Thursday 20 July 2023

የ“አነቃቂዎቹ” ድንዛዜ!

Please read in PDF

ዶክተር ወዳጄነህ መሐረነ “አነቃቂ” ንግግር ያቀርባሉ ከሚባሉ ሰዎች መካከል አንዱ ነው። በአነቃቂዎች ዙሪያ በተደጋጋሚ ለመጻፍ ዐስብና ብዙዎች መልስ በስላቅ፣ በቅኔ፣ በድራማ፣ በ“አሽሙር”፣ በስዕላዊ መንገድ፣ በወግ … መልስ ስለ ሰጡበት ብዙም መናገር አልፈለግኹም። በእርግጥ “አነቃቂ” እንደ ኾኑ የሚያስቡ አካላት፣ እጅግ በሚያደንቅ መልኩ የሕይወት ምሳሌነት የሌላቸው (ኹሉም በሚያስብል መልክ ትዳራቸው በፍቺ የተጠናቀቀ፣ ጾታዊ ግንኙነታቸው አኹንም እንኳ ጤናማ ያልኾነ)፣ ነገረ መለኮታዊ ዕሳቤያቸው ከመጽሐፍ ቅዱስ የማይገጥም፣ ከነባራዊው እውነትና ከማኅበረ ሰቡ መልካም እሴቶች ጋር ፈጽሞ የማይጣጣም፣ ግለኝነትን የሚያበረታታና መንፈሳዊና ማኅበረ ሰባዊ አንድነትን የሚንድ … አመለካከቶችን በውስጡ ያጨቀ ነው።


በምዕራቡ ዓለም በዚህ መንገድ የሄዱ ሰዎች፣ ፍጻሜያቸው አሰቃቂ እንደ ነበር ብዙ ምሳሌዎችን መጥቀስ ይቻላል። ንግግሮቻቸው ከቅዠት ዓለም ለመቀዳታቸው ነቢይነት አያሻውም! ከዚህም ባሻገር፣ የዕውቀት ጥጋቸው “ወደማይሰሙ ቅዱሳን” ጸሎትን ማቅረብ ኾኖአል፤ ይህም የሙታን ሳቢ መንፈስን መጠጋታቸውን ያሳያል። ለዚህ ደግሞ በዋቢነት ከላይ ስሙን የጠቀስነውን ሰው በምሳሌነት ሊነሳ ይቻላል።

ዶክተሩ የወንጌላውያን አማኝ ነኝ እያለ ከርሞ፣ በኋላ ላይ ወደ ኦርቶዶክስ ማዘንበሉ ይታወሳል፤ አኹን ደግሞ የካቶሊክን ወይም የኦርቶዶክስን መንገድ በመከተል፣ ወደ ማርያም ጸሎት ሲያቀርብ እንመለከታለን። አነቃቂ ነን ባዮቹ ሰዎች፣ የእምነት እንቅስቃሴ መንገድ ጠራጊዎች ለመኾናቸው ማሳያው፣ መሥራቾቻቸው የአዲሱ ትውልድ እንቅስቃሴ አራማጆች መኾናቸው ነው፤ ለምሳሌ ብንጠቅስ፦ የእምነት እንቅስቃሴ መሥራች በመባል የሚታወቀውን የኤሴክ ዊሊያም ኬንየንን ፍልስፍናዊ ትምህርት በመከተል የ“New thought theology” ፍልስፍናን ይበልጥ ያዘጋጀውና በሚገባ ያሰናዳው ፊንሐስ ቁምቢ(Phineas P. Quimby)(1829-1910 ዓመተ እግዚእ)፣[1] በመንፈሳዊውና በማይታየው የአእምሮ ክፍላችን፣ ሊመጣ ያለውን ማናቸውንም ነገር ማዘዝና መቈጣጠር እንችላለን የሚል እሳቤ ያዘለውን ትምህርት በማስተማሩ ሲታወቅ፣ ቦብ ፕሮክተር፣ “እኔ በሥጋ ውስጥ የምኖር መንፈሳዊ ሰው እንጂ ከመንፈስ ጋር የምኖር ሥጋዊ አካል አይደለሁም” በማለት በግልጽ የተናገሩ ናቸው[2]



