Friday 16 December 2016

የወዳጅ ሕመም

ደድሯል አካሌ፣ አመርቅዞ ውስጤ ፤
ነፍሴ ተኮራምታ፣ ተራቁታብኝ አቅሌ፤
ያጎረስሁት ያው እጅ፣ ይሸረክተኛል፤

በጋለ ስል ብረት፣ ይቀረድደኛል ፤
አንድ እጄ ሲያለብስ፣ ሌላው ያራቁታል፤
ሙቀት የሰጠሁት፣ ቆፈን ያዝልኛል፤
የማይወጣ ደዌ፣ ዘውትር ጥዝጣዜ፤
የወዳጅ ሕመም ነው፣ የታመምኩት እኔ፡፡

ጌታ በሚወደው፣ ይሁዳ ወዳጁ
“ተደፍሯል ተረግጧል፣” ሞገሳዊው ደጁ፤
ውድ ሰው ያ ኬፋም፣ ባ'ንዲት ጀንበር ዕድሜ፤
ወዳጅነት ሲክድ፣ ይታየኛል ባ'ይኔ፡፡

የወዳጅን ሕመም፣ ታመህ ያሳየኸኝ፤
ሕመሜን ታመኸው፣ ከመውደቄ ያቆምከኝ፤
አላጉረመርምም፣ ደማሁ ቆሰልኩ ብዬ፤

ለእውነት ደድሬያለሁ፣ ያ'ንተን አጋርነት በእምነት ተቀብዬ፡፡

No comments:

Post a Comment