Sunday 29 May 2016

ለካ በተጣዱበት የሚሞቁ ምርጥ አርቲስቶች አሉን?¡¡¡


    አውቃለሁ ፤ ክርስትና የመገለጥ ጉዳይ እንጂ የእውቀት ጉዳይ አይደለም፡፡ ይህን የምለውም በግኖስቲካዊ አቋም ዕውቀትን ከሚያመልኩ ጐን በመሰለፍ ወይም አምርረው ከሚጠሉትም ጐራ ራሴን በመደመር አይደለም፡፡ ክርስትና በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የሆነውን ቤዛነትና ውጅት ማመንና ይህንንም መንፈስ ቅዱስ በፍጹም መገለጥ የሚያስተምረን ሕያው እውነት ነው፡፡ ይህም የሚሆነው ላመኑትና ለተቀበሉት ብቻ ነው (ዮሐ.1፥12)፡፡

  ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን አምኖ መቀበል ማለት፥ በሕይወታችን ፣ በትዳራችን ፣ በሥራችን ፣ በሁለንተናችን እርሱን ማመንና በተገለጠ ቅዱስ ሕይወት እርሱን ጌታችንን በኑሮአችን መመስከር ማለት ነው፡፡ ጌታ ኢየሱስን ለማመንና ለመቀበልም ሆነ ለማገልገል ፍጹም መሞት ያስፈልጋል፡፡ በትክክል ሳንሞት በትክክል መኖር አንችልም ፤ በትክክል ሳንኖርም በትክክል መሞት አንችልም፡፡ መስቀል ባልፈተነው ጉብዝና እንደመኖር ባዶ ክርስትና የለም፡፡

    አማኝነት ከአባልነት የበለጠ ቅርበት አለው፡፡ የቀደሙት አማኞች ደቀ መዛሙርት ይባሉ ነበር፡፡ ደቀ መዝሙርነት ራስን መካድና መስቀል መሸከምን ይጠይቃል፡፡ ራስን መካድ ማለት፥ እኔ የሚለውን ማንነት ክዶ፥ ክርስቶስን በዚያ ቦታ መሾም ነው፡፡ ደቀ መዝሙርነት የቤተ ክርስቲያን ወይም የአማኞች ሁሉ ጥሪ ነው፡፡ መስቀሉ ጭልጥ አድርገን ልንጠጣው የታዘዝነው ውብ መንገድ ነው፡፡ የሽንፈት መንገድ ቢመስልም እንኳ ልናደርገው ታዝዘናልና ማድረግ ይገባናል፡፡ አስተውሉ! ጌታ ኢየሱስ የመከራንና የሞትን ስሜት በማደንዘዣ እንዲቀበለው አይሁድ ሆምጣጤን ሰጥተውት ነበር ፤ እርሱ ግን ተፋው ፤ ሊቀበለውም አልወደደውም፡፡ ጌታ ትክክለኛውን ሕመም ታሞ፥ ሞቷል፡፡ አቋራጩን መንገድ አልተጠቀመም ፤ “አባቴ፥ ቢቻልስ፥ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ፤ ነገር ግን አንተ እንደምትወድ ይሁን እንጂ እኔ እንደምወድ አይሁን” (ማቴ.26፥39) ቢልም፥ ጽዋው በመጣ ጊዜ ግን ጭልጥ አድርጐ ጠጥቷል፡፡
     የሽንፈት የሚመስለው ቦታ የድል ቦታ ሆኗል፡፡ ይህን የድል ቦታ እናልፍበት ዘንድ ተፈቅዶልናል ፤ ደግሞም እንድንኖርበት ታዘናል፡፡ ክርስቲያን ዘወትር መንገዱ፥ መስቀሉ ነው፡፡ ከመስቀሉ ውጪ አቋራጭ መንገድ የለንም፡፡ ይህን የደቀ መዝሙርነትን መንገድ ለማለዘብ ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ ዘመናት ብዙ ስህተቶችን ሠርታለች፡፡ እግር እንዲያጥቡ የተጠሩ ብዙ ደቀ መዛሙርት ቀሚሳቸው የማይነካ “ጀግኖች” ፤ የጦር ክተት አዋጅ አስነጋሪ ጄኔራሎች የሆኑትና ፤ የነገሥታትና የፖለቲከኞች ዲስኩርን በመምከር የባዘኑት የመስቀሉን መንገድ ለማለዘብ በማሰብና በመካድም ጭምር ነው፡፡
     ከአንድ ወር በፊት ቃና ቲቪ የትርጉም ፊልም ሥራዎቹን ለማቅረብ የተቆረጠ ቀኑን ሲናገር፥ የአርቲስቱ ዓለም ደቦ ተጠራርተው ተሰባሰቡ ፤ ተሰባስበውም ለኢትዮጲያ ሕዝብና ለወጣቱ ትውልድ ምንም ስሜት በማይሰጥ ቋንቋ፥ “ቃና ቲቪ ጥቅማቸውን ሊጐዳ ፤ ሙያቸውንም ዝቅ ሊያደርግ እንደሚችል ፤ አዲስና እንግዳ የሆነ የባህል ልምምድን ለትውልዱ ያስተምራል” ብለው “ተጯጯኁ”፡፡ ከወር በኋላ በሰሞኑ ደግሞ፥ “ሃይማኖተኞችን ነን” በማለት ልብሰ ተክህኖ ቀረሽ ልብሳቸውን “ደርተው” በየመገናኛ ብዙሃኑ ራሳቸውን ገልጠው ታዩ፡፡
     ለመሆኑ፥ አርቲስቶቻችን ኢ- ክርስቲያናዊና ኢ- ኢትዮጲያዊ የሆነ ምግባርን በማስተማር የሚቀድማቸው አለን? የፊልሞቻቸው አዝማችና የዘፈኖቻቸው መዳረሻ ርኩሰት ፣ መዳራት ፣ ዝሙትና ቅንዝረኝነት …  አይደለምን?  ከእጅግ በጣም ጥቂቶቹ በቀር ከሠሯቸው ሺህ ፊልሞች መካከል እስኪ አገራዊ ፣ ባህላዊ ፣ ፖለቲካዊ ፣ ኢኮኖሚያዊ … ፋይዳ ላይ አተኩረው የሠሩትን ፊልም ቆጥረው ያሳዩን? ለመሆኑ የሕዝብን በደልና ሮሮ ፤ ሐዘንና ችጋር ፤ ብሶትና ጭንቀት አድበስብሶ አላፊና አላጋጭ፥ ብሎም በትንታግ ብዕራቸው የጻፉ ስንት የኢትዮጲያ ምርጥ ልጆች የተገፉትና በጠለቀ መቃብር የተቀበሩት በእኛው “ሃይማኖተኛ አርቲስቶች” አይደለምን? ኸረ ለመሆኑ የኢትዮጲያን ብሔራዊ አንድነት ሸራርፈው በፊልሞቻቸውና በዘፈኖቻቸው በትውልዱ ሕሊና የልዩነትና የብሔርተኝነትን መንፈስ ከፖለቲከኖች ይልቅ የሰነቀሩት የእኛው ጉድ የማያልቅባቸው አርቲስቶች አይደሉም ወይ?
     አርቲስቶቻችን “ምንም አይሳናቸውም”፡፡ “የመንግሥትን ዘንግ” ጨብጠው ሴሰኝነትን ፣ ዝሙትን ፣ ዘፋኝነትን ፣ መለያየትን … ሲሰብኩብን ኖረው፥ አሁን ደግሞ “በቤተ ክህነት በትር” የሃይማኖት መልክ ለብሰው ፤ ዓኖቻቸውን በጨው አጥበው በቲቪ መስኮት ብቅ “አሉልን”፡፡ ታዲያ “ምን ይሳናቸዋል?”
    ቃና ቲቪ ሲከፈት ለጥቅማቸው ብቻ እንዳልተሟገቱና መንፈሳዊነት ምንም ግድ እንዳልሰጣቸው እያወቅንና እያወቁ፥ አሁን ለምን ይሆን ተቧድነው የሃይማኖት መልክ ይዘው የመጡት? ትላንትና ሃይማኖተኞች ነን ብለው “መዝሙር ዘመሩ ፣ ድራማ ሠሩ ፣ ስብከቱንም ሰበኩ” ፤ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር አካላት አይተው እንዳላየ ሆነው “ገንዘባቸውን ተቀብለው” በዝምታ አለፉት፡፡ የተዘነጋው ቀኖና ግን፦
     “ … እኒህን ሰዎች መላ ዘመናቸውን ከቤተ ክርስቲያን እንዳይገቡ ከምዕመናን እንዳይገናኙ ሊከለክሏቸው ይገባል” (ተግሳጽ ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አን.4 ገጽ.43)

      “ልበ ደንዳና ከሆነ ሰው መባዕ አትቀበል፥ … ከሰካሮችም ቢሆን ለባህርያቸው የማይገባውን ከሚሠሩም ከሚቀበሉ ቢሆን … መባእ አትቀበል፡፡ አሁን ከተናገርናቸው ከሌሎች ኃጥአንም ቢሆን መባዕ የሚቀበል ለእግዚአብሔር የሚገባውን መባእ ወደሚያቀርቡበት መሠዊያ የተከለከለውን ዓይኑ የታወረውን እግሩ ያነከሰውን ቃባ የያዘውን በግ ለመሥዋዕት  ያቀርብ እንደነበረው ምሥዋዐ ብርቱን እንደአሳደፈው እንደኦሪቱ ካህን እግዚአብሔርን  በክህነቱ ደስ አያሳሰኘውም፡፡”
    (ሃ.አ ዘሠለስቱ ምዕት ምዕ.22 ቁ.6-11 ገጽ.46-47)

      “ከደጋጎቹ ምዕመናን ቁርባን በቀር መሥዋዕት አይሠዉ፡፡ የተሳዳቢዎችን … የሴሰኞችን… የሌቦችን … የሰካራሞችን ባልቴቶችንና ድሀ አደጎችን የሚያስቸግሩትን የቀራጮችን የቀማኞችን የዓመጸኞችን መባዕ አይቀበሉ፡፡ ድሆችን የሚያስቸግሩ ጭፍሮች በግድ ሰዎችን ከሚያስሯቸው ባሮቻቸውን በክፉ አገዛዝ  ከሚገዟቸው ክፋትም ከሚያደርጉባቸው በግፍ ከሚበድሉ ሰዎች ወገን መባዕ(መሥዋዕት)አይቀበሉ፡፡ … ብልሁ ሰሎሞን እንደተናገረ እግዚአብሔር የኃጢአተኞችን መሥዋዕት ይጸየፋልና፡፡(ምሳ.15፥8) (ፍ.ነ አን.13 ቁ.501 ገጽ.138)

ይላል፡፡
     አንድ ነገር ግን መናገር እወዳለሁ፡፡ ቃሉ፦ “ሊሠራ የማይወድ አይብላ” (2ተሰ.3፥10) ይላልና ሥራ መሥራት በእግዚአብሔር የተፈቀደ መልካም ነገር ነው (ዘፍ.2፥15)፡፡ ሥራ መንፈሳዊ ተግባር ነው፡፡ መሥራት እየቻሉ አለመሥራት ኃጢአት ነው፡፡ ለአማኞች የትኛውም ሥራ የሚያመልኩትን ጌታቸውን የሚያስነቅፍ ፤ በክርስቶስ ደም የተቀደሰ ሕያው መቅደስ ሰውነታቸውን የሚያረክስ መሆን የለበትም፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ እንደነገረን፥ “ቀራጮች(የአገር ውስጥ ገቢ ሠራተኞች) ከታዘዘላቸው አብልጠው እንዳይወስዱ … ጭፍሮች(ወታደሮች ወይም ፖሊሶች) በማንም ግፍ እንዳይሠሩ ማንንም በሐሰት እንዳይከስሱ፥ ደመወዛቸው እንዲበቃቸው” ተናግሯል (ሉቃ.3፥10-14)፡፡ ምናልባት ዛሬ መጥምቁ ዮሐንስ ቢኖርና የአገራችን አርቲስቶች ቀርበው (ልብ ገዝተው ቢሄዱ ማለቴ ነው) “ምን እናድርግ?” ቢሉት፥ እንዲህ የሚላቸው ይመስለኛል፦
“አትሸቃቅጡ ፤ ራሳችሁን ሁኑ ፤ ሕዝባችሁን አትሸንግሉ ፤ መዳራት ፣ ርኩሰት ፣ ይብቃችሁ ፤ ያላገጣችሁበትንና የበደላችሁትን ሕዝብ ይቅርታ ጠይቃችሁ ንስሐ ግቡ ፤ የሃይማኖት መልክ ስላላችሁ የምትጸድቁ አይምሰላችሁ”

እንደሚላቸው አልጠራጠርም፡፡ እርሱ፥ እንኳን እነርሱን ሙሉ በትረ መንግሥት የጨበጠውን ሄሮድስንስ መች ፈርቶ?!
      እግዚአብሔር ቅዱስ ነው ፤ ቅድስናም የባሕርይ ገንዘቡ ነው፡፡ ልክ እንዲሁ፥ እግዚአብሔር በኃጢአት ላይ ጨካኝ ነው፡፡ ጨካኝ ስለሆነም ልጁን ለኃጢአት ቤዛ ይሆን ዘንድ በውርደት ሞት እንዲሞት ጨክኗል፡፡ እንዲህ ለልጁ አንዳች ሳይራራ እንዲሞት የጨከነ እግዚአብሔር ንስሐ በማይገቡ ፤ በሚያምጹና በሚያላግጡ ኃጢአተኞች ላይ በእውኑ እንግዳ ነገሩን (ፍርዱን) የማያመጣ ይመስላችኋልን? እውነት ሚዲያው በእጃችን ስላለና የሃይማኖት አባቶች “ጐበዞች ፤ ጥሩ እኮ ናችሁ” ስላሉንና፥ እኛም “ሃይማኖቴ ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ነው” ብለን በሽለላ መልክ ስለተናገርን የምንጸድቅ ይመስለናል? አይመስላችሁ ፤ ኦርቶዶክሳዊው የመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ለዘፋኝ መቼም እውቅና ፤ ለአመንዝራ ፣ ተዳሪና ሴሰኛ … አርቲስት “አባሌ ነህ” ብሎ የምስክር ቃሉን ሰጥቶ አያውቅም ፤ ወደፊትም አይሰጥም፡፡ ይህን እውነት በመሸቃቀጥ የሚያንሻፍፉ ቢኖሩ በቃሉ ያለ እርግማን እንደሚያገኛቸው ጥርጥር የለውም፡፡
     እኔን የአርቲስቶቹ ድፍረት አይገርመኝም ፤ እነርሱ በተጣዱበት ይሞቃሉና፡፡ ደግሞስ ለከፈላቸው “ምን የማይሠሩት ነገር” አላቸው?(እነርሱ አንሠራም ብለው ቢሸልሉም!) … እነርሱን የሃይማኖት ካባ አልብሶ የሚያቆማቸው የሃይማኖት አባትም ሆነ ፤ አካል ግን እርሱ ይበልጥ ያሳፍረኛል፡፡ እግዚአብሔር በሰው ዝናና ክብር ፤ ሥልጣንና እውቅና ፤ ከአለማዊነትም በተገኘ ሙገሳ ፈጽሞ ፤ እጅግ ፈጽሞ እንደማይሠራ ማን በነገራቸውና በሰሙ? “ … እግዚአብሔር ጥበበኞችን እንዲያሳፍር የዓለምን ሞኝ ነገር መረጠ፤ ብርቱንም ነገር እንዲያሳፍር እግዚአብሔር የዓለምን ደካማ ነገር መረጠ ፤ እግዚአብሔርም የሆነውን ነገር እንዲያጠፋ የዓለምን ምናምንቴ ነገር የተናቀውንም ነገር ያልሆነውንም ነገር መረጠ፥” (1ቆሮ.1፥27-28) የሚለው ቃል ከወዴት ተዘነጋ?
      የእኛ ክብርና ሽልማት የእግዚአብሔርን ሥራ አይሠራም ፤ የሰው ቅንአት የእግዚአብሔርን ቤት አይጠብቅም፡፡ ያለእግዚአብሔር የእግዚአብሔርን ሥራ መሥራት አንችልም፡፡  የእግዚአብሔርን ሥራ ልንሠራ የሚቻለን በእግዚአብሔር መንፈስና በቅድስና ብቻ ነው፡፡ በአለማዊ እውቀትና በምድራዊ ዝና ፤ በሰው ዘንድ ባለን ብርታት እግዚአብሔርን ለማገልገል ማሰብ እግዚአብሔርን ካለማወቅም ባሻገር ቅዱሱ አገልግሎት ላይ መዘባበት ነው፡፡
     አዎን! የእግዚአብሔር እውነተኛ አገልጋዮች ለዓለማዊው ርኩሰትና ኃጢአት የሞቱና ለክርስቶስ ወንጌል ሥራ ሕያዋን የሆኑ ትሁታን ባርያዎችና አለምና በውስጧ ያሉትን ሁሉ የናቁና የማይመኙ ፤ በተጣዱበትም ሁሉ የማይሞቁ ናቸው፡፡ እናም አርቲስቶቻችን ሆይ! ከአገልግሎታችሁና ከደፋ ቀናችሁ በፊት እግዚአብሔርን በልባችሁ ፣ በሥራችሁ ፣ በትዳራችሁ ፣ በገንዘባችሁ ፣ በሕይወታችሁ አንግሱት ፤ ወጭቱ በአግባቡ ሳይጠራ ማን ይሆን በወጭቱ መልካሙን ወጥ የሚያኖርበት? … ቀድሞ ወጭታሁን አጥሩ ፤ ንስሐ ግቡ ፤ የቀለዳችሁበትን ሕዝብ ንስሐ በመግባት ይቅርታ ጠይቁት ፤ እግዚአብሔር ጻድቅ ነውና፡፡
    ጌታ ማስተዋሉን ያብዛልን፡፡ አሜን፡፡



16 comments:

  1. Hulachenem Egziyabher yaseben

    ReplyDelete
  2. ewent new amelak agelegelotehen yebarek enesunem lebachewen elekegna edayaderegu amelak yeredachew amen

    ReplyDelete
  3. ከአንተ ክፉ አነጋገር በብዙ እጥፍ እነርሱ ይሻላሉ በእውነት። አምላካችን ክርስቶስ የሞተው መራራ ጽዋን የተጎነጨው ለኃጢያተኞች መስሎኝ ያሳዝናል መጀመሪያ አንደበትን መግታት ይቀድማል። አንተ ከቃል ባላለፈ ለማትኖርበት ክርስትና ምነው ከእነርሱ ፍጹምነትን ጠበቅህ። ልቦና ይስጠን።

    ReplyDelete
  4. Ha ha ha
    አይንህ ቀላ አይደል? ዲያብሎስ እና ልጆቹ መቼ ጥሩ ገር ትወዳላችሁ?

    ReplyDelete
  5. መቸም ሰዎች ስንባል የራሳችንን ሃይጥያት ተሸክመን የሰውን ማውራት እንወዳለን። እነሱ የተዘጉና ረዳት ያጡ ቤተክርስትያናትንና ገዳማትን ለመርዳት የበኩላቸውን ጥረዋል። ከጎናቸው ሆነን ልናበረታታቸው ሲገባ በስድብና ባሉባልታ አናት አናታቸውን እንላቸዋላን። መጀመርያ የራሳችንን እድፍ እናጥራ።

    ReplyDelete
  6. ለዚህ ሁሉ ተጠያቂዎቹ የሃይማኖት አባት ሊቃውንትና ጳጳሳት መሪዎች ናቸው የኸም ታጥቀው ሥረዓት አበግጅተው ባለማስተማራቸው ነው። ከተሳሳትኩ ይቅርታ ?

    ReplyDelete
  7. አዎን! የእግዚአብሔር እውነተኛ አገልጋዮች ለዓለማዊው ርኩሰትና ኃጢአት የሞቱና ለክርስቶስ ወንጌል ሥራ ሕያዋን የሆኑ ትሁታን ባርያዎችና አለምና በውስጧ ያሉትን ሁሉ የናቁና የማይመኙ ፤ በተጣዱበትም ሁሉ የማይሞቁ ናቸው፡፡ 2 ቆሮንቶስ 5:14 ይህን ስለቆረጥን የክርስቶስ ፍቅር ግድ ይለናልና፤ አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ፤ እንግዲያስ ሁሉ ሞቱ፤
    15 በሕይወትም ያሉት ስለ እነርሱ ለሞተውና ለተነሣው እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው እንዳይኖሩ ስለ ሁሉ ሞተ። ለሞተልን ብቻ መኖር እንድንችል ጌታ ጸጋዉን ያብዛልን!

    ReplyDelete
  8. አርቲስት ሰለ ጌታ ወንጌል ምን ያቅና!!!!

    ReplyDelete
  9. ይህን የመሰለ የቅናት መንፈስ የበግ ለምድ ከለበሱ ተኩላዎች የሚወጣ ነው:: የበጉ ለምድ አይገባህም:: ምን አይነት ህይወት እንደሚኖሩ ሳታውቅ ለመንቀፍ ቸኮልክ:: በርግጠኝነት አንተን ያጥፉሃል::

    ReplyDelete
  10. ምነው ገና ከመጀመርህ ፍረድ ፍረድ አለህ….ፈራሁልህ

    ReplyDelete
  11. ምነው ገና ከመጀመርህ ፍረድ ፍረድ አለህ….ፈራሁልህ

    ReplyDelete
  12. ምነው ገና ከመጀመርህ ፍረድ ፍረድ አለህ….ፈራሁልህ

    ReplyDelete
  13. እውነት ነው መዝፈን መጠጣት ለኦርቶዶክስ ምንም አይደለም አጢያት አይደለም ጌታን ለተቀበለ ብቻ ነው አጢያት

    ReplyDelete
  14. መዝፈንም መጠጣትም መዘመርም ለኦርቶዶክስ ይቻላል

    ReplyDelete