Thursday 27 June 2019

ሰዶማዊነት - መዘንጋት የሌለበት ጉዳይ! (የመጨረሻው ክፍል)


የሰዶማውያን ስውር ደባ
    በግልጥ ማንነታቸው ቢመጡ የሚቀበላቸው እንደሌለ ያውቁታል፤ ስለዚህም ስውርና ሰዎች ቀስ በቀስ ወይም በድንገት እንዲላመዱ የሚያደርጉባቸው መንገዶች አሏቸው፤ ለምሳሌ፦ የታወቁ የፊልም አክተሮችን በዋና ተዋናይነት ማጫወት፣ በሕጻናት ፊልሞች ውስጥ ሰዶማዊነትን መሰንቀር [ስንቶቻችን ለሕጻናቶቻችን ፊልሞችን አስቀድመን አይተን መርጠን እናቀርብላቸዋለን?]፣ በአኹን ሰዓት ከክርስቲያን ፊልሞች በቀር በማናቸውም ፊልሞች ላይ እጅግ በአብላጫው የሰዶማውያንን ሃሳብ እናያለን፣ ቀስ በቀስ ያላምዱናል፣ በቀዝቃዛ ውኃ ጥደውን ቀስ አድርገው እሳቱን እያነደዱ መቀቀልና መፍረስን ያላምዱናል፤ ምልክቶቻቸውን በተቃውሞ መልክ እንድናሠራጭ ይቈሰቁሳሉ፤ በዚህ ረገድ የአገራችን የቅርቡ ኹኔታ በሚገባ ተሳክቶላቸዋል፡፡

   በባለፉት ጥቂት ሳምንታት በአገራችን የግብረ ሰዶማውያንን ተቃውሞ ለማሰማት እጅግ አያሌ ሰዎች ባንዲራቸውንና አድራጎታቸውን ጭምር ሲያስተዋውቁ አስተውለናል፤ አንዳንዶችማ አንዳንዱን ምስልና ምስለ ድምጽ ከየት አመጡት? ወይም እንዴት አገኙት? የሚያስብል ጥያቄ ኹሉ ያጭራል። በእርግጥ አንዳንድ ሰዶማውያን ተቃዋሚ መስለው ምስሎቻቸውና ምስለ ወድምጻቸው እንዲሠራጭ እንደሚያደርጉ እሙን ነው። በተለይም የምዕራቡ ዓለም “ቀሳውስትና አገልጋዮች” በዚህ የተካኑ ናቸው፤ ጨላጣ ሰዶማውያን ኾነው ነገር ግን ራሳቸውን እንደ ተቃዋሚ አድርገው ቀርባሉ! [የአገራችንንስ ማን አየልን?]፡፡
 ግብረ ሰዶማውያን፣ ሰዶማዊ አባላትን የሚመለምሉበት አንዱ መንገድ እንደ ሽብርተኞች፣ በማኅበራዊ ሚድያ በተለይም እንደ ፊት ገጽ(facebook) ባሉ መንገዶች ነው፤ ለዚህም ማባበያ ይኾን ዘንድ ቀላል የማይባል የገንዘብ እርዳታዎችን ይለግሳሉ፤ የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊና የፊት ገጽ ባልንጀሮቹ በፊት ገጽ እጅግ ልንጠብቃቸው ከማንችላቸው ሰዎች የሰዶማዊነትን ጥያቄዎችን ሰምተዋል፤ [የፊት ገጽ ባልንጀሮቻችሁ እነማን ናቸው? በፊት ገጽ የምታወሩአቸው ሰዎች ምን ያህል ታውቁአቸዋላችሁ? በሕይወታቸው ስለማታውቋቸው አገልጋዮች ምን ያህል ከዚህ ርኩሰት ንጹሐን ስለመኾናቸው “እርግጠኞች” ናችሁ?
   ለመኾኑ አንዳንድ የሚታዩና በሰው ዘንድ ተወዳጅ አገልጋዮችን ግብረ ሰዶማውያን ተከታዮቻቸው የሚያደርጉት ለምን ይመስሏችኋል? ቀላል ግን አደገኛ የወጥመድ መንገድ ነው፤ ከአገልጋዮች ጀርባ ያሉትን አማኞች ለሰዶማውያን “ቀለል ባለ መንገድ ለግብዣ” ለማቅረብ ስለሚመች ነው። አንዳንዶች የአገልጋይን ድካምና ኾን ብሎ በተለሳለሰ ጠባይ እንደ ተኵላ የሚያደባ ማንነት መለየት ባለመቻል፣ በአንድም በሌላም መንገድ ድጋፋቸውን ሲሰጡ የተለመደ ከኾነ ሰነባበተ። ከግብዝነት ብዛት የፈሪሳውያንን የሃይማኖት ሊቃውንት ኢየሱስ “ወዮላችሁ” ብሎ መናገሩን ሊተቹ ኹሉ ይቃጣቸዋል፤ እንደ ፈሪሳውያን ያሉ አገልጋዮችን “እሹሩሩ” ባይ በዘመናችን የትየለሌ ናቸውና፣ ራሳችሁን ከኀጢአት ብቻ ሳይኾን ወደ ኀጢአት ባሕር ከሚያደርሱ የኀጢአት ጅረቶችም ጠብቁ፡፡
አለሌ ስህተቶች
   ግብረ ሰዶማውያን አስብተው ሊያርዱን ከልብ ተግተው እየሠሩ ነው፤ ኦባማ ጥቁርና ነጭ ጸጉር ባወጣ፣ የማታ የማታ ሊመሽ ከሥልጣኑ ሊሰናበት “አንድ ሃሙስ ሲቀረው” የሠራው አጸያፊ ስህተት፣ የግብረ ሰዶማውያንን “መብት” ማክበሩ ነበር፤ የአሜሪካ ሕዝብ በአንድ ወቅት “የወንጌል ፋና ወጊ” ነበር፤ መደላደልና የሃብት ክምችት ሲመጣ ግብረ ሰዶማዊነትን መብት ብለው በአብላጫ ቊጥር አጸደቁት፤ ከእኛ አገር ጋር እጅግ ተቀራራቢ የማኅበራዊና ሃይማኖታዊ እሴት ያላት አየርላንድ፣ ግብረ ሰዶማዊነትን “yes” ብላ የተቃራኒ ጾታ ጋብቻን “no” ብላ ስታጸድቅ ያልደነገጠ እውነተኛ አማኝ ይኖር ይኾንን?
  በአኹን ሰዓት ከአገራችንስ ሚኒስትሮች አንዳንዶች ሴታዊና ወንዳዊ ሰዶማዊ መኾናቸውን ከሐሜት በዘለለ ስንሰማ ምን ተሰምቶን ይኾን? ከጥቂት ዓመታት በፊት በአዲስ ዓመትና በበዓላት ለታራሚዎች ከሚደረገው ይቅርታ ውስጥ ሰዶማውያንም እንዲካተቱ ጥያቄ ቀርቦ እንደ ነበር ስንሰማስ፣ መንግሥት አቋሙ ምንድር ነው? ማለታችን አይቀርም፣ “በወንጀል ሕጉ የተቃወመውን ወንጀልና ኃጢአት በጓዲያ ማሽሞንሞን ለምን አስፈለገው?” ያልን ስንቶች እንኾን? ድህነታችንን ተተግነው በጉዲፈቻ ከአገር የሚወሰዱት ሕጻናት አድራሻቸውና መድረሻቸው የት ነው? … እውን ተከታታይ አላቸውን?
   ማረሚያ ቤቶቻችን ከዚህ ድርጊት ምን ያህል ጽዱ ናቸው? አዳሪ ትምህርት ቤቶቻችን ውስጥ ምን ይኖር ይኾን? ኹለተኛ ደረጃና ከፍተኛ የትምህርት ተቋሞቻችን ውስጥ የሚሰማው ጆሮ ጭው የሚያደርገው ነገር ምነው ችላ ተባለ? የከፍተኛ ትምህርት ቤቶቻችንን ድንገተኛ ፍተሻ እያደረጉ አስነዋሪና አጸያፊ የዝሙትና የርኩሰት ዕቃዎችን ከማጽዳት በዘለለ፣ መዝሙር እያደመጡ፣ ከቤተ ክርስቲያን ሳይጠፉ፣ እያገለገሉ፣ ሰዶማዊነትን ራሱ እየተራገሙ … እንዲህ ባለ ነውር ውስጥ ለሚመላሱ አማኞችና አገልጋዮች ወንጌልን እንደ ገና በአዲስ መልክ መስበክ እንዳለብን አስበን ይኾን? የመናፍቃንና ያላመኑ አሕዛብ የሚያስፈልጋቸው ያህል ለሰዶማውያንስ እንደ አዲስ ወንጌል መስበክ አያስፈልግ ይኾንን?!
