Monday 16 June 2014

“ሁላችሁ ወንድማማች ናችሁ”(ማቴ.23፥8)(ክፍል አንድ)

    Please read in PDF :- hulachihu wendmamach nachihu 1

 “ወንድም” የሚለው ቃል በቀጥታ ትርጉም ከአንድ እናትና አባት የተወለዱ ተወላጆችን የሚያመለክት ሲሆን በታላቁ መጽሐፍ ግን ከተወላጅ ባሻገር ለሌሎች ወገኖችም በተለያየ ጊዜ ተሰጥቶ ሥራ ላይ ሲውል እናገኛለን፡፡  ጥቂቱን ብንመለከት፦
ሀ. በሀገር ተወላጅነት
    የአንድ ሐገር ተወላጆች ብቻ በመሆን ወንድም መባባል እንደሚቻል መፅሐፍ ቅዱስ ሙሴንና  የእስራኤልን ልጆች በመጥቀስ እንዲህ ይላል፦ “በዚያም ወራት እንዲህ ሆነ፤ ሙሴ ጎበዝ በሆነ ጊዜ ወደወንድሞቹ ወጣ፤ የሥራቸውንም መከራ ተመለከተ፥ የግብፅም  ሰው የወንድሞቹን የዕብራውያንን ሰው ሲመታ አየ” (ዘፀ.2፥11 ፤ ሐዋ.7፥23-26)፡፡ በእርግጥም ሙሴ ለሀገሩ ለእስራኤል ልጆች ሁሉ ፍፁም ታላቅ ወንድም(ወንድም ጋሼ) ነበር፡፡
ለ.  ከጥብቅ ወዳጅነት የተነሣ
     ግብረ ሰዶማውያን በክፉ የተሰጡለትን የኃጢአት እሾህ መፅሐፍ ቅዱሳዊ ለማስመሰል እጅ ጠምዝዘው ከሚተረጉሙት ታሪክ አንዱ የዳዊትንና የዮናታንን የጠበቀ ወንድማዊ ፍቅርን በመጥቀስ ነው፡፡ ዳዊትና ዮናታን ወዳጅነታቸው እንደወንድም የነበረ መሆኑን ፥ዳዊት ዮናታን በተገደለ ጊዜ በእንባ ቃል በአንደበቱ እንዲህ አለ፦ “ወንድሜ ዮናታን ሆይ፤ እኔ ስለአንተ እጨነቃለሁ፤ በእኔ ዘንድ ውድህ እጅግ የተለየ  ነበር፤ ከሴት ፍቅር ይልቅ ፍቅርህ ለእኔ ግሩም ነበር ፡፡ (2ሳሙ.1፥26-27 )

