Wednesday 19 December 2018

“ግብረ ሰዶማዊ ሎጐ” በስፖርት መንደር!

 Please read in PDF
 የሰው ልጅ በኀጢአት ከወደቀ በኋላ፣ ነገሮችን ኹሉ ይቃኝ የነበረው በወደቀውና ከእግዚአብሔር በተለየው የኀጢአት ዝንባሌው ነው።አዳም በኀጢአት ሲወድቅ ከእግዚአብሔር ተለየ፤ በመለየቱ ልክ እንደ እርሱ ያለውን ከእግዚአብሔር የተለየ ልጅን ወለደ፤ (ዘፍ. 5፥3) ከእግዚአብሔር የተለየው ልጅ ቃየል ወንድሙን በመግደሉ (ዘፍጥ. 4፥8) “ኀጢአት በደጁ የምታደባበት፣ ፈቃድዋም ወደ እርሱ” ኾነች፤ (ዘፍጥ. 4፥7)። የኀጢአተኝነት ዝንባሌ በትውልዱ ልክ የጥፋት ውኃ እያየለው እንደ ሄደው እንዲኹ ተንሰራፊና ተስፋፊ እየኾነ ሄደ፤ (ዘፍ. 7፥19)።




   ቃየል ከተማን ሊመሰርት ከእግዚአብሔር ፊት ወጥቶ ወደ ኖድ ምድር ሲሔድ (ዘፍ. 4፥16)፣ በሚመሰርታት ከተማ ላይ የራሱን የኀጢአተኝነት ዝንባሌ ሊያሳርፍ እንደሚችል እሙን ነው፤ ከተማ “ሰዎች በአንድነት ለመኖር ሲፈልጉ ውሃ በሚገኝበትና ለምሽግ በሚመችበት አምባ ወይም ተራራ ላይ ቤቶቻቸውን የሚሠሩበትን ስፍራ ያመለክታል”፤ “ታላላቅ” ከተሞች የታላቅነታቸው መለኪያ አንዱ የሕዝብ ብዛታቸውና የመከላከል አቅማቸው፣ የምሽጐቻቸው ጥንካሬ ነበር። ነነዌን በምሳሌነት ማንሣት ይቻላል (ዮና. 1፥2፤ 4፥11)። በከተማ ውስጥ ጐልተውና ደምቀው ከሚወጡ ነገሮች አንዱ ኅብረተ ሰባዊ ኀጢተኝነት አንዱና ዋናው ነው።
    ለዚህ መስፋፋት እንደ ቀኝ እጅ ከሚያገለግሉ ነገሮች መካከል ዋነኛው ደግሞ፣ ስፖርት ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ነው። በአገራችን ኢትዮጵያ የእግር ኳስን ስፖርት ከትንሽ እስከ ትልቅ፣ ፊደል ከቈጠረው እስካልቈጠረው ድረስ በሚሊዮናት የሚቈጠር ሰው ይደግፈዋል፣ ያወራበታል፣ ይጋደልበታል፣ ይሰዳደብበታል፣ ይኳርፈበታል፣ ይቧደንበታል፣ ይቋመርበታል፣ ይጨቃጨቅበታል፣ ካራ ይሳሳልበታል፣ ጩቤ ይማዘዝበታል፣ ደም ይፋሰስበታል፣ የኤፍ ኤም ሬዲዮኖቻችንና ቲቪዎቻችን የማለዳና የሠርክ አሰልቺና ጆሮ አደንቋሪ ከንቱ ልፈፋቸውን “ሳይታክቱ” ይለፈፉበታል … ።
   በአውሮፓ ምድር ደግሞ ላሉ ክለቦችና ተጨዋቾች ደግሞ፣ የእግር ኳስ ስፖርት ዓመታዊ ገቢያቸው በቢሊዮንና ትሪሊዮን የሚቈጠር እንደ ኾነ ከኹሉ ሰው ፊት የተሰወረ አይደለም። በእውኑ ይህ ኹሉ ብር የሚፈስስበት ስፖርት፣ ስርፖት ብቻ ነውን? ለሆስፒታሎች የማይበጀት፣ ለድሆች የማይታሰብ፣ በጦርነት ለፈረሱ ሕዝቦች የማይቆረስ፣ ለታረዙት የማይመጸወት፣ ለሕሙማን የማይቸር … አስፈሪ ብር ለእግር ኳሱ ሲንፎለፎልና ሲንዶለዶል እውን የጤና ነውን?
   ቀዳሚው የኪዳን ሕዝብ እስራኤል፣ ስፖርትን ልማዱ ያደረገ አልነበረም።ስፖርት በቀጥታ ትስስሩ ከአሕዛብ አማልክትና ባህሎቻቸው ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት ነበረው። በጥንት ግሪክ እያንዳንዱ ፍጡር ብቻ ሳይኾን፣ እያንዳንዱ የሰው አካል[ብልት] ተመላኪና ክብር የሚሰጠው ነበር። በጥንት የግሪክና የሮማ ኮሎሴየምና አሪና(እስታዲየም) ሰዎች እስኪሞቱ ድረስ የሚደረጉ የስፖርት ፍልሚያዎች ነበሩ። በዚህ ኹሉ ውስጥ በኮሎሴየሙ ዙርያ የተሰበሰበው ሕዝብ በሰዎች መሞት እንኳ ይዝናና ነበር፤ በዋና ምሳሌነት የክርስቲያኖችን ለአውሬ በመሰጠት ይደረግ የነበረውን ፌሽታና መዝናናትን ማስታወስ በቂና አሳማኝ ነው።
  በጥንቷ ግሪክ አፍሮዳይት[ቬኑስ ቬነሪ] የተባለችው የውበትና የፍቅር አምላክ እና አርጤምስ[አርቴሚድ ድያና] የተባለችው የአደን፣ የበረሃና የጨረቃ አምላክ፣ በልዩ ልዩ የስፖርትና የጭፈራ እንቅስቃሴ የዝሙት መስዋዕት ይቀርብላቸው ነበር፤ ለዚህም አጵሎን[አፓሎ] የተባለው የሙዚቃና የዘፈን፣ የትንቢትና የዕውቀት፣ የእርሻና የመንጋ ጠባቂ አምላክ፣ ለእነዚህ ሴት አማልክት ሙዚቃና ዘፈኑን ሲያሰናዳ፣ አቴና[ፓላድ ሜኔርቫ] የተባለው የጥበብ አምላክ ደግሞ ዘፈኑን፣ ጭፈራውን፣ ስፖርቱን፣ ዝሙቱን … ኦርጂ በተባለ መንገድ የልቅ ወሲባዊና የመጠጥ አምላክ ከኾነው ዲዮኒስ[ባኮ] ጋር “በመነጋገር” ያቀርበዋል። በዚህ ሥፍራም ኦርጂ የተባለውን ዳንኪራ፣ ዝሙትና ዘፈን፣ መዳራትና መስከር፣ ራስን ስቶ መዘረር ኹሉ እንደ ቅዱስና ትክክለኛ ተግባር ይቈጠራል።

   ከዚህ የተነሣ የመጀመሪያይቱ ቤተ ክርስቲያን የሮምንና የአቴናን ስፖርትና በአፈጻጸሙ የሚታየውን መጨናነቅ፣ መተፋፈን፣ ዝሙት፣ ጭፈራ፣ ግድያ … እጅግ አጥብቃ ትቃወም ነበር። ምክንያቱም ድርጊቱና መንፈሱ እጅግ ኢ መንፈሳዊና ከሥነ ምግባር የጐደለ ተግባር ነውና። ልክ እንዲሁ በዛሬ ዘመንም ሰዎች ለስፖርት ብዙ ዋጋ ይከፍላሉ።  እርግጥ ነው፣ ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረ፣ “ሰውነትን ለሥጋዊ ነገር ማስለመድ ለጥቂት ይጠቅማልና” (1ጢሞ. 4፥8) መጠነኛ ስፖርት ለሰው ጥቅም ቢኾንም፣ ነገር ግን ሰው ይህን ያህል በስፖርት ተስቦ አብላጫ ጊዜውን ስፖርት ይዞት ስናይ የሚገባን መንፈሳዊ እውነት የኅብረተ ሰባችን ኀጢአት መበከልንና መዋጥን ነው። ደግሞም “ሰውነትን ለሥጋዊ ነገር ማስለመድ ለጥቂት የሚጠቅመው፣ እግዚአብሔርን መምሰል የአሁንና የሚመጣው ሕይወት ተስፋ ስላለው፥ ለነገር ሁሉ ነው”።
   ለዚህ ደግሞ የባለፈውንና በአውሮፓ ምድር የእግር ኳስ ሜዳዎች የተገለጡትን፣ አስደንጋጭና ጆሮ ጭው አድራጊ ትዕይንቶችን መመልከት በቂ ነው። ግብረ ሰዶማውያን ሰተት ብለው በሜዳው ላይ ራሳቸውን ገለጡ፤ ከመጀመሪያውም በኀጢአት የተበከለውን የስፖርት ዐለም “እጅግ” ሊያረክሱት፣ ሊያጅሉት፣ ዐመጻውን በመላው ዐለም በተመሳሳይ መልኩ እንዲፈጸም ለማድረግ በነውር ማንነታቸው GLBTዎች [እንደ አንድ ወንድም አገላለጥ ግልብጦች] ተገልጠዋል!

   ዘወትር ማኅበረ ሰብ ከእግዚአብሔር ሲለይ በስውርና በግልጥ ኀጢአት ተጠልፎ ይወድቃል።“እግዚአብሔርን ለማወቅ ባልወደዱት መጠን እግዚአብሔር የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው፤” (ሮሜ. 1፥28) እንዲል፣ ዝንባሌውና ምርጫው፣ ፍላጎትና መሻቱ ከተፈጠረለት ዐላማ በተቃራኒ ይኾናል። ትልልቅ ከተሞች የፈረሱትና በጥፋት እሳት የተገለጡበት በኃጢአቶቻቸው እንደ ኾነ አለመዘንጋት ብርቱ ማስተዋል ነው፤ የስፖርት ማኅበረ ሰብ ዛሬ በግልጥ እግዚአብሔር አምላክን ከሚቃወሙ ግብረ ሰዶማውያን ጐን መቆሙን አሳይቷል፤ በማይረባ አእምሮ ተላልፎ ሊሰጥ በራሱ ፈርዷል። ይህ ምን ያህል የማኅበረ ሰብን ከእግዚአብሔር ይልቅ ለዚህ ዐለም እንደ ተገዛና ዐለምን በመውደድ እንደ ታወረ ያሳያል፤ ከዚህ ባለፈ ከምን ጊዜውም የጌታ ኢየሱስ መምጫ መቃረቡንም ያመለክታል።     
    ተወዳጁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ የስፖርትን ነገር እጅግ አሳንሶ፣ ክርስትናን እጅግ በጣም አልቆ ሲናገር ኹለቱን በንጽረት ያቀርባል፦
1.     ስፖርት ጠንካራና የታወቁት ብቻ ተጫዋቾች ይጫወታሉ፤ ሌሎች ግን በዙርያው ተኮልኩለው ተመልካች ናቸው፤ በክርስትና ውድድር ግን ኹሉም ተሳታፊ፣ ሩጫውን ጨራሽ ደግሞ የሕይወት አክሊል ተሸላሚ ነው፤ (1ጢሞ. 6፥11፤ ዕብ. 12፥1፤ ራእ. 2፥10)፣
2.    ምድራዊ ስፖርተኞች ለሚጠፉ ክብር ይሮጣሉ፤ በክርስትና የሚሮጡት ግን የማይጠፋውን ለማግኘት በእምነትና በመጋደል ይሮጣሉ (1ቆሮ. 9፥25፤ 2ጢሞ. 2፥5)፣
3.    በዓለማዊ ስፖርት የቀድሞ ድሎች ተረስተው የአኹኑ ብቻ ይከበራሉ።በክርስትና ውድድር ግን ኹል ጊዜ ለወደ ፊት ወደምንቀበለው አክሊል እንመለከታለን፤ (1ቆሮ. 9፥24፤ ፊል. 3፥10፤ 2ጢሞ. 2፥4፤ ዕብ. 12፥1)።
   እንኪያስ ምርጫችንን እናስተካክል! ርቀን ሳንሄድ፣ ቀናችን ሳይዋገድ፣ ጉብዝናችን ሳይነጥፍ፣ መቅረዛችን ሳይወሰድ፣ “ጨውነታችን” ድንጋይ ተብሎ ሳይጣል ... እንመለስ፤ ለሚበልጠውና ለማይጠፋው ሩጫ ተግተን በመጋደል እንሩጥ! ከርኩሰቱ መንደር እንውጣ! የመዳን ሰዐት አኹን ነው! በጌታችን ኢየሱስ በትክክል በማመንና በእርሱ የጽድቅ ሕይወት በመኖር ከግልም ከማኅበረ ሰብም ኀጢአት እንሽሽ! ግብረ ሰዶማዊነትን በግልጥ እንደ ጌታ ኢየሱስ ቃል እንጠየፍ! አምርረን እንቃወም፣ በዚህ ነውር የተጠላለፉትን በፍቅር ራርተን እንታደግ! መንፈስ ቅዱስ በነገር ኹሉ ማስተዋልን ያድለን፤ አሜን።

ዋቢ መጻሕፍት
ü  ኪዳነ ወልድ ክፍሌ/አለቃ/፤ መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ፤ 1948 ዓ.ም፤ አርቲስቲክ ማተሚያ ቤት።
ü  የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት 6ኛ እትም፤ አዲስ አበባ፤ ባናዊ ማተሚያ ቤት።
ü  ቄስ ኮሊን ማንሰል፤ ትምህርት ክርስቶስ 2 እትም፤ 1999 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ ንግድ ማተሚያ ድርጅት።
ü  አበራ በቀለ(ሊቀ ጉባኤ አባ)። ትምህርተ ሃይማኖት እና ክርስቲያናዊ ህይወት። 1996 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ። ንግድ ማተሚያ ድርጅት(ማህበረ ቅዱሳን)። ገጽ.276

ü  ዲያቆን በለጠ መርዕድ፤ ባዕድ አምልኮ፤ 1995 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ አለም ማተሚያ ድርጅት።

4 comments:

  1. beYEsus sim kemidr lay yinekel

    ReplyDelete
  2. እግዚኦ መሀረነ ክርሥቶሥ 🙏

    ReplyDelete
  3. ነገ ለኛም አይቀርም ዛሬ መዘጋጀት ግድ ነው

    ReplyDelete
  4. እግዚአብሄር ያጥፋቸው

    ReplyDelete