የመንግሥትና የሕዝብ ልልነት
  በአንድ ወቅት በሻሸመኔዋ ኩየራ አንድ መነኩሴ በአዳሪ ሕጻናት ወንዶች ተማሪዎች ላይ እንዲህ ያለ አጸያፊ ተግባር በብዙ ትብብር ተይዞ ለፍርድ ቢቀርብም፣ የፍትሕ አካላት ባመቻቹለት መንገድ በቀላሉ ከአገር እንደ ወጣ፤ መዝገቡም እንደተዘጋ አንስተውም፤ መገናኛ ብዙሃንም ፍርድ ቤት መቅረቡን እንጂ፣ ከተከሰሰ በኋላ ያለከልካይ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ያለ ከልካይ ዘና ብሎ እንደ ወጣ አልነገሩንም። የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ ያ መነኩሴ ከዘጠኝ ያላነሱ ሕጻናት ላይ ድርጊቱን መፈጸሙን ካያቸው ምስሎችና ካነጋገራቸው ማስረጃዎች ማረጋገጥ ችሎአል። በሰሜን ሸዋ ፍቼ ውኃ ልትቀዳ ወደ ወንዝ የምትወርደዋን አሥራ ስምንት ያልሞላትን ሴት ልጅ፣ በኃይል አፍነው ሌሊቱን ሙሉ ድንግልናዋን ሳይነኩ ፊንጢጣዋን ሙሉ ለሙሉ ቀደው ከጫካ ጥለው ስለተገኘችው ሴት ያልተሰቀቀ ድምጹን አሰምቶ ያልጮኸ ማኅበረ ሰብ እንዳለን ሳስብ ነፍሴ እጅግ ትጨነቃለች፡፡
   በአንድ ወቅት “ሰው ኹሉ በፊቱ መልካም የኾነውን ያደርግ በነበረበት ወራት”፣ እንዲህ ያለ ተግባር በአንዲት ሴት ላይ በእስራኤል መካከል ተፈጽሞ፣ ውጤቱ ግን ለአንድ ነገድ መደምሰስ ምክንያት ኾኖአል፤ ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ያሉና በገለዓድ ምድር የሚገኙት እስራኤላውያን በአንድነት ተነሥተው፣ የጊብዓ ሰዎች እንዲህ ያለውን ነውር በመፈጸማቸው ምክንያት እንደ አንድ ሰው መቱአቸው፤ የብንያም ሰዎች ግብረ ሰዶማውያኑን፣ ወስላቶቹን፣ መጋጦቹን አሳልፈው ባለመስጠት ከጊብዓ ሰዎች ጋር በመስማማታቸው ምክንያት ታላቅ ቊጣ ወርዶባቸዋል፤ (መሳ. 19-21)፡፡
 ምን እስከምንኾን እንደምንጠብቅ ግራ ነው፤ ጆሮ ጭው የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች በመካከላችን ቢፈጸሙም ሥነ ምግባርና ሞራላችን እጅግ ላሽቆአል፤ ኀጢአትን ፊት ለፊት ላለመጸየፍ መጽሐፍ ቅዱስን በልካችን ሰፍተን ክንብንብ ብለን ለብሰናል! ጌታ ለምድራችን ኢትዮጵያ ምሕረት እንዲያደርግ እንማልዳለን፤ ከወራት በኋላ የሚመጡት ግብረ ሰዶማውያን አዘናግተው ምድራችንን እንዳያረክሷት እጅግ ተጠንቅቀን መሥራት እንዳለብን መዘንጋት የለብንም፤ ለዚህም ቤተ ክርስቲያን ከምንም ጊዜ በላቀ በጸሎት፣ ምእመናንንና ምእመናትን በማንቃት፣ ወንጌል በመመስከር ቀዳሚ ድርሻዋን ልትወጣ ይገባታል! ጌታ ኢየሱስ ሆይ! ራራልን፤ ልክፉዎችም አሳልፈህ አትስጠን፤ አሜን!!!

1 comment: