Monday 6 January 2020

የእግዚአብሔር ቅንአት!

Please read in PDF
የእግዚአብሔር ቅንዓት ይህን ያደርጋል።”
   ነቢየ ልዑል ኢሳይያስ፣ ሕጻኑ ወንድ ልጅ ጌታ ኢየሱስ ከርስቶስ ለእኛ በውድ ስጦታነት እንደ ተሰጠ ይነግረናል። “ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤” በማለት አብ ብዙ ስጦታዎችን ለእኛ ሰጥቶናል፤ ኢየሱስን የሚያህል ስጦታ ግን አልሰጠንም፤ ወደ ፊትም አይሰጠንም፤ የተሰጠን የትኛውም ስጦታ ከኢየሱስ አይበልጥምና። አስቀድሞ በራሱ መልክና ምሳሌ ፈጥሮን፣ የራሱን መልክና አምሳል በእኛ በማኖር ክብሩንና ጽድቁን፣ ዕውቀቱንና አለመሞትን ለኹላችን አድሎናል። እግዚአብሔር ሰውን ቅዱስ አድርጎ በመፍጠሩም፣ ከሌሎች ፍጡራን በተለየ መልኩ፣ ሰው የእግዚአብሔርን ቅድስና ተካፋይ ኾነ።




  እግዚአብሔር ሰውን በመልኩና በምሳሌው በመፍጠሩ፣ ታላቅና ክቡር ሥራውን በፍጥረት ኹሉ ፊት አሳይቶአል፤ በሌላ ንግግር ሰው የእግዚአብሔርን መልክና አምሳል በመያዙ፣ እግዚአብሔር ሰውን በታላቅ ክብር አክብሮታል እያልን ነው። እግዚአብሔር ሰውን በታላቅ ክብርና ዘውድ የፈጠረበት ምክንያቱ ደግሞ፣ ሰው ክብሩን ይቀኝ፤ ክብርንም ለእግዚአብሔር ብቻ ያመጣ ዘንድ ነበር። ነገር ግን ሰው ሲታመን፤ ሲገዛ፤ ለፈጠረው ጌታና አምላክ ክብርን ሲሰጥ አንመለከትም።

  ሰው በኀጢአት ምክንያት ደካማ፣ ተሰባሪ ሸክላ፣ ሕመምተኛ፣ ቀሰስተኛ ኾነ፤ ከመላእክት ይልቅ ክቡር የነበረው፣ ከኹሉም ፍጥረታት በላይ በእግዚአብሔር መልክና አምሳል የተፈጠረው ሰው፣ ተራና እንሰሳዊ “ማንነትን” ገንዘብ አደረገ። ከዚህ የተነሣ አንዴ ሲፈጠር ዘላለማዊና ቅዱስ የነበረው፣ “ውሱን”ና ፍጹም ኀጢአተኛ ኾነ፤ ጯኺ፣ መንቻካ፣ ባተሌ፣ ተቅበዝባዥ፣ ብኩን፣ ደም ግባት አልባ፣ የማይረካ፣ ኮብላይም ኾነ።

  እግዚአብሔር ከሰው የተነሣ በምድር ላይ ልዩ ዐላማ ዐለመ፤ ሰው እንደ እንሰሳ ወድቆ፣ እንደ ተጣሉቱም የጨለማ መላእክት ተጥሎ እንዲቀር አልወደደም። እግዚአብሔር ሰው ኃጢአቱን እንዲያስብ፣ እርሱ ግን ለዘላለም ሊረሣና ሊተው እንዳለ በታላቅ ምሕረቱ ሊገለጥ ወደደ። የጣቶቹ ሥራ የኾነውንም ሰው ከወደቀበት ውድቀቱ፣ ከረከሰበት ርኩሰቱ፣ ሊነሣ አይችልም ከተባለበት ዕድፋም ዝንባሌው ሊያጠራው፣ ያህዌ ኤሎሂም ወደ ሰው ሊመጣ ወደደ፤ ወይም ይመጣ እንደ ነበረው ያይደለ አካል ነሥቶ፣ ሥጋ ለብሶ፣ ሰውን ኾኖ ሊገለጥ ወደደ።

   ለወደቀውና ለረከሰው ዓለም እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እንዲኹም ሰጠ፤ ይህ እንዴት እንደ ኾነ ኢሳይያስ ሲናገር፣ “የእግዚአብሔር ቅንዓት ይህን ያደርጋል።” ይላል። እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ለማዳን፣ ሕዝቡን ላይተው እንደ ቀናተኛ አፍቃሪ ኾነ፤ ቀናተኛ አፍቃሪ ሚስቱ በሌላ ወንድ ስትነጠቅበት ዝም እንደማይል፣ እግዚአብሔር በገዛ መንገዳችን በሰይጣን ተታልለን ስንሄድበት፤ ስንወድቅበት ዝም ይል ዘንድ ፈጽሞ አልተቻለውም፤ እንደ ቀናተኛ አፍቃሪ በመኾን ውድና አንድ፤ የብቻ ልጁን ወደ ምድር በመላክ ሊያድነን ወደደ።

   በድጋሚ እላለሁ፣  እንደ ቀናተኛ አፍቃሪ ሊወድደን፣ መልሶ ሊያፈቅረን፣ ላይተወን፣ ሊይዘን፣ ሊሸከመን ወደደ። ቀናተኛው አፍቃሪ ወደ ክብር ሊያስገባን ክብሩን ጥሎ መጣ፣ በከብቶች በረት ሲወለድ ክብሩን የተወ ንጉሥ አየን፤ የሚያብረቀርቅ ንጉሣዊ ክብሩንና ልብሱን የተወ “የአብ ስጦታ” በከብቶች ግርግም አየነው። ቀናተኛው እጅግ ምስኪን የኾንነው እኛን በማፍቀር እጅግ ተዋረደ!

   ቀናተኛ አፍቃሪው፣ እኛን በመውደዱ እንዴት እንደ ተዋረደ እዩ! ላይተወን ላይጥለን በቅዱስ ቅንአት ቀንቶ ከአንዲት ድሃ ድንግል ሴት፣ ከተጎሳቆለች ስሟ ገናና ካይደለ የናዝሬት ከተማ ተወልዶ እንዴት እንደ ተገለጠ አስተውሉ! ሊያከብራችሁ ተዋረደ፤ በቅዱስ ቅንአቱ በበረት ተገኘላችሁ፤ በልደቱ ልደታችንን ያበስር ዘንድ የቀናተኛው ፍቅር እንዴት ይደንቃል?!!! አንድያ ልጁ የምድር የመጨረሻውን ዝቅታ ዝቅ ብሎ፣ እኛ በአባቱ መንግሥት በኵራት አደረገን፤ ደስ ይበላችሁ፤ ቅዱስ ቅንአቱ ልባችንን ይግዛ፤ ኹለንተናችንን ይውረስ፤ አሜን።

4 comments:

  1. amen tsega yibzalih

    ReplyDelete
  2. kalehiwot yasemmaln

    ReplyDelete
  3. ጌታዬን እየሱስን ታስተዋውቀኛለክ

    ReplyDelete
  4. God bless you the message is support me very much

    ReplyDelete