Tuesday 13 February 2018

ዘርፌ ከበደና የመዝሙር ምረቃዋ የተሰቀለውን ኢየሱስን አልገፋ ይኾን?

Pleas read in PDF

      ኢትዮጲያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጉባኤያት፣ በንግሥ በዓላት፣ በባዛር ዝግጅቶችና በሌሎችም ላይ ስእላትን፣ ለስእለት የመጡትን እንሰሳትና የተለያዩ ቁሳቁሶችን ማጫረትና ለሽያጭ ማቅረብ እንግዳ ድርጊት አይደለም። በተመሳሳይ ይዘት በወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናትም በአብዛኛው በመጻሕፍትና በካሴት ምረቃ ላይ ማጫረት “የደራ” ተግባር እንደኾነ አንድ ወዳጄ አጫውቶኛል፡፡ ድርጊቱ ከመንፈሳዊ መልኩ ይልቅ ከንግድ ጋር የተያያዘ ስለኾነ፣ በዓለማውያንም ዘንድ ሲዘወተር ይስተዋላል። ጥቂት ምሳሌዎችን ብንጠቅስ፦ በባለፈው ወር ሊዮናርዲ ዳቪንቺ የሳለውን “የጌታ ኢየሱስን” ስእል ለጨረታ መቅረቡን ከወደአውሮጳ ተሰምቶ ነበር፤ እናም፣ አንድ ማንነቱ ያልታወቀ ሰው ገዛው ቢባልም፣ በኋላ ሲጣራ “ከወደሳውዲ አረቢያ ባለሃብቶች” አንዱ መግዛቱን ሲወሳ ነበር። ባለፈው ሳምንት ደግሞ በአገራችን በኢትዮጲያ ከዘፋኞች አንዲቱ፣ “አዲስ” የዘፈን አልበሟን ስታስመርቅ የራሷን ስእል(ፎቶ) በማቅረብ በብዙ መቶ ሺህ ብሮች መሸጧን ሰማን። እጅግ “ወደእኛ” ሲቀርብ ደግሞ፣ ከትላንት በስቲያ እሁድ በብዙ መልካም ዝማሬዎቿ የምናውቃት ዘማሪት ዘርፌ ከበደም፣ አዲስ የሠራችው መዝሙሯን ስታስመርቅ አንዲት የሲዲ መዝሙሯን በማቅረብ አጫርታ፣ በሺህ ብሮች መሸጧን በሩቅ እንሰማ የነበረውን በቅርብ ደግሞ አየን።


   በመንፈሳዊ ስፍራዎች ላይ ይደረጉ በነበሩ ጨረታና ማናቸውም ንግድ መሠል የተንዛዙ፣ እጅግ የረዘሙ፣ አሰልቺ ተግባራትን ማየት ነፍሴ አብዝታ ትጠየፈዋለች። ነገሩን ከንግድና ከግል ገቢ አንጻር ብቻ አይቶ ቀለል አድርጐ ማለፍ ይቻላል። ነገር ግን የክፋት ምሳሌነቱ የጐላ ስለኾነ፣ ጉባኤው ላይ የነበረውን ጠቅላላ ነገርና ነገረ ጨረታን አያይዞ ማንሣት ወደድኹ። ምክንያቱም ወንጌልን ማዕከል ያላደረጉ ማናቸውም “መንፈሳውያን እንቅስቃሴዎች” በሌሎች አገልግሎቶች ላይ የሚያሣርፉት አሉታዊ ተጽዕኖ አደገኛና መራር ናቸውና።
   የቅዱስ ወንጌልን አገልግሎት ስናስብ ዘወትር ሊታወሰን የሚገባው፣ የአገልግሎቱ ባለቤት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ የፍቅር ትእዛዝ ነው፤ “… በከንቱ ተቀበላችሁ፥ በከንቱ ስጡ።” (ማቴ.10፥8) የሚለው። መዳናችንን በነጻ እንደተቀበልን፣ የመዳንንም ወንጌል ስንሰብክ፣ የይቅርታ ስጦታን፣ የመፈወስን ኃይል፣ የአገልግሎቱን አደራ ለሌሎች አሳልፈን ስንሰጥ፣ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተቀበልነው እንዲሁ ከጸጋው የተነሣ ያለዋጋ ሊኾን ይገባዋል። ቅዱሳን ሐዋርያትም ይቅርታን ማወጅ፣ በተሰጣቸው የመፈወስ ኃይል ያለዋጋ መፈወስና ሌላውንም አገልግሎቶች እንዲኹ ሠርተው ነበር።
   ከዚኹ ጋር በተያያዘ፣ ቅዱሳን ሐዋርያት በአገልግሎታቸው፣ ቃሉን በማስተማር፦ “ድውዮችን እንዲፈውሱ፤ ሙታንን እንዲያስነሡ፤ ለምጻሞችን እንዲያነጹ፤ አጋንንትን እንዲያወጡና ቅዱስ ቃሉን ሲሰብኩ፣ “ … ከማይቀበላችሁም ቃላችሁንም ከማይሰሙ ሁሉ፥ ከዚያ ቤት ወይም ከዚያች ከተማ ስትወጡ የእግራችሁን ትቢያ አራግፉ።” በማለት ነግሯቸዋል። ከኹሉ አስቀድሞ ቅዱስ ቃሉን[ወንጌልን] መስበክ፣ ማወጅ፣ መመስከር ይቀድማል። አጋንንትን ማውጣትና ማሳደድ ግልጥ ጦርነትን መክፈትና ማወጅንም ጭምር የሚያመለክት ነው፡፡    
    ቅዱስ ቃሉን ስናስተምር፣ ስናውጅ፣ ስንሰብክ … ደግሞ “በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና” ነው። መዝሙር ወይም ዝማሬ ወይም የውዳሴ መዝሙር ወይም መንፈሳዊ ዜማ አምልኮን ለማቅረብ፣ ተመላኪውን አምላክ ብቻ ልንወድስበት፣ ወንጌልን ለሌሎች ልንመሰክር ከምንችልባቸው መንገዶች አንዱ ነው፤ (ዘጸ.15፥20-21፤ ሐዋ.16፥25፤ ኤፌ.519፤ ላ. 316 ራእ.59፤ 153)። በመዝሙር ብዙዎችን የደረሱና ወንጌልን የመሰከሩ እንዳሉ እናምናለን። ቅዱስ ቃሉ ከሚናኝበት መንገዶችም አንዱ ነው ማለታችን፣ ከጸጋዎችም ተርታ መመደቡ (1ቆሮ.14፥26) ይኸንኑ የሚያመለክት ነው።
    በእርግጥ፣ አገልግሎት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ማግነን፤ ማላቅም ነው፤ ራስን ደግሞ እንደማይጠቅም ባርያ መቁጠር። ጌታችን እንዲህ አለ፦ “እናንተ ደግሞ የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ፦ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን፥ ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል በሉ።” (ሉቃ.17፥10) ይህንን በመንፈስ ቅዱስ የተረዳው መጥምቁ ዮሐንስ፣ “እኔ የጫማውን ጠፍር ልፈታ የማይገባኝ፥ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ ይልቅ የሚከብር ይህ ነው”፣ “እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ያስፈልጋል” (ዮሐ.1፥27፤ 3፥30) በማለት፣ አገልግሎቱን እንደሚገባ እያገለገለ ራሱን ግን ፈጽሞ ዝቅ ዝቅ፣ የማይጠቅምም እንደኾነ ያህል ቆጠረ። በሌላ ቋንቋ የአገልግሎቱን ዋጋ ቁጭ ብሎ ለመተመን በልቡ አላሰበም።