እኒህን በምሳሌነት አነሳን እንጂ፣ አብዛኛዎቹ “የአዲሱ ትውልድ እንቅስቃሴ” አነቃቂ ነን ባይ ለፍላፊዎች፣ ትምህርቶቻቸውና ልምምዳቸው ከዚህ የራቀ አይደለም። እንግዲህ ከአገራችን “አነቃቂ ነን” ባዮች መካከል አንዱ ነው፣ ወደ ማርያም ሲጸልይ የምንመለከተው። ድንግል ማርያምን ማክበር ማለት፣ ከመጽሐፍ ቅዱስ በተቃራኒ “ወደ እርስዋ መጸለይ” ማለት አይደለም። ብጹዕ አቡነ ሺኖዳ፣ “ወደ ማርያም ወደ ቅዱሳን መጸለይ ተገቢ ነው?” ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ ቆፍጠን ያለ መልስ መልሰዋል፤ ወደ ቅዱሳን መጸለይ ተገቢ እንዳልኾነና ወደ እነርሱም እንደማይጸልዩ በግልጥ በመናገር።[3] እንግዲህ የቤተ ክርስቲያኒቱ እውነተኛ አባቶች የማይሉትን፣ እነዶክተርና አነቃቂዎቹ ለመወደድና ዝና ለማግኘት በመቃተት በከንቱ ይባዝናሉ! እንግዲህ ለሚሰማ እንዲህ እንላለን፤ “መንፈስ ግን በግልጥ፦ በኋለኞች ዘመናት አንዳንዶች የሚያስቱ መናፍስትንና በውሸተኞች ግብዝነት የተሰጠውን የአጋንንትን ትምህርት እያደመጡ፥ ሃይማኖትን ይክዳሉ … ለዚህ ዓለም ከሚመችና የአሮጊቶችን ሴቶች ጨዋታ ከሚመስለው ተረት ራቅ። እግዚአብሔርን ለመምሰል ግን ራስህን አስለምድ።” (1ጢሞ. 4፥1-2፡ 7)።

“ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን በማይጠፋ ፍቅር ለሚወዱ ኹሉ ጸጋ ይኹን፤ አሜን” (ኤፌ. 6፥24)።

 



[1] አንዳንዶች ኬንየን ከፊንሐስ ኩምቢ ትምህርት መማሩን ወይም ተምሯል የሚለውን ሃሳብ አይቀበሉም፤ ምክንያታቸውን ሲያቀርቡ ኬንየን በዚያ የተማረው ሰውየው ኮሌጁን ከቀየረ በኋላ ነው በማለት ይሞግታሉ። እንዲህም ቢኾን እንኳ ግን አንድ ነገር መሳት አንችልም፤ የትምህርቱን ተዛማጅነትና ትስስር፤ ምሳሌ ብንጠቅስ፦ ኹለቱም ትምህርቶች ሰው፣ በሽታና ፈውስን በተመለከተ የሚሰጠው አስተምኅሮ ተመሳሳይ ይዘት አለው፤ ይኸውም ሰው መንፈሳዊ ነው፤ በሽታም አእምሯዊ ወይም መንፈሳዊ ስለኾነ፣ ከበሽታ አንድ ሰው የሚፈወሰው ወይም የሚድነው በአእምሯዊ መንገድ ወይም በመንፈሳዊ መንገድ ነው የሚለው አስተምህሯቸው አንድ ዐይነትነት አለው። ምንም እንኳ ኬንየን በዚያ መንገድ አልተማረውም ብንልም፣ የትምህርቱ ውጤት አንድ መኾኑን ልንዘነጋው አይገባንም።

[2] አቤንኤዘር ተክሉ (ዲያቆን)፤ የእምነት እንቅስቃሴ የዛሬዪቱ ቤተ ክርስቲያን ፈተና፤ 2010 ዓ.ም ዐዲስ አበባ፤ አሳታሚ ቤቱ ያልተጠቀሰ።

