Thursday 5 January 2017

“ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት … ተወልዶላችኋልና”(ሉቃ.2፥11)

   Please read in PDf
የዳዊት ከተማ ቤተ ልሔም ናት፤ የስሟ ትርጓሜም “የእንጀራ ቤት” ማለት ነው፡፡ በያዕቆብ ዘመን “ኤፍራታ” ተብላ ትጠራ ነበር፤ ቤተ ልሔም የብዙ ባለታሪክ ቅዱሳን አባቶች አገር ናት፤ የኢብጻን፣ የቦዔዝ፣ የእሴይና የዳዊት ከተማ ናት፤ (መሳ.12፥8 ፤ ሩት.2፥4 ፤ 1ሳሙ.17፥12)፡፡ ዳዊት ንጉሥ ስለመሆኑ በሳሙኤል እጅ በቤተ ልሔም ተቀባ፤ (1ሳሙ.16፥13)፡፡ በነቢዩ በሚክያስ አንደበትም፥ “አንቺም ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል፤”(ሚክ.5፥2) ተብሎ እንደተነገረው በዚህችው በዳዊት ከተማ ቤተ ልሔም ክርስቶስ ኢየሱስ ተወለደ፤ (ሉቃ.2፥4)፡፡

    ቤተ ልሔም ከይሁዳ አእላፋት ከተሞች መካከል ‘እዚህ ግቢ የማትባል’ ከተማ ናት፤ በነቢዩ አንደበትም ታናሽ የተባለች ናት፡፡ መሲሑ ጌታ ግን በፍልስፍና ወደገነነችው አቴና ወይም የሃይማኖት ሊቃውንት ወደበዙባት ወደኢየሩሳሌም ፈጽሞ አልመጣም፡፡ ሰዎች የጠበቁት ወደ“ገናናዎቹ” ከተሞች እንደሚመጣ ነበር፤ እርሱ ግን በከብቶች በረት ፍጹም ማንም ሊሆን ይችላል ብሎ ባልጠበቀበት ሥፍራ በቤተ ልሔም ተወለደ፡፡ ቤተ ልሔም ከመሲሑ የተነሣ ስሟ የገነነና ከይሁዳ ከተሞች የበለጠ ስምን ያዘች፡፡ መሲሑ በእርሷ ተወልዷልና፡፡ ክርስቶስ ዝቅታን ያከብራል፤ ደግሞም ከፍ ከፍ ያደርጋል፡፡ የተናቀችይቱ ከተማ ክርስቶስ በእርሷ በመወለዱ ምክንያት ከይሁዳ ከተሞች ይልቅ ከፍ አለች፡፡ ዛሬም የኢትዮጲያም ሆነ የየትኛይቱም አገር ክብሯና ልዕልናዋ ክርስቶስ ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ ያለኢየሱስ ለመክበር የምታስብ ከተማ እርሷ፥ “እነሆ፥ ቤቷ የተፈታ ሆኖ ይቀርላታል፤” (ማቴ.23፥38)፡፡ ጌታ ኢየሱስ የሕይወት ብቻ ሳይሆን የከተማም ሞገስ ነው!
    በሰዎችም ረገድ ብንመለከት፥ በዚያ ስፍራም የተገኙት በምድራዊ ኑሯቸው የማይገናኙ ሁለት “ተቃራኒ” ቅዱሳን ናቸው፡፡ እጅግ በጣም በብዕል ድኾች የሆኑ[ኑሯቸውን በአናጢነት ሙያ የሚመሩት ቅድስት ማርያምና አረጋዊ ዮሴፍ፣  እረኞችና ሌሎችና] እጅግ ባዕለ ጠጋ የነበሩ የምሥራቅ ነገሥታት፡፡ ሁለቱም የእግዚአብሔር መንግሥት ከመካፈል የሚከለክላቸው ምንም ነገር የለም፡፡ እግዚአብሔር ልባዊ ማንነትን እንጂ ቁሳዊ ማንነትን ፈጽሞ አይመለከትም፡፡ ድኾች ብንሆን ባዕለጠጎች ብንሆን ሁሉን ለጌታ ክብር እናደርገዋለን እንጂ በልባችን መመካትን አንጀምርም፡፡
    ብዙ አይሁድና ሊቃውንቱም ጭምር ክርስቶስ ከዳዊት ከተማ ከቤተ ልሔም እንደሚመጣ ያውቁ ነበር፤ (ማቴ.2፥5-7 ፤ ዮሐ.7፥42) ነገር ግን ማወቃቸው ምንም አልጠቀማቸውም፤ እርሱ ከቤተ ልሔም ከድኾች ቤተሰብ ተወልዶ “የእርሱ ወደ ሆኑት መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም፤” (ዮሐ.1፥11)፡፡ መላእክቱ እንኳ፥ “ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና፤” (ሉቃ.2፥11) ብለው ቢናገሩም የሚሰማቸው አላገኙም፡፡ “ታላላቆቹ” መሲሑን ናቁት፣ ድኾችና ያልተጠበቁት ግን ኢየሱስን በማክበራቸው ከበሩ፤ መድኃኒትም ሆናቸው፡፡
     ሌላው ደግሞ፥ ቦታውና ተቀባዮቹ ብቻ ሳይሆኑ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ ተራ በሆነ መንገድ ተወለደ፡፡ የከብቶች በረት ለንጉሥ “ያልተገባ” ሥፍራ ነው፤ ንጉሠ ሰማይ ወምድር ክርስቶስ ግን በዚህ ቦታ በሚያስደንቅ መልኩ ተወለደ፡፡ ሰው የክብር ሥፍራውን በኃጢአት ውርደት አጣ፤ ክርስቶስ ግን የተዋረደውን የሰውን ልጅ ሊያከብር እርሱ አለልክ ዝቅ ዝቅ አለ፡፡
ኢየሱስ ተወልዶልናል፤ ለምን ተወለደልን? ብንል፥
1.    ከእኛ ጋር ሊሆን፦ “አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ” ጌታ አምላክ ክርስቶስ፥ ከአባቱ ሳይለይ ወደሰው ልጅ የታሪክ ሐረግ ሊቆጠር ወደሰው ታሪክ ገባ፤ ወይም ከሰው የዘር ሐረግ ጋር በትውልድነት ተቆጠረ፡፡ ስለዚህም በፍጹም ሰውነቱ የእኛን በመንሳቱ እንደእኛ ሰው ሆኖ “አማኑኤል” ተባለ፡፡
     እንኳን ልጆች ባርያዎች ልንባል የማይገባን ክርስቶስ በፍጹም ሰውነቱ ከእኛ ተወልዶ ከእኛ ጋር በመሆኑ ምክንያት ልጆችና ወራሾች ሆንን፡፡ ክርስቶስ ኢየሱስ የሰው ልጅ በመሆኑ ምክንያት እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ለመባል በቃን፡፡ እጅግ ታላቅ ምስጢር!
2.   መድኃኒት ሊሆነን፦ የተወለደው ሕጻን አምላክ ነው፡፡ መድኃኒትነት የአምላክነት ባሕርይ ነው፡፡ ከአምላክ በቀር ለሰው መድኃኒት መሆን የሚቻለው ማንም የለም፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ራሱ፥ “እኔ ፈዋሽህ እግዚአብሔር ነኝና አለ፤”(ዘጸ.15፥25) እንዲሁም በነቢዩ አንደበት፥ “እኔ፥ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፥ ከእኔ ሌላም የሚያድን የለም፤”(ኢሳ.43፥11) በማለት ከያህዌ በቀር አዳኝ እንደሌለ ተናገረ፡፡ መዝሙረኛውም ይህንን በማመን፥ “አንተ አምላኬ ነህ አመሰግንህማለሁ። አንተ አምላኬ ነህ፥ ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ፤ ሰምተኸኛልና፥ መድኃኒትም ሆነኸኛልና አመሰግንሃለሁ፤” (መዝ.118፥28) በማለት ተቀኘ፡፡  
     ጌታ ኢየሱስ አዳኝ መሆኑን፥ “የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአልና” በማለት ተናገረ፤ (ሉቃ.19፥10)፡፡ ኢየሱስ የመባሉንም ምክንያት መልአኩ፥ “እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ” በማለት መሰከረ፤ (ማቴ.1፥21)፡፡ በእርግጥም፥ “ሰዎችን ሁሉ የሚያድን የእግዚአብሔር ጸጋ ተገልጦአል፤” (ቲቶ.2፥11)፡፡ ደግሞም፥ “ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው፤”(1ጢሞ.1፥15)፡፡ እኛም ከመንፈስ ቅዱስ የተነሣ የዚህ እውነት ምስክሮች ነን፤ “እኛም አይተናል አባትም ልጁን የዓለም መድኃኒት ሊሆን እንደ ላከው እንመሰክራለን፤”(1ዮሐ.4፥14)፡፡
    ለመሆኑ ግን፥ ክርስቶስን መድኃኒታችን ነው ስንል፥ ከምንድር ነው የሚያድነን?
2.1.  ከኃጢአት፦ “ኃጢአትን በተመለከተ በሰማይም በምድርም ከክርስቶስ በቀር ምንምና አንዳች መፍትሔ የለም፡፡ ያለ ክርስቶስ የኃጢአትን ሥርየት ማግኘት ፈጽሞ አይቻልም፡፡ ኃጢአት የሰማይን ደጅ ሲዘጋና ሰው የፈጣሪውን ፊት ማግኘት ፍጹም ሲሳነው፥ ክርስቶስ ወደሰማይ መግቢያችን በር ሆኖ መጣልን፡፡
      በሰማይና በምድር “ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፤ አስተዋይም የለም፤ እግዚአብሔርንም የሚፈልግ የለም፤ ሁሉ ተሳስተዋል፥”(ሮሜ.3፥11) ተብሎ በተነገረበት ዋዜማ፥ ክርስቶስ አዳኝና የኃጢአታችን ማስተሥረያ ሆኖ መጣልን፡፡ “ልጆቼ ሆይ፥ ኃጢአትን እንዳታደርጉ ይህን እጽፍላችኋለሁ። ማንም ኃጢአትን ቢያደርግ ከአብ ዘንድ ጠበቃ አለን እርሱም ጻድቅ የሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እርሱም የኃጢአታችን ማስተስሪያ ነው፥ ለኃጢአታችንም ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ለዓለሙ ሁሉ ኃጢአት እንጂ፤” (1ዮሐ.2፥1-2) ተባለልን፡፡ እግዚአብሔር በእርግጥም “እርሱንም እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው፤ ይህም በፊት የተደረገውን ኃጢአት በእግዚአብሔር ችሎታ ስለ መተው ጽድቁን ያሳይ ዘንድ ነው፥”(ሮሜ.3፥25)፡፡
    ስለዚህ ከእርሱ የኃጢአት ማስተሥረያነት በቀር ሌላ ስለኃጢአት መላና መፍትሔ የለንም፡፡ መወለዱ ስለኃጢአታችን መድኃኒትነት ነው፡፡ ልደቱን ማክበር ማለት ዳቦ መቁረስና ጮማ መቁረጥ አይደለም፤ የኃጢአት ሥርየትን ያገኘንበት ታላቅ መንፈሳዊ ምስጢር በማሰብ አምልኮአችንን በፍርሃት የምንፈጽምበት ቀን እንጂ፡፡ አዎን! “ከአዳም ጀምሮ እስከዛሬ ከተፈጠረው ፍጥረት ሁሉ ማንም ማን ሊያድነን አልቻለም፡፡ ከእግዚአብሔር ቃል (አካላዊ ቃል፤ ከአዳኝ ኢየሱስ በቀር) በሰው ቢሆን አለኝታችን ከንቱ እንዳይሆን የባሕርይ አምላክ እርሱ ሰው ኾነ እንጂ፡፡”[1]
2.2. ከዚህ ክፉና ጠማማ ዓለም[ትውልድ]፦ ሕጻኑ ኢየሱስ እኛን “ክፉ ከሆነ ከአሁኑ ዓለም ያድነን ዘንድ እንደ አምላካችንና እንደ አባታችን ፈቃድ ስለ ኃጢአታችን ራሱን ሊሰጥ” የመጣና ደግሞም የሰጠ ነው፤ (ገላ.1፥4)፡፡ ይህንንም ከልደቱ ጀምሮ በተቆጠረለት “በገዛ ዘመኑ ምስክርነቱ ነበረ” (1ጢሞ.2፥6)፡፡ በዚህ በገዛ ዘመኑም ከዚህ ክፉ ዓለምና ከክፉ ትውልድ እንድንርቅና እንድንጠበቅ ደጋግሞ አስተማረን፤ (ማቴ.16፥6 ፤ ሉቃ.12፥15 ፤ 20፥46) ከክፉ ማንነታችን፣ ከሱሳችን፣ ከተያዝበት ከኃጢአት ልማድ፣ መለየት አልችልም ከምንለው ክፋትና የሰይጣን የሽንገላ አሠራር ነጻ የሚያወጣና የሚያድን ሕጻኑ ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡
2.3.  ከዘላለም ሞት ፥ ከኩነኔ ፍርድ በኃጢአት ምክንያት ያገኘን ትልቁ ፍርድ በሞት መኮነን ነው፡፡ በዚህም በእግዚአብሔር ፊት የመቅረብን ጸጋና ሞገስን አጣን፡፡ ክርስቶስ ግን በመወለዱ ሁላችን በእግዚአብሔር ፊት የምንቆምበት ጸጋና ሞገስ ሆነን፡፡ ደግሞም በመድኃኒትነቱ ከዘላለም ሞትና ከኩነኔ ፍርድ አዳነን፤ ስለዚህም፥ “እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኵነኔ የለባቸውም” (ሮሜ.8፥1) ተባለልን፡፡
    በክርስቶስ ልደት በእርሱ መድኃኒትነት መዳናችን ተበስሯል፤ በመወለዱ ከማይጠፋው ዘር ለተወለዳችሁ እውነተኛ ክርስቲያን አማኞች ሆይ! በክርስቶስ ፍቅርና ደስታ እንኳን ደስ አላችሁ! መወለዱን በመብልና በመጠጥ፤ በቧልት፣ በሳቅና በጨዋታ ያይደለ በእውነትና በፍቅር፤ ቃሉን በማንበብና በማጥናት የምታሳልፉበት ሳምንት እንዲሆንላችሁ በክርስቶስ ፍቅር ማለድኳችሁ! ሕጻኑ መድኃኒት ይሆነን ዘንድ ተወለደልን፤ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ደስ ይበላችሁ፤ አሜን፡፡




[1] ይማኖተ አበው ዘኤጲ.ምዕ.58 ክ.13 ቁጥር 46-49

No comments:

Post a Comment