   ቅዱስ ጳውሎስ፣ “ነገር ግን ሩጫዬንና ከጌታ ከኢየሱስ የተቀበልሁትን አገልግሎት እርሱም የእግዚአብሔርን ጸጋ ወንጌልን መመስከር እፈጽም ዘንድ ነፍሴን በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ።” (ሐዋ.20፥24) ሲል፣ እንዴት ባለ ታላቅ መሰጠት ውስጥ ኾኖ ይኾን? ነፍሱን እንኳ እንደማትከብር ከንቱ ነገር እስከመቁጠር ያደረሰውስ እንዴት ያለ መንፈሳዊ ጭከና ነው?፣ ለክርስቶስ በኹለንተና ራስን ማስረከብ፣ ለቅጽበት እንኳ የራስን ክብርና ጥቅም አለማስቀደም እንዴት ያለ መታደል፣ እንደምን ያለ ማስተዋል ነው?!
   የተሰጠን የእግዚአብሔር ጸጋ፣ ወንጌልን መመስከር ነው። ምስክርነት ጥብቅና ታላቅ አደራ ነው፡፡ የእምነት አርበኞች ሰማዕታት እንዴት እንደመሰከሩ አስተውሉ! ፦ “ … እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጕድጓድ ተቅበዘበዙ።” (ዕብ.11፥35-38)፡፡ ሰማዕታት የተቀበሉትን መልእክትና አገልግሎት የሚጠይቀውን ከፍተኛውን ዋጋ፣ ነፍስን መስጠት እንኳ ሳይሳሱ አድርገውታል፡፡ ትኩር ብለው የተመለከቱት አገልግሎታቸውን ሳይኾን፣ የሚያገለግሉትን ጌታ ነበር።
    በቅምጥል ሥፍራ የነበሩት የእምነት አርበኞች እንኳ፣ “ከግብፅም ብዙ ገንዘብ ይልቅ ስለ ክርስቶስ መነቀፍ እጅግ የሚበልጥ ባለ ጠግነት እንዲሆን አስቦአልና ለጊዜው በኃጢአት ከሚገኝ ደስታ ይልቅ ከእግዚአብሔር ሕዝብ ጋር መከራ መቀበልን መረጠ፤ ብድራቱን ትኵር ብሎ ተመልክቶአልና፤” (ዕብ.11፥25-26)። በሰው ፊት የከበረውን ዘንግቶ በእግዚአብሔር ፊት የከበረውን ማስተዋልና ማየት እንዴት ያለ ታላቅ አብርሆት ነው?!
   እንግዲህ እህታችንን ዘርፌንና ከእርሷ ጋር የነበሩትን “አጋፋሪዎችን” የምንሞግትበት የእውነት መሠረት ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ ሁለት ነገሮችን በግልጥ ማንሣት እፈልጋለኹ፦
1.     ጨረታው ሂደት ፍጹም አለማዊና “የእግዚአብሔርን ጸጋ ለትመና” ያቀረበ፣ ኢ መንፈሳዊ ርካሽ ተግባር ነው። ሲዲን ማጫረት ለወንጌል ማስፋፊያ ተብሎ፣ ማጨናበሪያ ምላሽ እንደማይሰጥበት ተስፋ አደርጋለኹ። ነገር ግን ብርን የማከማቻ ሌላ እጅግ የተሻለ የንግድ ዘዴ መፈለግ[በአጭሩ ተግቶ መሥራት] እያለ፣ ለምን ይኾን መንፈሳዊ ካባን ማልበስ ያስፈለገው? ለመኾኑ ምንም ያልለፋንበትን ገንዘብ በአስባበ አገልግሎት፣ በአስባበ መዝሙር ማጫረት ... እንሰበስብ ዘንድ ማን ፈቀደልን?
  ለመኾኑ ዛሬ ኖሮ ቢኾን ቅዱስ ጳውሎስና ሲላስ የዘመሩት ዝማሬ በጨረታ ስንት ይሸጥ ይኾን? ሰማዕታት ከአንበሶችና ከእሳት ጋር ስለስሙ ምስክርነት፣ ፊት ለፊት ሲጋጠሙ የዘመሩት ዝማሬ ዛሬ ቢገመት ዋጋው ስንት ያወጣ ይኾን? …
   አገልጋይ መከሩን ሲያገለግል፣ የሚያስፈልገውን ማናቸውንም[መብል፣ መጠጥ፣ ልብስ፣ መጠለያ …] ከዚያው ከመከሩ ውስጥ እንደሚያገኝ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ “ … ለሠራተኛ ምግቡ ይገባዋልና። በምትገቡባትም በማናቸይቱም ከተማ ወይም መንደር፥ በዚያ የሚገባው ማን እንደ ሆነ በጥንቃቄ መርምሩ፤ እስክትወጡም ድረስ በዚያ ተቀመጡ።” (ማቴ.10፥10-11) በማለት ነግሮናል፡፡ በአገልግሎት ሽፋን ግን ሃብትን ለማካበት መመኘትና መፈለግ ግን ከምንጩ ይልቅ በወራጁ ለመርካት የሚደረግ የመንከራተት ጉዞ ነው።
2.    ግልጽ ኑፋቄ የሚታወቁና ብዙዎችን ያሰናከሉ “የእምነት እንቅስቃሴ አገልጋዮች”፣ የበደሏቸውንና ያሰናከሏቸውን አንዳቸውንም ይቅርታ ሳይጠይቁ፣ ትምህርቱንም መተዋቸውንና ኑፋቄ መኾኑን ሳያጋልጡ በ“ዓውደ ምሕረቱ” ላይ “ጉብ” ብለው ታይተዋል።
