Thursday 28 January 2016

“በኦርጋን ልንዘምር ይገባል ፤ አይገባም” ከሚለው ክርክር ጀርባ ...


       የቤተክርስቲያንን ታሪክ እንደምናጠናው ቤተክርስቲያን እጅግ ዘግናኝና አሰቃቂ የአላውያን ነገሥታትን ስደትና መከራ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ድል አድራጊነት የተወጣችውን ያህል፥ የተድላውን ዘመን ማለፍ ሲሳናት አስተውለናል፡፡ ለምሳሌ ያህል፦ የመካከለኛው ዘመን በሚባለው ከ590-1517 ዓ.ም [1] ከብዙው መካከል በዋናነት ሁለት አስነዋሪና ዘግናኝ ስህተቶችንእ ናስተውላለን፡፡


1.     ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስን ወንጌል መናኘት ፤ መስቀሉን መሸከም ፍጹም ትታ ከ1095-1270 ዓ.ም ድረስ ሰይፍን በማንሳት ፤ “የመስቀል ጦረኞችን” በማዝመት “የመስቀል ጦርነትን” በማካሄድ በሚሊየን የሚቆጠሩ ሰዎችን አቆሰለች፤ ገደለችም፡፡
2.    ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ከመሰብሰብ ፣ ተግቶ ከማስተማር ፣ እንደእረኛ ከማሠማራት ይልቅ፥ ምንም ፋይዳ በሌላቸው “በአንድ መርፌ ላይ ስንት መላዕክት ይቆማሉ? በአንድ መርፌ ስንት መላዕክት ይሾልካሉ?” በሚለውና በሌሎችም ጉንጭ አልፋ ክርክሮች እርስ በራሷ ተጠማምዳ በመካሰስ ላይ ስለነበረች የእስልምና ሃይማኖት ያለአንዳች ድካም ብዙ ነፍሳትን “መውረስ ችሏል፡፡”
    ቤተ ክርስቲያን ዝናርዋን በታጠቀችባቸው ወራት የትኛውም የተደራጀ ሃይልና ፤ የታጠቀ የሥጋ ሠራዊት እንዲሁም (ኤፌ.6፥21) የገሃነም ደጆች አይችሏትም፡፡ (ማቴ.16፥18) ትጥቋን በገዛ ፈቃዷ ፈታ “የአሮጊት ተረትና ጉንጭ አልፋ ክርክር” ውስጥ ገብታ ወደከንቱ መለፍለፍ ስታዘነብል ጸሎት ፣ የወንጌሉ ምስክርነት ፍጹም ይዘነጋል፡፡ ሳታስበውም የገሃነም ደጆች የማይችሏትንና “ሁሉን ትችልበት ዘንድ” የተሰጣት ሃይሏ ይወሰድባታል፡፡
    ጠላት ትልቁን ሥራውን ሊሠራ ሲወድ የሚያደርገው ነገር ቢኖር ማዘናጋት ነው፡፡ የመካከለኛዋን ዘመን ቤተ ክርስቲያን ለማዘናጋት “የራሷ አገልጋዮች” የተጠቀሙበት መንገድ መንፈሳዊ መሳይ የማይጠቅም የስንፍና ትምህርት ነው፡፡ ከትላንት ታሪክ ስላልተማርን ዛሬም እየሆነ ያለው ይኸው ነው፡፡
    “በኦርጋን ይዘመር ወይስ አይዘመር” የሚለውን ክርክር ከልብ ከሆነ በመንፈስ ቅዱስ” የሚመራው ቅዱስ  ሲኖዶስ በአንድ ጉባኤ የማያዳግም መጽሐፍ ቅዱሳዊና ቀኖናዊ መልስን መስጠት አይቸግረውም፡፡ ነገር ግን እያየን ያለነው ነገር ጳጳሳት ፣ ቆሞሳት ፣ ሰባክያን ፣ ዘማርያንና ሌሎችም አገልጋዮች ለኃጥአንና ለአህዛብ ሊሰበክ የሚገባውን አስደናቂውን የጸጋ ወንጌል ችላ ብለው ሙግት ውስጥ ገብተዋል፡፡
    በእውኑ ይህን ለመከራከር ጊዜው ነውን? የጊዜውስ ቃል ነውን? እውነት አሁን የቸገራችሁና ያንገበገባችሁ ፤ ውስጣችሁንም ያቃጠላችሁ የኦርጋን ጉዳይ ነው? ለተራበ ፣ ፍትሕ ላጣ ፣ በገዛ ወገኑ ጥይት ለሚቆላ ፣ በደም ለጨቀየ ምድር እውነት የኦርጋን ንትርክና ጭቅጭቅ ምንድር ነው ?በውኆች ድምጽና በነፋሳት ፉጨት ፤ በድንጋዮች እልልታና በፌንጣ ሲርሲርታ ፣ በንቦች እምምታ ፣ በጥጆች ቡርቅት ፣ በላሞች ማንቧለል  ... የሚመሰገነው ጌታ ኦርጋን ለእርሱ ምኑ ነው? ኦርጋን ሳይኖርም፥ ክብር ይግባውና ጌታ ምስጉን ነው፡፡ በእውኑ ከቅድስት ቤተክርስቲያን አባልነት በአስርት አመታት ዕድሜ በሚሊየን ቁጥር ከአብራኳ የተለዩት ልጆቿ እኛን አይገዳችሁምን? የተራበው አስራ አምስት ሚሊየን ሕዝብ አንዳች አይሰማችሁምን?
    የትኛው ሰማዕት ይሆን በዚህ ጉዳይ መከራን የተቀበለ? እኛ በዚህ ክርክር ሰጥመን እንደዶሮ ስንመነታተፍ መናፍቃን ምን እየሠሩ ነው? ጠላት ዲያብሎስ ትልቁን ሥራ አስጥሎ በትንሹ ሲያበላላን ፣ ሲለያየን ፣ ሲከፋፍለን መች ይሆን እንደቀን ልጆች ለእግዚአብሔር ሥራ ጠቢባን የምንሆነው? በትውልድ ፊት ስህተትን በመሥራት የማሰናከያን ዐለት አናስቀምጥ፡፡ ከክርክሩ ጀርባ ያለው የጠላት ሃሳብ ገብቶን ይሆን?
   ወንጌል መስበክ ፤ ወንጌል መስበክ ፤ ወንጌል መስበክ የምንሰብከውን በሕይወት መኖርን ከቅዱስ ቃሉ ተምረን በዘረኝነት የታሰረውን ቤተ መንግሥትና ቤተ ክህነት ፣ በረሃብ እየተፈጀ ያለውን ተማሪና የአገር ተወላጅ ፣ በጥይትና በቆመጥ የገዛ ወገኑን ሳይመርጥ ለሞት የሚማግደውንም ወደገዛ ልቡ እንዲመለስና ምድሪቱ ዕረፍት እንድታገኝ ቤተክርስቲያን ያለባትን የዘመን የቤት ሥራዋን ብትወጣ እጅግ መልካምነው፡፡ አልያ “እንደእሳት ነበልባል የሆኑ ዓይኖች ያሉት በእቶንም የነጠረ የጋለ ናስ የሚመስሉ እግሮች ያሉት የእግዚአብሔር ልጅ” (ራእ.2፥18) ያያል፡፡

 አቤቱ ጌታ ሆይ! ለሕዝብህ ማስተዋልን አብዛ፡፡ አሜን፡፡

[1]እንደምሁራኑ የዘመናቱ ክፍፍል ይለያያል፡፡ 










[1] እንደምሁራኑ የዘመናቱ ክፍፍል ይለያያል፡፡ 

3 comments:

  1. ሃይልህ ሲገለጥ ከሰማይ አቤት ማን ይቆም ይሆን ከፊትህ ማን ይቆም
    ይሆን??

    ReplyDelete
  2. በቤተክርስቲያን እንዳንተ ያሉ አሳሳች እና አስመሳዮች በርክተው ምን ስራ ይሰራል፡፡ ለመሆኑ ስለዜማ መሳሪያ ቅዱስ ሲኖዶስ እንዳልወሰነ በማስመሰል ‹‹ሲከራከሩ›› ማለትን ምን አመጣው፡፡ ቀሳጢ ተሀድሶ(ሐራ ጥቃ) መሆንህን አናውቅ መሰለህ!!!

    ReplyDelete