Monday 20 May 2019

በሕማሙና በትንሣኤው ዙርያ የነበሩ ምስክሮች (ክፍል ሦስት)

 Please read in PDF

3. ማርያም መግደላዊት፦ የክርስቶስ ከሙታን ትንሣኤ መካከል በእውነት መነሣት የክርስትና ዋና ማዕከል ነው፤ በመስቀል ላይ ቤዛ ኾኖ መሰቀሉ በእውነት ለኃጢአተኞች መኾኑና የቤዛነት ክፍያውም መረጋገጡን የሚያበስረው ከሙታን መካከል መነሣቱ ነው፤ “እንግዲህ ክርስቶስ በአብ ክብር ከሙታን እንደ ተነሣ እንዲሁ እኛም በአዲስ ሕይወት እንድንመላለስ” ክርስቶስ ከሙታን መካከል ተነሥቶአል፤ (ሮሜ 6፥4፤ 7፥6፤ ሐዋ. 2፥24፤ 2ቆሮ. 5፥17፤ ኤፌ. 4፥22፤ ቈላ. 3፥10)። ጌታ ኢየሱስ ከሙታን መካከል ባይነሣልን፣ “ክርስቶስም ካልተነሣ እምነታችሁ ከንቱ ናት፤ እስከ አሁን ድረስ በኃጢአታችሁ አላችሁ” (1ቆሮ. 15፥17) እንደ ተባለ፣ ከኃጢአታችን ሳንላቀቅ እስከ አኹን እንደ ተጣባን፣ የሙጥኝ ብለን እየኖርን አለን ማለት ነው። ክብር ይኹንለትና እርሱ ግን የኀጢአት ዋጋችንን በሥጋው መከራ በመስቀል ላይ ደሙን አፍስሶ ከፍሎልን፣ ዋጋችንም የጸደቀና የተረጋገጠ መኾኑን በትንሣኤው አጽንቶልናል።




   ጌታ ኢየሱስ ከሙታን መነሣቱ ከእርሱ እንድንቀበር ያደረገን ብቻ አይደለም፤ ተቀብረን ከነበርንበት ደግሞ ከእርሱ ጋር በሕይወት እንኖር ዘንድም አብረነው ከእርሱ ጋር ተነሥተናል። ኃጢአትን በሚጠየፍና በተጠየፈ ማንነት አብረን ከእርሱ ጋር እንኖር ዘንድ፣ ክርስቶስ ፈጽሞ ሊነጥፍ የማይችል የሕይወትን ሙሉ በረከት በእኛ ውስጥ አፍስሶአል። ይህ ያፈሰሰው የሕይወት ሙላት በኃጢአት እንመላለስ እንደ ነበረው ዐይነት ሕይወት ሳይኾን፣ ፍጹም አዲስ ሕይወትን እንድንኖር የሚያደርገን ነው።
   ክርስቶስ ኢየሱስን በትክክልና በእውነት ካመንነውና ከተከተልነው አኗኗራችን ፈጽሞ እንደ ቀድሞው አይደለም፤ አይኾንምም!
   ኢየሱስ ክርስቶስን በትንሣኤው ኃይል ያዩት ቅዱሳን ኹሉ ይኖሩበት የነበረውን ያንን ፍሬ አልባ የሚታፈርበት ሕይወት (ሮሜ 6፥21) ሙሉ ለሙሉ እርግፍ አድርገው፣ በተለወጠ፣ ለውጡም በሌሎች ዘንድ በሚታይና ታይቶም በሌሎች በሚመሰከርና በማይታበል በአዲስ ማንነት ሊከተሉት ኹሉን ትተው ወጥተዋል። ያመንነው ወንጌል ከዓለማውያን ካልለየንና ከክፋት ኹሉ ነጻ አውጥቶ በልዩነት ካላቆመን እንደ ገና መንገዳችንን በንስሐ አስተካክለን መጀመርና መቀደስ አለብን።
  ከእነዚህ ድንቅ የትንሣኤው ምስክሮች መካከል ከቀዳሚዎቹ ተርታ በወንጌላት የተመደበችው ሴት፣ ማርያም መግደላዊት ናት፤ መግደላዊት ማርያም በአራቱም ወንጌላት የተጠቀሰች ተወዳጅ የትንሣኤው ምስክር ናት፤ (ማቴ. 28፥1፤ ማር. 16፥1፣ 9፤ ሉቃ. 24፥10፤ ዮሐ. 20፥1፣ 18) በማርቆስ ወንጌላዊ አነጋገር ደግሞ፣ “ሰባት አጋንንት የወጣላት ማርያም” ተብላለች፤ (ማር. 16፥9)። ጌታ ኢየሱስ ሲቀበር በሩቅ ኾና፣ “በሐዘን ኩርምት” ብላ ያኖሩበትን ስትመለከት በመቃብሩ አንጻር የነበረች ተወዳጅ ሴት ናት፤ (ማቴ. 27፥61፤ ማር. 15፥40-41)።
   እንዲህ በመሪር ሃዘን ውስጥ ለነበረች ሴት፣ የኢየሱስ ከሙታን መካከል መነሣት ምን ዐይነት ደስታ ሊፈጥርባት እንደሚችል አስቡት!!! የሞተው፣ ሲቀበር ያየችው፣ የተቀበረው፣ ሞትን ድል ነሥቶ፣ መቃብርን አሸንፎ፣ መፍረስና መበስበስን ሽሮ ሲነሣ እንዴት አትረካ?! እንዴት በደስታ አትሰክር?! እንዴት እንደ እንቦሳ አትዘልል?! እንዴትስ አትፈነጭስ?! እርሷ ካልመሰከረች ማን ሊመሰክር ይችላል?! በእውነት ኢየሱስን የቀመሱት ኹሉ ዝም ይሉ ዘንድ ፈጽመው አልቻሉም፤ ማርያም ዝም ያላለችበት ምክንያቱ፦
1.      ከሰባት አጋንንት ገላግሎአታልና፦ አጋንንት እጅግ ክፉዎች ናቸው፤ የሰው ልጅ ዋነኛ ጠላቶችና ጨካኞችም ናቸው፤ (ማቴ. 12፥43-45)። አጋንንት በእግዚአብሔር ላይ ያላቸውን ጥላቻቸውን የሚገልጡትና ማሳየት የሚፈልጉት በእግዚአብሔር አምሳል በተፈጠረው በሚያሳዩት እጅግ አስነዋሪ ተግባር ነው፤ ሰይጣንና አጋንንቱ ኹል ጊዜ ሰዎችን በማሳትና በመጣል ለመርካት ይሻሉ፤ ከእግዚአብሔር ውጭ መኾን የሚፈልገውን ዓለም በመግዛትና በመጨቆን፣ በማስጨነቅና በማዋረድ ይታወቃሉም፤ (ዮሐ. 12፥31፤ 2ቆሮ. 2፥2፤ ኤፌ. 6፥10)። በጨረቃ የሚጥሉና ክፉኛ የሚያሳቅዩ (ማቴ. 4፥24፤ 17፥14)፣ ሰውን ከሰው ጋር የማያስማሙ (ማር. 5፥1-3)፣ ሰውን በቀንና በሌሊት በመቃብርና በተራራ የሚያስጮኹ፣ የሥጋን ሰውነት በድንጋይ የሚያቧጭሩና የሚያስተለትሉ (ማር. 5፥4)፣ ዕውርና ዲዳ የሚያደርጉ (ማቴ. 12፥22) ... ለሰዎች ፈጽመው የማይራሩ እጅግ ክፉዎች ናቸው።
    አጋንንት ሰዎችን ከእግዚአብሔር ፈቃድ በመነጠል ፈጽሞ ባሮች አድርገው የሚገዙ ናቸው። ጌታ ኢየሱስ ሰዎችን ነጻ ለማውጣት ኃይለኛውን ማሰር እንደሚገባ “ ... ሰው አስቀድሞ ኃይለኛውን ሳያስር ወደ ኃይለኛው ቤት ገብቶ እቃውን ሊነጥቀው እንዴት ይላል? ከዚያም ወዲያ ቤቱን ይበዘብዛል።” (ማቴ. 12፥29) በማለት ተናገረ። ስለዚህም ጌታ ኢየሱስ ያልነበሩ እስኪመስሉ ድረስ አጋንንት አሳደዳቸው፤ ከሰዎች ላይ ሥልጣናቸውን ሻረው፤ ከሰዎችም ኹሉ አራቃቸው፤ ሰዎችንም አሳረፋቸው፤ (ማቴ. 4፥23፤ 9፥20፤ ማር. 1፥23፤ 3፥10፤ 6፥7፤ 7፥24፤ 16፥17)።
   ማርያም መግደላዊት ነጻ የወጣችው ከዚህ ክፉ “ጌታ” ነው። ከአንድ ሳይኾን ያውም ከሰባት ክፉ አጋንንት!!! ኢየሱስ የመግደላዊትን አስጨናቂዋን አስጨንቆታል፣ ያዋረዳትን አዋርዶታል፣ ያሰቃያትን አሰቃይቶ ሕይወቷን በሙሉ እረፍትና ሠላም ሞልቶታል።
   ሰዎች ያለ ኢየሱስ ስምና ሥልጣን ከአጋንንት እስራት ፈጽመው ነጻ መውጣት አይችሉም። አጋንንትን ድል መንሣት የሚችለው ኢየሱስና ድል ነሺው ስሙ ብቻ ነው። ወንጌላት ይህን በማርያም መግደላዊት ሕይወት ላይ የኾነውን እውነታ አጉልተው መስክረዋል። ከማርያም አጋንንትን ያወጣው ኢየሱስ እንደ ኾነ፣ እንዲሁም ከመላው የሰው ዘር አጋንንትን ማውጣትና ማሳደድ የተወዳጁ ኢየሱስ ሥራና ሥልጣን ብቻ ነው። ማንም ከኢየሱስ ስምና ሥልጣን ውጪ አጋንንትን “ቢያወጣ” እርሱ ሐሰተኛ ነው።
   የመግደሎሟ ሴት ማርያም ይህን እውነት በሚገባ አስተውላለች፤ እናም ከአስጨናቂው “ጌታ” ነጻ ላወጣት ተወዳጅ ጌታ ኢየሱስ ፍቅሯንና ያላትን ታማኝነት፣ ጽናት፣ መሰጠት ለማሳየት በሕማምና በመቃብሩም በትንሣኤው ከዋነኞቹ ምስክሮች ቀዳሚዋ ነበረች። ደግሜ እላለሁ፦ ኢየሱስን በትክክል የቀመሰ ዝም ይል ዘንድ ፈጽሞ አይችልም። በተለይ ከመከራና ከስቃይ የተገላገለ፣ ለፍቅር ጌታ በፍቅር የሚገዛ፤ ውድ ጆሮውን የተበሳ ባርያ ነው። ማርያም መግደላዊት ለኢየሱስ እንዲህ ናት! ከአስጨናቂው ከሰይጣን ባርነት ነጻ የወጣች ለኢየሱስ ግን በውድና በፍቅር በመሰጠት የተገዛች ውድ ባሪያው!!!
    ማርያም ለኢየሱስ የምሕረቱ መገለጫ ናት፤ እናም ወዳ ትገዛለታለች፤ በክርስቶስ ያመንን ኹላችንን የምሕረቱ መገለጫዎች ነንና የምንናገርለት የምንመሰክርለት ሕያው ምስክርነት አለን፤ በሕይወታችን ኹሉንም መልካም ነገር የሠራውና ሕይወታችንን የለወጠው ኢየሱስ ብቻ ነው፤ በየትኛውም መልካም ነገራችን ላይ ቀዳሚና ዋናው ኢየሱስ ብቻ ነው፤ ሊወደድ፣ ሊመለክ፣ ሊከበር፣ ሊወደስ፣ ሊቀደስ፣ ልንበረከክለት ... የሚገባውና ሊቀበልም ሥልጣን ኢየሱስ ብቻ ነው፤ እንዲህ የወደደን አማኑኤል ኢየሱስ ስሙ ይባረክ፤ አሜን።

ይቀጥላል ...

2 comments: