Thursday 6 June 2019

“እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ” (ሐዋ. 1፥9)

Please read in PDF
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን መካከል ከተነሣ በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ፣ “አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ ራሱን አሳያቸው” (ሐዋ. 1፥3)። የጌታችን ትንሣኤ እውነታነቱ በታሪክ ማስረጃም ጭምር ያሸበረቀ ነው፤ ታሪክ ሊክደው በማይችለው መልኩ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን መካከል ሰውነቱን ሳይጥል ተነሥቶአል። መነሣቱንም ለደቀ መዛሙርቱ በብዙ ማስረጃዎች አስረግጦ አሳይቶአል፤ ለድንጉጥ፣ ለተጠራጣሪ፣ ተስፋ ቆርጠው ወደ ገዛ መንገዳቸው ላዘነበሉት፣ በሃዘን ለተሰበሩት፣ ብዙ ጊዜ በመፍራትና በመስጋት ወደ ኋላ ለመመለስ ያመነቱ ለነበሩት ደቀ መዛሙርት ባለ ብዙ ምሕረት ኢየሱስ ሳይታዘባቸውና ሳይጠየፋቸው ፍጹም በተደጋጋሚ ተገልጦ ታያቸው፤ ራሱንም ገለጠላቸው።


“ከትንሣኤ በኋላ ኢየሱስ የታየው ለሚከተሉት ነው፦ (1) ለመግደላዊት ማርያም (ዮሐ. 20፥11-18)፤ (2) ከመቃብሩ ደርሰው ለተመለሱት ሴቶች (ቊ 9-10)፤ (3) ለጴጥሮስ (ሉቃ. 24፥34)፤ (4) ለሁለቱ የኤማሁስ መንገደኞች (ሉቃ. 24፥13-32)፤ (5) ከቶማስ በስተቀር ለሁሉም ደቀ መዛሙርትና አብረዋቸው ለነበሩት ለሌሎች (ሉቃ. 24፥36-43)፤ (6) ከአንድ ሳምንት በኋላ እሁድ ምሽት ላይ ለደቀ መዛሙርቱ በሙሉ (ዮሐ. 20፥26-31)፤ (7) በገሊላ ባሕር አጠገብ ለሰባት ደቀ መዛሙርት (ዮሐ. 21፥1-25)፤ (8) በገሊላ ለአምስት መቶ ሰዎች (ቊ 16-20ን ከ1ቆሮ. 15፥6 ጋር ያወዳድሩ)፤ (9) ለያዕቆብ (1ቆሮ. 15፥7)፤ (10) ታላቁን ተልእኮ ለተቀበሉት ደቀ መዛሙርት (ቊ 16-20)፤ (11) በዕርገቱ ጊዜ ለነበሩት ሐዋርያት (ሐዋ. 1፥3-11) እና (12) ለሐዋርያው ጳውሎስ (1ቆሮ. 15፥8)።”[1]
ተወዳጁና ሰውን አፍቃሪው ኢየሱስ ለእኒህ ኹሉ ኀጢአተኞች፣ ከታላቅና ወደር ከሌለው ምሕረቱ የተነሣ በእውነት እንዲያምኑበት በተደጋጋሚ ተገለጠላቸው፤ እግዚአብሔር ብዙ ዕድል በተደጋጋሚ የሚሰጠን በትክክል ወደንና ፈቅደን አምነን እንድንከተለው ስለሚሻ ነው። በተለያየ ኹኔታና በተለያየ መንገድ ውስጥ ላሉ ሰዎች መገለጡም የሚያመለክተውም ይኸንኑ ነው። አዎን እርሱ፣ “በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወዶአቸዋል” (ዮሐ. 13፥1)።
ጻድቅና ቅዱስ ሳለ፣ እንዲህ ላሉትና ላልታመኑት ደቀ መዛሙርት የመንግሥቱን ነገር አስተማራቸው፤ የአባቱንና የፍቅር መንግሥቱን እውነት ሳይሸሽግ ገለጠላቸው፤ እርሱ እንደ ብዙዎች መምህራን አይደለም፤ ብዙ መምህራን ለተማሪዎቻቸው ኹሉን ነገራቸውን አይገልጡም፤ አይሰጡምም። በዓለማችን ባሉ ብዙ ባህሎች ውስጥም ለአደራ በላተኛ አደራ አይሰጥም፣ ለማይታመን ሰው የእምነት ሥራ አይሰጥም፤ ጌታ ኢየሱስ ግን እንዲህ አላደረገም፤ ለከዳተኛው ጴጥሮስ ትልቅ አደራ ሰጠው፤ ለተጠራጠረው ቶማስ ሐዋርያነትን አልከለከለውም። እኛ ኹላችን እንዲህ ነበርን፤ ጌታ ኢየሱስ ግን በማያልቅ ምሕረቱ ኹላችንን አመነን፤ ወደደን፣ አፈቀረን፤ በማይጥልና በማይዝል ክንዶቹም ያዘን።
ጌታ ኢየሱስ የእግዚአብሔር መንግሥትን ጉዳይ የገለጠው በቤተ መቅደሱ ለነበሩት ለሊቀ ካህናቱ ሐናና ቀያፋ ሳይኾን፣ እጅግ ለተናቁትና ምንም ስፍራ ላልተሰጣቸው ከገሊላ [ከተናቁትመንደር] ለተጠሩ ቅዱሳን ደቀ መዛሙርት ነበር። ይህንም በብዙ ማስረጃ አረጋገጠው። አኹንም ለደቀ መዛሙርቱ የመጨረሻውን መገለጥ ከተገለጠላቸው በኋላ፣ ደግሞ በኹሉ ላይ ሥልጣን ያለውና ኹሉን ያሸነፈ ጌታ መኾኑን ይገልጥ ዘንድ ወደ ሰማያት ሲያርግ እየታያቸውና በትክክል ሊያስተውሉ በሚችሉበት መንገድ ነበር፤ መጽሐፍም እንዲህ በማለት ይገልጠዋል፤ “ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው” በማለት መጽሐፍ ይነግረናል።
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዓይናቸው በርቀት እንጂ በምትሐት አልተሰወረም፤ በዓይናቸው እያዩት እንጂ በመርቀቅ ከቅዱሳን ደቀ መዛሙርት አልተለየም። እየተናገራቸው ከፍ ከፍ አለ፤ በከፍታ ወደ ሰማይ እየራቃቸው ተለያቸው፤ ሥጋውን በመተው ያረገ አይደለም፤ ሲናገራቸው ይሰሙት እንደ ነበር እንዲሁ፣ ሲያርግም እንዲሁ በዐይኖቻቸው አይተውታል። ከሙታን መነሣቱ እውነት እንደ ኾነና ፈጽሞ ሊስተባበል እንደማይችለው ኹሉ፣ ወደ ሰማያት ከፍ ከፍ ብሎ ደመና ተቀብላው ማረጉም እውነትና ሊስተባበል የማይችል ነው።
   ደቀ መዛሙርቱ ከሙታን መነሣቱ እጅግ ደስታቸው እንደ ነበር እንዲሁ፣ ወደ ሰማያት ከፍ ከፍ ብሎ ማረጉም ደስታና በረከታቸው ነበር። ዕርገቱ አብ የሰጠው ተስፋ ወደ ምድር መምጣቱን እጅግ የሚያፈጥን ነው፤ (ሉቃ. 24፥49)። ቅዱሳን ደቀ መዛሙርት ጌታ ከፍ ከፍ እያለ በጌትነት በማረጉ አላዘኑም፤ ይልቁን እጅግ ደስተኞች ኾኑ እንጂ፤ ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ መውረድ ልደቷን ከአሥር ቀን በኋላ ታከብራለች፤ ታበስራለችም። ለዚያ መሲሑ ከፍ ከፍ ብሎ ማረግና በግርማው ቀኝ በጌትነትና በሊቀ ካህናትነት ሊቀመጥ ይገባዋል።
በምድርም በሰማይም ያለ ከፍታ ኹሉ የማይደርስበት ልዩ ከፍታ የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ከፍታ ነው፤ ለዚህ ነው፣ ብቻውን ሊመለክ፣ ሊመሰገን፣ ሊከበር፣ ሊፈራ፣ ሊወደድ፣ ሊፈቀር፣ ሊሰገድለት፣ ሊወደስ፣ ሊቀደስ … ይገባዋል የምንለው፤ የምድር ኹሉ ደስታ መሲሑ ኢየሱስ ሆይ! ዕርገትህን እናምናለን፤ በመሄድህም ደስ ይለናል፤ በመንፈስህም ስለምትባርከን እናመሰግንሃለን፤ አሜን።




[1] ምሉእ ሕይወት መጽሐፍ ቅዱስ ከነማብራሪያው ገጽ  1482-1483

2 comments: