Monday 22 July 2019

ከክርስቶስ ይልቅ “ቄሣርን” አወዳሽ “ነቢያት”! (የመጨረሻ ክፍል)

Please read in PDF
“ወንጌላውያን” ነቢያትና ቤተ መንግሥታዊ ማስታወቂያነታቸው
  “ወንጌላውያን” ነቢያትና ጥቂት የማይባሉ ኦርቶዶክሳውያን አገልጋዮችም ጭምር ቤተ መንግሥቱ በሕዝብ ዘንድ ዕውቅና ያገኝ ዘንድ ተግተው “እያገለገሉ” ይመስላል፤ ለዚህም ለምሳሌ፦ ጠቅላይ ሚኒስቴሩ መወቀስ አይገባቸውም እስከሚለው ጥግ የሄዱ አገልጋዮችን አይተናል፤ እንዲያውም ቤተ ክርስቲያን ከቤተ መንግሥት ባነሰ ማንነት መኖሯን ራሳቸውን ጭምር በመስደብ ያቀረቡትን ሰምተናቸዋል። ለዚህም ለከት አልባ በኾነ መንገድ ግልጥ ፖለቲካዊ ቃላትን በመጠቀም ሲወርዱ ተመልክተናቸዋል።
ለምሳሌ፦
-       “አርበኝነት በደሙ የተዋሐደው” ኢትዮጲያዊነት፣
-       ሃያ ሰባት ዓመታት መብታችን ተጥሶ … ፣
-       የኢትዮጵያ … የጠላቶቿ ድንጋይ አቀባዮች (የማርሲሉ ዮናታን አክሊሉ)፣
-       ኢትዮጵያን እግዚአብሔር በቃል ኪዳን ጠብቆአታል፣
-       የጠቅላዩ ዙፋን የተቀባና በእግዚአብሔር ፈቃድ የተከናወነ ነው፤(ኢዩ ጩፋ) የሚሉትንና ሌሎችንም መጥቀስ ይቻላል።