   መናገር የቻሉ ኹሉ አገልጋዮች መኾን ቢቻላቸው፣ በቤተ መንግሥት፣ በኪነ ጥበቡ ዓለምና በብዙ ቦታ ከእኛ የተሻሉ እልፍ አንደበተ ርቱአንና አፈ ቀላጤዎች አሉ። አገልግሎት መናገርና ሰውን አፍ ማስያዝ ፈጽሞ ቀዳሚ ሚዛኑ አይደለም።  የአገልግሎት መሠረቱ የክርስቶስ መስቀል፣ ማዕከሉ የክርስቶስ ቤዝወት፣ ጉልላቱም “ክርስቶስ ለኀጢአተኞች ሞቷል” የሚለውን መመስከርና ማወጅ፣ እንዲኹም ሕይወታችን ለክርስቶስ የተገዛና በእርሱም ቁጥጥር ሥር መኾኑን የሚያሣይ የጽድቅ ሕይወት ሲታይብን ጭምር የሚከናወን ነው። ትምህርትና ውሏቸውን ሳናጣራ ተናጋሪዎችንና ስል ምላሰኞችን መሰብሰብ ውድቀታችንን እንደሚያፈጥኑ በቅርብ ካሉቱ መማር ብልኅነት ነው።
    አንድ ነገር ደፍሬ መናገር እችላለኹ፤ የመዝሙር ምረቃው ጉባኤ ማንንም መወከል እንደማይችል፤ የመዝሙር ምረቃውን እንጂ የትኛውንም ቤተ እምነት ኾነ፣ ማናቸውንም ማኅበር ሊወክል እንደማይችል አምናለኹ፡፡ ምክንያቱም ብዙ ጊዜ በጉባኤው ላይ የተገኙት የእምነት እንቅስቃሴ አማኞችና አገልጋዮች ራሳቸውን በአንድ ቤተ እምነት ወይም በአንድ ማኅበር ውስጥ ማካተት አይፈልጉምና፡፡ ስለዚህም አብዛኛውን ሥራቸውን የሚሠሩት ለትውልድ በማያስብ ሕሊና ኃላፊነትን በመጣል ነው፡፡ እጅግ የሚያንገበግበው ነገር፣ እኒህ ሰዎች የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ሲቃወሙ ማናቸውንም [መንፈሳዊውንም፣ ዓለማዊውንም] መንገድ መጠቀማቸውና “ወንጌል እናምናለን” የሚሉ ወገኖች ደግሞ ኹልጊዜ የጥቃታቸው ሰለባ ሲኾኑ አለማስተዋላቸው ነው፡፡
3.    ገልግሎት “አማኞችን ከታንኳ ታንኳ ማገላበጥ” አይደለም፡፡ በመዝሙር ምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ከጥቂት ኦርቶዶክሳውያን በቀር፣ ዘጠኝ አሥረኛውን ያህል ቁጥር የተገኙት ከወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናትና ከእምነት እንቅስቃሴ በመጡ ሰዎች ነበር። እንግዲህ በሌላ ቤተ ክርስቲያን ታንኳ ላይ ያሉትን፣ በ“ተውሶ” አስመጥቶ፣ “ጉባኤ ማድረግ” የጤናማ አገልግሎት መገለጫ ነው ለማለት ከቶ አይታሰብም። ያልደከሙበትን መከር እንደራስ መከር ቆጥሮ “ቤተ ክርስቲያንን ለመክፈት” ማሰብም፣ [መቼም በዚህ ዘመን ጥሩ የምዝበራ መንገድ ነውና]  “ዘመነኞቹ ነቢያትና ሐዋርያት ነን ባዮች” ያደረጉትና የተበላ ዕቁብ ነው፡፡ መቼም ለዚህ፦ “እኔም እናንተ ያልደከማችሁበትን ታጭዱ ዘንድ ሰደድኋችሁ፤ ሌሎች ደከሙ እናንተም በድካማቸው ገባችሁ።” (ዮሐ.4፥38) የሚለውን ጥቅስ እንደማትጠቅሱ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡[ጠቅሶ የተከራከረኝን አንድ ሰው ማስታወሱንም ሳልዘነጋ]።
    [አገልግሎት መሲሑን ለማስደሰት ካልተጋና ማዕከል ካላደረገ ሰውን ኹሉ ለማስደሰት በሚደረግ ጥረት ያባክናል] … እንዲያውም አንድ ነገር እንዳስታውስ አደረገኝ፤ በ1990ዎቹ “ሐድሷውያን ነን” ብለው ተነሥተው፣ በኢግዝብሽን ማዕከል ጉባኤ አድርገናል ባሉ ማግሥት፣ ግራ እንደተጋቡትና ከኦርቶዶክስም፣ ከወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናትም፣ ከተሐድሷውያንም ሳይኾኑ ተንሳፍፈው እንደቀሩት መነኰሳት አንቺና ባልንጀሮችሽ ፎርሻችኹ እንዳትቀሩ እሰጋለሁ። ከተጠመደ ታንኳ ያለውን አማኝ ሰብስቦ “መናገር የፈለጉትን መናገር” እርሱ አገልግሎት አይደለም።
  እህቴ ዘርፌ ሆይ! የቁልቁለት መንገድ ቀላልና ድካም የሌለበት ቢኾንም፣ ቆም ብለሽ ብታሰላስይ እጅግ መልካም ነው። በዙርያሽ ከከበቡሽና ከእኩያዎችሽ ምክር ጥቂት ፈቀቅ በይና፣ ነገሮችን ግራና ቀኝ አጥርተሽ ለማየት ዕድልን ለራስሽ አብዢ፡፡ የመዝሙር አገልግሎትሽ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ እንዲኾን፣ ፊተኛው ክርስቶሳዊ ዓላማሽንና በስሙ የተነቀፍሽበት እውነት ትዝታ ይኹንሽ! እንዲህ ያለ አደባባያዊ ስህተት በአገልግሎት ዘመንሽ እንደማይደገም ተስፋ አደርጋለኹ፡፡ ጌታ መንፈስ ቅዱስ ፊቱን ያብራልሽ፤ ይራራልሽም፤ መንገድሽንም ያቅናልሽ፤ ፊቱንም ወደ አንቺ ያንሣ፥ ሰላምንም ይስጥሽ፤ አሜን፡፡


11 comments:

  1. ወንድሜ ሆይ!!! ሰሚ ጆሮና አስተዋይ ልብ ያላችውን አገልጋዮች እና ሰዎች እግዚአብሄር ይስጥህ፡፡ ዘርፌን በጣም ከማከብራችውና ከተጠቀምኩባቸው አገልጋዮች አንዱዋ ነች ነገር ግን ከቃሉ እውነት ሚዛን ካነሱብኝ በወንድማዊ ፍቅር ደረጃ እወዳቸዋለሁ፡፡ እህቴም ከዚህ ትንቢታዊ/እኔ ብያለሁ/ መልእክት ብዙ እንደምትማሪ እንደምታስተካክይ ተስፋ አደርጋለሁ ወንድሜም እህቴም ተባረኩ፡፡

    ReplyDelete
  2. እውነት ነው ግን እርሷ የምትሰማህ አይመስለኝም፡፡ እርስዋ እኮ በጴንጠየው አለም ወደንግስትነት እየተሸጋገረች ያለች ናት፡፡ ልቧም ሸፍቷል፡፡ ፕሮግራሙ ላይ ብታያት ብዙ ስትዝት ነበር፡፡ ደጋግማ ስትፎክርም ነበር፡፡ እና ብትሰማ ደስ ይል ነበር፡፡ አንተ ግን ትቢያን አራግፈሃል፡፡ በሥራህ በርታ