[3] አቡነ ሺኖዳ፤ Comparative Theology; ገጽ 121-122

2 comments:

  1. የማቴዎ ስወንጌል
    10፥40 እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል።

    ወገን እናስተውል! ይህንን ቃል የተናገረው ጌታችን መድኋኒታች ኢየሱስ ክርስቶስነው፥
    መዳን በሌላ በማንም የለም፡እውነት ነው ቃሉ የታመነ ነው።ግን ምን ማለት ነው? ቤ/ንም በዚህ ቃል ታምናለች። ጸሃፊው ጌታን እና ቅዱሳንን እያወዳዳረነው በጣም ይገርማል ትልቅ ስህተት ነው።ቅዱሳን ይህ ቃል የተሰጣቸው እርሱን ተጠግተው ነው። ቃሉን ሰምተው የተሰጣቸው ልዩ ስጦታ ነው። እንደውም እርሱን ለመቀበል የመጀመሪያው መስፈርት አድርጎታል።ምን ይዋጥህ?? ምቀኛ!! አርፈህ ቃሉን አስተውል። የክርቶስን ማዳን ማንም አይተካዉም፣ የሚተካውማ ብኖር ወደዚህ ምድር ምን አስመጣው??? በኦሪቱ ብዙ መስዋት ተሰውቷል፡ብዙ ነብያትም ነበሩ፡ አልቻሉም ምክኛቱም አዳማዊ ህትያት በደማቸው ስለነበር፡ አካላዊ ቃል፣ በሱ ፈቃድ ባባቱ ፈቃድ እንዲሁም በባሕሪ ህየወቱ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ወደዚህ ምድር መጣ። እኛን ሊያድን። አዳነን ነጻም አወጣን። ስለዚህ ይህ ድህነት በማንም አልነበረም ወደፊትም አይኖርም።ባጭሩ

    ReplyDelete
  2. እግዚአብሔር አዳኝ አምላክ ነው። ማዳኑን ሥራ ለቅዱሳን ሰጣቸው።ያዕቆብ ወንድም ይሁዳ ቁጥር 22 አንዳንዶችንም ከእሳት ነጥቃችሁ አድኑ። የምለው የጌታ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ቃል ሐዋርያው የተናገረውን መካድ የክርስቲያን ጠባይ አይደለም።ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በሞቱ ፍጥረታቱ ሁሉ በደሙ ከሐጢአታችን አንጽቶናል። ይህን ስራ ማንም ልያደርገው አይችልም። ነገር ግን ሰዎች ከሐጢአት መንገድ መመለስ አንዱ የማዳን ሥራ ነው። ሐጢአት መስራት በራሱ ሞት ነውና። ከዚህ ከሐጢአት ሞት ሰዎችን በመመለስ በህይወት እንድኖሩ ማድረግ ለቅዱሳን ሰዎች የተሰጠ ስልጣን ነዉ። ስለ ሰው ሐጢአት መጸለይ የማዳን ስራ ነው። ሰዎች ወደቅድስና ሕይወት እንድመለሱ ማድረግን የማዳን ስራ ነው። ነገር ግን የአዳምን በደል በሞቱ ያጠፋው ጌታችን አባታችን ኢየሱስ ከርስቶስ ብቻ በመስቀል ዲያቢሎስን ድል በመድረግ አዳነን። ለአንደና ለመጨረሻ በእርሱ ተፈጸመ። ዛሬ ግን እርሱ በየቀኑ አይሞትልንም እኛ ሞቱን ስለበዳለችን እንደሆነ እንመሰክራለን። በጌታ የምያምኑ ቅዱሳን ሰዎች ለሌሎችን ሐጢአት ይጸልያሉ ከሐጢአት ሞት በጸሎት ያድናሉ። ሐዋርያዉ ጰዉሎስም እንኳን እንድህ በማለት ተናግሮዋል 'ወንድሞቼ ሆይ ስለ እኛ ጸልዩ" ማለት ተናግሮ ነበር ወደ 1ኛተሰሎም 5 ፡ 25

    ReplyDelete