Tuesday 17 January 2023

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፳፫)

 

“በመድሎተ ጽድቅ” መጽሐፍ ውስጥ፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ሥልጣን በተመለከተ ጐልተው የሚታዩትን ስህተቶች በባለፈው ክፍል ከጠቀስናቸው ስህተቶች ባሻገር የሚከተሉትም ይካተቱበታል።

1.2.    የተባለውን በትርጉም በመቃወም፦

የመድሎተ ጽድቅ ጸሐፊ፣ መዳን በክርስቶስ ብቻ እንዳልኾነና በመዳን ውስጥ እኛም ድርሻ እንዳለን ለማሳየት ከተጠቀመበት ጥቅስ አንዱ እንዲህ የሚል ነው፤

“ኦርቶዶ ክሳውያን አባቶቻችን የጸጋው ሥጦታ ነጻ(እንዲሁ) የሚሰጥ መኾኑን በአንድ በኩል ፣ የሰውን ነጻ ፈቃድ (ነጻነት) ደግሞ በሌላ በኩል አስተባብረው በመያዝ ለሰው መዳን የኹለቱ መስተጋብር አስፈላጊ መኾኑን በአጽንዖት ያስተምራሉ። ይህም በቅዱስ ጳውሎስ  ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነንና።” ተብሎ የተገለጸው ነው(1ቆሮ. 3፥9)”

እንግዲህ በራሱ መዳን ያልቻለው ሰው፣ ከጌታ ጋር ተባብሮ ዳነ ብሎ ማለት እንዴት ያለ ጸያፍ ነገር ይኾን? መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ፣ “እንኪያስ እግዚአብሔር ለአሕዛብ ደግሞ ለሕይወት የሚሆን ንስሐን ሰጣቸው” (ሐ.ሥ. 11፥18) እንዲል፣ በሩቅ ላሉት አሕዛብ የሕይወት ንስሐ የሚሰጥ ራሱ እግዚአብሔር ነው፤ ይህ ብቻ አይደለም፣ “በአምላካችንና በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጽድቅ ካገኘነው ጋር የተካከለ የክብር እምነትን ላገኙ፤” (2ጴጥ. 1፥1) እንዲል እምነትንም እንኳ የሚሰጥ ራሱ እግዚአብሔር እንጂ ሰው መልካሙን እንኳ ለመምረጥ የማይቻለው እንደ ኾነ ቅዱስ መጽሐፍ በግልጥ ያስተምራል፤ (ሮሜ 3፥23)።

የመድሎተ ጽድቅ ጸሐፊ በክርስቶስ የሚገኘውን መዳን አብዝቶ በመግፋት የሚስተካከለው ያለ አይመስልም፤ ሰዎች እግዚአብሔርን አብረውት ሠርተው እንደሚድኑ የጠቀሰው ጥቅስ (1ቆሮ. 3፥9) በርግጥ ስለ መዳንና የምንድነውም ከእግዚአብሔር ጋር ተረዳድተን እንደ ኾነ የሚናገር ነው? ፈጽሞ አይደለም።

ቅዱስ ጳውሎስ እየተናገረ ያለው፣ በመለያየት መንፈስ ውስጥ ስለ ተከፋፈሉት የቆሮንቶስ አማኞች የተናገረው ቃል ነው። ክፍሉ የሚናገረው “እኔ የጳውሎስ ነኝ፥ ሁለተኛውም፦ እኔ የአጵሎስ ነኝ” መባባል እንደሌለባቸውና ይህም ክፉ ምሳሌ እንደ ኾነ በመጥቀስ፣ አማኞች የትኛውንም ሰብዓዊ መሪ መርጠው መከተላቸው ትክክል እንዳልኾነ በተግሳጽ የተናገረበት ክፍል ነው። ሰዎች ላይ ከማተኮር ይልቅ የችግሮቻችን መፍትሔ የኾነውን የመስቀሉን ክርስቶስ እንደምንዘነጋ የተናገረበት ክፍል ነው።

ይልቁን “የእግዚአብሔር እርሻ ናችሁ፤ የእግዚአብሔር ሕንፃ ናችሁ፤ ከእርሱ ጋር አብረን የምንሠራ ነንና።” እንዲል፣ ጳውሎስና አጵሎስ የሚሠሩበት ዕርሻም ኾነ ሕንጻ ባለቤቱ እግዚአብሔር ነው፤ የሚሠሩትም በእግዚአብሔር ዕርሻ ውስጥ ነው፤ የቆሮንቶስ አማኞች ደግሞ የእግዚአብሔር ዕርሻና ሕንጻ ናቸው፤ ኹሉም ከእግዚአብሔር ጋር በዚያው ውድ እርሻ ውስጥ የሚያገለግሉ ናቸው ለማለት እንጂ እግዚአብሔር ከሰው ጋር በመራዳት ሰውን ያድናል ማለት እጅግ ጸያፍ ንግግር ነው!

ይልቅ ስለ ተሰቀለው ክርስቶስ ቅዱሳት እንዲህ ይመሰክራሉ፤

“መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።” (ዮሐ. 10፥11) ከኢየሱስ በቀር ነፍሱን ለበጎች የሚያኖር ሌላ የለም!

“ስለ ጻድቅ የሚሞት በጭንቅ ይገኛልና፤ ስለ ቸር ሰው ግን ሊሞት እንኳ የሚደፍር ምናልባት ይገኝ ይሆናል። ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል። … ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን፥ ይልቁንም ከታረቅን በኋላ በሕይወቱ እንድናለን፤” (ሮሜ 5፥8-10)

በእንዲሁ ፍቅር የወደደንና የሞተልን፤ ከእኛ ምንም ሳይኾን በራሱ ብቻውን ሞቶ ያዳነን ክርስቶስ ይባረክ፤ አሜን።

ይቀጥላል …

 

No comments:

Post a Comment