    ReplyDelete
  3. wendme betam Geta ybarkh. ene botaw lay neberku ndd neber yalkut. geta lib yistat bcha

    ReplyDelete
  4. wendme sibeza betam dekama neh. lemn sihtt bcha tayalh.esua yemeretechwn meketel tichilalelch. dikam binorbatm endih mebal alneberebetm

    ReplyDelete
  5. ጌታ ኢየሱስ በነገር ሁሉ ይርዳህ፡፡

    ReplyDelete
  6. እንግዲያው ምን ታመጣለህ ይኸው እስዋ ሞገስ አጊኝታ በአዋሳም ድጋሚ አስመረቀች፡፡ ተቃጠሉ፡፡ ምን ጣመጡ፡፡ ለእኛ ትልቅ አገልጋያችን ናት፡፡ እንደምታየው በሁሉም ቦታ ትወደዳለች

    ReplyDelete
  7. የመዝሙር አገልግሎትሽ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ እንዲኾን፣ ፊተኛው ክርስቶሳዊ ዓላማሽንና በስሙ የተነቀፍሽበት እውነት ትዝታ ይኹንሽ!...ጌታ መንፈስ ቅዱስ ፊቱን ያብራልሽ፤ ይራራልሽም፤ መንገድሽንም ያቅናልሽ፤ ፊቱንም ወደ አንቺ ያንሣ፥ ሰላምንም ይስጥሽ፤ አሜን፡፡
    its seams good zealous and i think your observation and advice is for the gospel not for religious.

    ReplyDelete
  8. አሁንስ ሰለቻችሁ ወሬዋ ሁሉ እሷ

    ReplyDelete
  9. ሰው ኃጢአት ሲሰራ ፀሎት እንጅ ሃሜት የሃይማኖት መገለጫ አይደለም ፀልዩ እንፀልይ እንድትመለስ እንዳትርቅ።

    ReplyDelete
  10. metfiyashen abejesh ewenet temochaleshe

    ReplyDelete
  11. Zerfa ena getchwe asfa hultum ande nachew y Ethiopian people yekadu

    ReplyDelete