    ዳዊትና ዮናታን የተዋወቁት ዳዊት ጎልያድን በእግዚአብሔር  ቅዱስ ስም ድል አድርጎ ፤ ይህንንም በአበኔር ጋባዥነት  እንዴት ጎልያድን እንደገደለ ለሳዖል በነገረው በዚያን ቀን ነው፡፡  ዮናታን ዳዊትን የወደደው የእግዚአብሔር ሰው በመሆኑና እግዚአብሔርም  ከእርሱ ጋር እንደሆነ በማመን እንጂ በአመፃ ለሚሠራ ኃጢአት ሊያጠምደው አይደለም፡፡ (1ሳሙ.17፥55፤18፥1-6) በእውነት ዳዊት ለዮናታን ብቻ ሳይሆን እስራኤልና ይሁዳ ሁሉ የዳዊት  ወዳጆች ነበሩ፡፡ (1ነገ. 18፥16) ዳዊትና  ዮናታንም በክፉ ቀን እንኳ ያልተለያዩ መልካም ወንድማማች ነበሩ፡፡
ሐ.  ከቅርብ ዘመድ የተነሣ
            “ … ወንድምህ እስራኤል እንዲህ ይላል … ” (ዘኁ.20፥14)
    የኤዶም ህዝብ የያዕቆብ ወንድም ከሆነው ከኤሳው የትውልድ ነገድ ነው፡፡ በኋላ ላይ በአጋጣሚ መታየት በማይገባው የጠብ ምክንያት እንደዋናና መሠረታዊ የጠብ መነሾ በማድረግ ተለያይተው እስከማይተዋወቁ ድረስ ቢከፋፉም፥ በእርግጥ ያዕቆብና ኤሳው የአንድ አባትና እናት ፍፁም  ወንድማማች ፤የኤዶም ህዝቦችም ከዚህ የተነሣ ለእስራኤል ሁሉ ወንድማማች ነበሩ (ዘፍ.36፥10፤ሮሜ.9፥3)
መ.  በቃል ኪዳን
    ወንድማማችነት በቃል ኪዳንም ሊገኝ ይችላል፡፡ ጢሮስ ለእስራኤል እንደወንድም ያለ ወዳጅ ልትሆን ከዳዊትና ከሰሎሞን ጋር ኪዳን ገብታ ነበር፡፡ (1ነገ.5፥1፤12) ነገር  ግን ይህን የወንድማማችነት ኪዳን በማፍረስ ወንድም የሆናትን ህዝብ አሳልፋ በመስጠት ከባድ ኃጢአት በመስራቷ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር በከባድ ቁጣ ሊቀጣት እንዳሰበ እንመለታለን፡፡ (አሞፅ.1፥9)
     ወንድማማችነትን የሚያረክሱና በክህደት የሚለውጡ እኒህ ያለርህራሄ ሊቀጡ ይገባቸዋል ፡፡
    እኒህ ጥቂት ማሳያዎች  ከአንድ ማህፀን ከመወለድ ባሻገር ሌሎችም ወንድሞቻችን መሆናቸውን እንመለከታለን፡፡ ወደ ርዕሳችን ስንመለስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈሪሳውያንን በወቀሰበትና በገሰፀበት ክፍሉ ላይ የተናገረውን ቃል እናገኛለን፡፡ በተለይም በትዕቢትና በውዳሴ ከንቱ በመጠመድ በምሳም የከበሬታ ስፍራ፤ በምኩራብም የከበሬታ ወንበር ፤በገበታም ሰላምታና መሞገስን በመሻት አባትና መምህር ተብለው መጠራታቸውን ፈፅሞ  መውቀሱን ፤አለመቀበሉንም እንመለከታለን፡፡
    በእርግጥ “በመካከላችን የሚደክሙትን በጌታም የሚገዙንን የሚገስፁንንም እናውቅ ዘንድ  ስለሥራቸውም በፍቅር ከመጠን ይልቅ ልናከብራቸው” ይገባናል፡፡ (1ተሰ.5፥13) ይህ ብቻ አይደለም፦ “በመልካም የሚያስተዳድሩ ሽማግሌዎች፥ ይልቁንም በመስበክና በማስተማር የሚደክሙት፥ እጥፍ ክብር ይገባቸዋል።(1ጢሞ.5፥17) በመልካም የሚያስተዳድሩና በጌታ  የሚገዙንን ልናከብራቸው ታዘናል፡፡ ይህን እንደባዕለ አእምሮ ስናስብ በአለቃና ሎሌ፣ በጌታና ምንዝር፣ በበላይና በበታች፣ በገዢና በተገዢነት መንፈስ ሳይሆን “ልዩ ልዩን የእግዚአብሔርን ጸጋ ደጋግ መጋቢዎች እንደ መሆናችሁ፥ እያንዳንዳችሁ የጸጋን ስጦታ እንደ ተቀበላችሁ መጠን በዚያው ጸጋ እርስ በርሳችሁ አገልግሉ፡፡” (1ጴጥ.4፥10-11) ተብለን በፍቅር በታዘዝነው መሠረት በወንድማማችነትና ግብዝነት  በሌለበት ፍቅር ሊሆን ይገባዋል፡፡ (ሮሜ.12፥9)
    በወንድማማችነት ፍቅር አለመዋደዳችን ብዙ ጎድቶናል፡፡ምዕመናን ራሳቸውን እንደቤተ ክርስቲያን አስራት አውጪ እንጂ እንደቤተ ክርስቲያን አካል ያልቆጠሩበት አንዱ ምክንያት አገልጋይ የተባሉቱ እንደጌታ፣እንደአለቃ፣እንደየበላይ፣እንደአዛዥ፣እንደሁሉን አዋቂና “ዶግማ ደንጋጊ ብሎም ቀኖና ቀናኒ” አድርገው እንጂ እንደወንድም ራሳቸውን ቆጥረው አለማቅረባቸውና አለመቅረባቸው ነው፡፡
     እውነት እንናገር ከተባለ በእግዚአብሔር ቤት አገልግሎት ውስጥ ትንሽ የሚባል አገልግሎት፤ ትልቅ የሚባል አገልጋይ የለም፡፡ በአባቱ ቤት ያገለግል የነበረውና ፍለጋውን እንድንከተል  ምሳሌ ትቶልን የሄደው (ሉቃ.2፥49፤1ጴጥ.2፥21) ጌታ ኢየሱስ ይህን እውነት “ከሁላችሁ የሚያንስ እርሱ ታላቅ ነውና” (ሉቃ.9፥48) በማለት ስለራሱ ተናግሯል፡፡ ጌታ ኢየሱስ  በእርግጥም ጌታና መምህር ሲሆን የደቀ መዛሙርቱን እግር አጥቧል፡፡ (ዮሐ.13፥14) እርሱ  ስለሁላችን ጥቅም የባርያን መልክ በመያዝ፤ ራሱን ባዶ አድርጎ በመዋረድ ፍፁም  የታዘዘ ነው፡፡ (ፊሊ.2፥1-11)
    ከሁሉ  ይልቅ  ደግሞ እርሱ የአብርሃምን ዘር በመያዝ በነገር ሁሉ ወንድሞቹን ሊመስል የተገባው፤ የእኛ ወንድምም ሆኖ ሊጠራ ያላፈረብንና ወንድሞቼ ብሎን የጠራን፤ የወደደንም ነው፡፡ (ዕብ.2፥13፤ማቴ.12፥50) “አኪያ” ሚለው ስምም  “እግዚአብሔር ወንድሜ” ተብሎ  ተተርጉሟል፡፡ እንኪያስ ዋናውና ከተናገርነውም ትልቁ  ምስጢር  ይህ ነው፡፡ እርሱ ወንድማችን ሆኖ ዛሬም እንኳ በሰማያት እንመካበታለን፡፡
ፍጹም ወንድም ኢየሱስ ሆይ! ክብር ይግባህ፡፡አሜን፡፡

ይቀጥላል …

1 comment:

  1. kale hiwot yasemalin, also for their, they could not understood the meaning of brother, God be open their mind!, for all thanks to God every microseconds!

    ReplyDelete