    ይህን ያህል ራስን ጥሎ፣ በባዶነት ቆሞ ስለ ምድራዊ ብእልና መንግሥት ከመስበክ፣ ሌላ የጥላቻ ዘር በትውልድ መካከል ከመዝራት ዝምታ እንዴት እጅግ የተሻለና እጅግ ማራኪ ነው።ለቤተ መንግሥት ኢዮርብአማዊ የማንበርከኪያ ኮረብታ ለማቆም ከመጣርም ለኢየሱስ ክብር ተዋርዶ መሥራትን ገንዘብ ቢያደርጉ በተሻላቸው ነበር።
እስላማዊ አገልጋዮች እስላማዊ ተልእኮአቸውንና አጀንዳቸውን መትተው አብረው ከሚወያዩበት መድረክ ሲወርዱ፣ ወንጌል ያዝን ያሉቱ ኢየሱስን መጥራት ተስኖአቸው መታወራቸውና አንዲት የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስ ሳይጠቅሱ፣ የቀደመውን ዘመን በእርግማንና በጥላቻ ተናግረው ንግግራቸው ሲዘጉ ማየት ልብ ይሰብራል፤ እውነተኛ የጌታ ኢየሱስ አገልጋይ በየትኛውም መልኩ በማናቸውም መንገድ ያገኘውን ዕድል አሟጥጦ መጠቀም ካለበት የኢየሱስን የሰላምና የመዳን ወንጌል በመናገር ነው፤ ከዚህ አንሶ ከተገኘ ግን በኢየሱስ እንዳፈረ እንጂ ምንም ሊባል አይችልም፡፡
የደቀ መዝሙርነት መለኪያው
   አንድ ነገር ያለ መለኪያ ስፍሩም ልኬቱም፤ እውነታውም አይታወቅም፤ ስብከትና ትምህርት ኢየሱስን ማዕከል ካላደረገ ሰው፤ ሰው መሽተቱ፤ እጅ እጅ ማለቱ አይቀርም። እየሆነ የምናየውም እውነት ይህ ነው። በክርስቶስ ወንጌል የተሰጠውን ጨውና ብርሃንነት ታፍሮበት ፖለቲካና ዲስኩር ሲደነቅና ሲወደድ እንደ ማየት ለደቀ መዝሙር ምን አንገት የሚያስደፋ ነገር አለ?! ልክ ቱንቢው ሲዛነፍ የቤቱ ኹለንተና እንደሚዛነፈው፣ መለኪያው በትክክል ካልጸና በቀር ልከኛ ኑሮና አምልኮ፣ ትምህርትና ልምምድን ማግኘት ፈጽሞ ሊታሰብም፤ ሊገመትም አይችልም።
   ለክርስትናው የጽድቅ ኑሮ ልኩ ኢየሱስ ነው ካልን፣ ደቀ መዝሙር ከኢየሱስ ውጪ ማንንም መምሰል አይችልም። ከኢየሱስ ውጪ የሚመስለው ካለ በርግጥ እርሱ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር አይደለም። በኢየሱስ ያገኙትን “ዕውቅና” ይዞ ከአሻሮው ዓለማዊነትና የቤተ መንግሥት ዲስኩር መዶልና መጠጋት፣ “የንጉሥ ልጅ ኾኖ ባርነትን የመጐምጀት ያህል” መውረድ ነው። የምንኖረው የኑሮ መልክና በፍጻሜም የምንለብሰው መንፈሳዊ አካል የልጁ የክርስቶስ ኢየሱስን ነው።
   ለየትኛውም የክርስትና ሕይወትና ትምህርት መለኪያው ክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው፤ ከኢየሱስ ውጪ ያለ የትኛውም አገልጋይ እንደ ኢየሱስ የክርስትና መለኪያ ሊኾን አይችልም። በግለሰብ የሚመሩ አብያተ ክርስቲያናት፣ በቦርድ የሚተዳደሩ የዲያስፖራ አድባራት፣ በብሔርና በዘር የሚመሩ አያሌ አብያተ ክርስቲያናት መለኪያቸው የሚመሯቸውን ግለሰቦች ወይም ቡድኖች ወይም ቦርዶችን ከመኾን እንደማያልፍ ልኬታቸውን ቀርቦ የተረዳ ብቻ ያስተውለዋል።
   የወንጌል አገልግሎትን ከሚያጠቁት ቀዳሚ ተግባራት አንዱ፣ ከጥቂቶች በቀር አያሌ “ፊተኛ አገልጋዮች” ኹሉን አማኝና አገልጋይ በራሳቸው መልክና ቅርጽ፣ ቁመናና ልክ ለመቅረጽ የመቃተታቸው “ግለ ጽድቅ ጥረት” ነው። አገልግለን፣ አገልግሎታችን ከኢየሱስ ይልቅ እኛን ከጠቆመና ካመላከተ አይፎርሹ ፎርሸናል። በትክክል ባሪያዎች ከኾንን ማሳየት ያለብን የጌታችንን ፊትና መልክ፤ ትምህርትና ሕይወት ብቻ ነው። በግለሰብና በግለሰቦች፤ በቦርድና በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት የሚተዳደሩ አብያተ ክርስቲያናት ከተጋረጠባቸው አደጋዎች አንዱ ይህ ነው ማለት ነው፤ ባሪያ የገነነባቸው እውነተኛው ጌታና የቤቱ አባወራ የተዘነጋባቸው አብያተ ክርስቲያናትን ቤት ይቊጠራቸው።
   ደቀ መዝሙርነት መለኪያው ለጌታው በሚሰጠው ጆሮ ልክና በትክክል ልክ እንደ ጌታው ቃል ከመታዘዙ ላይ ነው። በትክክል መታዘዝ በትክክል ከመስማት ይጀምራል፤ ቅዱስ ቃሉን በትክክል ከመጽሐፍ ቅዱስና ከመንፈስ ቅዱስ አብርሆት የሚሰማና የሚያደምጥ ለመታዘዝና ለመሸነፍ ልቡ አይደድርም። ጌታ ኢየሱስን በትክክል መስማት የእውነተኛ ደቀ መዝሙር ኹነኛ ጠባይ ነው፤ መታዘዝና እንደ ቃሉ መኖርና መፈጸም ደግሞ የታመነ አገልጋይ መገለጫው ነው።
ተፈጸመ፤ በረድኤተ ኢየሱስ፤ አሜን።

2 comments:

  1. ደቀ መዝሙርነት መለኪያው ለጌታው በሚሰጠው ጆሮ ልክና በትክክል ልክ እንደ ጌታው ቃል ከመታዘዙ ላይ ነው። በትክክል መታዘዝ በትክክል ከመስማት ይጀምራል፤ ቅዱስ ቃሉን በትክክል ከመጽሐፍ ቅዱስና ከመንፈስ ቅዱስ አብርሆት የሚሰማና የሚያደምጥ ለመታዘዝና ለመሸነፍ ልቡ አይደድርም። tebarek wendmachin

    ReplyDelete
  2. geta lib yistachew

    ReplyDelete