማሰብ አይደለም፡፡)

  መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት የወረደበትን ዕለት የክርስቶስን የማስታረቅ አገልግሎት ተንትኖ የጻፈው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ “የቤተ-ክርስቲያን የልደት ቀን” ይላታል፡፡ ቤተ-ክርስቲያን የምትባለው የምዕመናን አንድነት የምትወለደው በመንፈስ ቅዱስ ስትጠመቅ ብቻ ነው፡፡የቤተ-ክርስቲያን የመኖር ህልውናዋ ÷ ኢየሱስን ክርስቶስ ነው ብላ የመስበክ ኃይልዋ እርሱ የብርታት መንፈስ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡
     ቅዱሳን ሐዋርያት ቃሉን በመገለጥ የሰበኩት÷ህይወታቸው ያለንግግር ዓለማውያንን÷የክርስቶስን የክብር ወንጌል የማይቀበሉ መናፍቃንን÷ አህዛብን … የወቀሰው÷ አጋንንትን በትዕዛዝ ስሙን በመጥራት ብቻ ያስወጣው … መንፈስ ቅዱስ ሲመጣ ነው፡፡ ክርስቶስን ያመነች ቤተ-ክርስቲያን የጌጥ ልብሷ÷ የድንግልና የክብር ካባዋ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ለቃል ስብከት ብቻ ለሐዋርያት አልወረደም፤ የሚናገሩትን የጸጋ ወንጌል በህይወት እንዲተረጉሙትም እንጂ፡፡ ክርስቶስን አዋቂ ሆኖ ማውራትና(መስበክና) ክርስቶስን መመስከር ፍጹም ይለያያል፡፡ ሐዋርያት ክርስቶስን አላወሩትም መሰከሩት እንጂ፡፡ ስለዚህ ምስክርነታቸውም ያለቃል ንግግር እንኳ ነፍሳት ይጨመሩላቸው ነበር፡፡
    “ያቺ” ቤተ ክርስቲያን በማያምኑ አረማውያን አህዛብ ፊት በቀረበችና በተከሰሰች ጊዜ ቤተ-ክርስቲያን መልስ የሚሆናትን የሞገስ ቃል ያገኘችው÷ ሳትጨነቅም መልስ የሰጠችው እርሱ መንፈስ ቅዱስ አንደበት ሆኗት ነው፡፡ ትጠፋለች ሲባል የበዛችው÷ አበቃ ከእንግዲህ አትኖርም እየተባለ ምድርን የከደነችው ÷በሙታን መካከል የክርስቶስን ህይወት የዘራችው÷ የብዙዎችን ልብ  እየፈተነች ለክርስቶስ የማረከችው … ጌታ መንፈስ ቅዱስ የግርማ አክሊል ሆኗት ነው፡፡
     አምስት ሺህ አምስት መቶ አመታት ጌታ አብ ህዝቡን በነቢያት አንደበት "ልጄ ፣ ወዳጄ ደስ የምሰኝበት ጻድቅ ባርያዬ መሲህ መጥቶ ያድናችኋል ፤ተስፋውን በመናፈቅ ጠብቁ" እያለ አጽናንቷቸዋል፡፡ ብርቱ ነቢያት ይህንን የትንቢትና የተስፋ ቃል ሳይሰለቹ አስተምረዋል÷ ምሳሌውንም አምነው አገልግለዋል፡፡ የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜም ከገሊላዊት ድንግል ከቅድስት ማርያም የተወለደው የናዝሬቱ ኢየሱስ ሠላሣ አመት ወላጆቹንና ዘመዶቹን፤ ሦስት ዓመቱን ደግሞ ቅዱስ አባቱንና እኛን በገዛ ዘመኑ አገልግሎ በገዛ ደሙም ዋጅቶ፤ የመለኮቱ ተካፋይ እንሆን ዘንድ ቃሉን አሰምቶ ጮኾ ጠራን፡፡ ጻድቅ ልጁ ወደሰማያት በክብር ባረገ ጊዜ ቅዱስ መንፈስ የተፈጸመውን ጽድቅ በምድር ሊናኝ ÷ዘመኑ የምህረትና የጸጋ መሆኑን ሊያበስር ÷ቤተ-ክርስቲያንን ሊያጽናና÷ እንዴት እንደምንጸልይ ሊያስተምረን÷ ድካማችንንም ሊያግዝ÷ ራሱም በማይነገር መቃተት ሊማልድልን(ሮሜ.8፥28)÷ የአብ ልጅ የኢየሱስን መልክ እስክንመስል(እስክንይዝ) በብዙ ሊሰራን … ታዛዥ ሆኖ ወደዚህ ምድር መጥቷል፡፡
    ይህ ዘመን የመንፈስ ቅዱስ ዘመን ነው፡፡ቤተ-ክርስቲያን ያለእርሱ ምንም ማድረግ አይቻላትም፡፡ ደግሜ እላለሁ፥ በጣም ልብ የሚነካውና በሐዘን የሚሰብረው ነገር ደግሞ ለቅዱሳን ÷ ጻድቃን ÷ ሰማዕታት … አዕላፍ "መታሰቢያ" ተሰርቶ ለአንዱ ጌታ ለመንፈስ ቅዱስ በ"መታሰቢያነት" እንኳ አንድ "ቤተ-ክርስቲያን" በስሙ ተሰይሞ ለማግኘት ጭንቅ መሆኑ ምን እየሆን ነው? ያስብላል ÷ ምነው "ትንሹን" ስናከብር ትልቁ አኗሪው ተዘነጋን? ያሰኛል ÷  ምነው “ከዚያ ሁሉ” መዝሙር አንድ መዝሙር  ስለመንፈስ ቅዱስ ጠፋ? … መዋረዱና በአለማወቅ መደንዘዝ ለካ እንዲህ እስከመጨረሻ ነውን? ያሰኛል፡፡
        በመንፈሱ እየኖሩ መንፈሱን ላለማንሳት መጠንቀቅ ምን የሚሉት ጉዞ ነው? እንዴትስ ሊረሳ ቻለ? እንደምንስ ተዘነጋ? … ብርቱው አጽናኝ ÷ እውነተኛው መምህር ÷ ሁሉን የሚተካ ወዳጅ ÷ የዘላለም ባልንጀራ ÷ ህይወትን የሚያድስ ÷ የክርሰቶስን መስቀል በልባችን የሚስል ÷ በቅድስና የሚያስጌጥ ÷ ብቃታችን፣ ሰማዕታትን በእሳት ላይ ያራመደ፣ መናንያንን በአንበሳ ጉድጓድ የመገበ፣ ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ እንዲቀበሉ ያስጨከነ፣ አሁን እንኳ አለን ብለን እንድንናገር አለኝታ የሆነን … እንደምን እኮ እንዴት ተረሳ? …
     ቤተ-ክርስቲያን ሆይ ከወዴት እንደወደቅሽ አስቢ! … የቆምሽበትንም መርምሪ!!! ከሙሽራሽ ከኢየሱስ ስለመጋባትሽ ማጫ ሆኖ የተሰጠሽን መንፈስ ቅዱስን ገለል ብለሽ ካለፍሽበት ጎዳና ዳግም በንስሐ ፈልጊው፡፡ ያለመንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔርን ፈጽሞ ማገልገል አይቻልም፡፡ምናልባት አገልግሎት አገልግለን የሆንን ቢመስለን ከክስረታችን ባሻገር ፍጹም በሰይጣን ሽንገላ ለመታለላችን ማስረጃ አያሻንም፡፡ ቆም ብለን ማሰቡ፤ የተሰጠንን የንስሐ ዘመን መጠቀሙ የጥበብ መንገድ ነው፡፡ ሰባክያን የምንመሰክረው፣ መምህራን የምናስተምረው፣ካህናት የምንመክረው፣ዘማርያን የምንዘምረው ፣ጸሐፍት የምንጽፈው፣ … ከመንፈስ ቅዱስ ለመሆኑ መንፈሱ ለመንፈሳችን መመስከሩን እርግጠኞች ብንሆን እንዴት ባማረልን!?

      ቡሩክ ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስ ሆይ! የቤተ-ክርስቲያንን ሐሳብ እንደንስር ክንፎች ለቅድስናና ለቅድስና ብቻ አድስልን፡፡አሜን፡፡

2 comments:

  1. እጅግ ድንቅ ነው። ይህንም ያናገረ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው እናም ልብ ልንለውና ልናጤነው የሚገባ ነገር ነው። ይህንም እናደርግ ዘንድ እገዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ይርዳን።
    ቃለ ህይወት ያሰማልን።

    ReplyDelete
  2. first of all did you ask your fathers before posting this issues. Please sit with your fathers and discuss it before you comment Ethiopian Church.

    ReplyDelete