Friday 13 September 2013

"ተራ" ምዕመናን አሉን?



        ባለኝ የሥራ ኃላፊነት በአብያተ ክርስቲያናት አለመግባባት መካከል ግጭት ሲፈጠር  አንዳንዴ በአባልነት ፣ሌላ ጊዜ በሽማግሌነት፣አልፎ አልፎ ደግሞ በታዛቢነትና ክስ በማድመጥ የምገኝበት ጊዜ ብዙ ነው፡፡የሌላውን ልተወውና የእኛን የአንድ ቤተ ክርስቲያን  አማኞች ጎራ ለይተው በ"ለኃይማኖቴ እቀናለሁ" በሚል  ፈሊጥ ሲሰዳደቡ ፣ሲካሰሱ ፣ሲደባደቡ፣ሲነካከሱ፣ዓለማዊ ፍርድ ቤቶች ላይ ሲጨቃጨቁ እንደማየት አስቀያሚና አጸያፊ ነውር የለም፡፡ምንም እንኳ ዛሬ ባይታፈርም፡፡ቤተ ክርስቲያን ጸጋ እግዚአብሔር ሲለያት ጠላት ሳይኖርባት እንደእፉኝት ራሷን በራሷ እየበላች ታልቃለች፡፡
     እግዚአብሔር ፍቅር ነው፡፡ፍቅር ነው ሲባል በምንም አይነት ተአምር ቅያሜ አያውቅም፣ማፍቀር እንጂ መጥላት አይችልም  ማለት ነው፡፡ እኛ የእርሱ ልጆች ከሆንን እንደግብዝ ፈሪሳዊና እንደተፈጥሮ ሰው "የእኛ የሆነውን ብቻ በመውደድ " ሳይሆን ጠላትንም እንድንወድ ጠላት የሆነውን እኛን በወደደ በክርስቶስ ኢየሱስ ፍቅርና ርህራሄ ተለምነናል፡፡እኛ ጠላትና ባላጋራ ሳለን ከተወደድን ፍቅሩ አለልክ በዝቶልናል ማለት ነው፡፡ጠላት ሆነን በእንዲሁ ፍቅር ከተወደድን ሌላውን ጠላት ነው ለማለት ሥልጣን ከየት አገኘን? እኛን የያዘ እጅ ሌላውንም የያዘ ነው፡፡የእኛን ጠላትነት በፍቅር የቻለ ልብ የሌላውንም ጠላትነት አብዝቶ የቻለ ነው፡፡አንተ ነውር የተከደነልህ የሌላውን ነውር ታወራና ትከስ ዘንድ ማን ነህ?


       ከሁሉ በላይ ጆሮን ጭው የሚያደርግ ነገር ነው፡፡በተገኘሁባቸው ብዙዎቹ መንፈሳዊ በተባሉ ስብሰባዎችና ውይይቶች ላይ የግል ስሜትና ኢ-ሚዛናዊነት ሲንጸባረቅ አይቻለሁ፡፡ይህ ብቻ ግን አይደለም "አጠፉ፣በደሉ ፣ተሳሳቱ…" የተባሉ ወገኖች (በተለይ ሰንበት ተማሪና ክህነት ያላቸውም አልፎ አልፎ) በአግባቡ ሳይደመጡ ለፍርድ ሲቸኮል ሳይ " ምነው እግዚአብሔርን መፍራት ሆይ! የት ነህ? ሐፍረትስ ከወዴት ጠፋህ? እላለሁ፡፡ ያውም "ተራ ምዕመናንን ለመዳኘትና በእነዚህ ለመፍረድ ጳጳስና ሲኖዶስ አያስፈልግም" ከሚል ንቀትና እንጭጭ አመለካከት ጋር ሲሰማ ልብን ያደማል፡፡
      እውነት ግን "ተራ" የሚባል ምዕመን አለ እንዴ? (ለአንድ አማኝ የሚጨነቁና እንደክርስቶስ ብሌን የሚሳሱ ፣ብዙም የሚለፉና ሐገር አቋርጠው የሚጠይቁ፣ የሚያጽናኑ ምርጥ አገልጋይ ካህናትን፣ዲያቆናትን ፣ቆሞሳትን ፣ወንጌላውያንን፣አባቶችና እናቶችን፣ወንድሞችና እህቶችን፣መጋቢያንና መነኮሳትን እጅግ በጣም የተራራቁ ቢሆኑም ልዩ አክብሮትና ልዩ ስስት ለእነርሱ እንዳለኝ ፈጽሞ የረሳሁ ግን አይደለሁም፡፡እኔ እንኳ ይህንን አለም አይቼ እንደዴማስ ላፈገፍግ ባልሁ ጊዜ አድራሻዬን ፈልገው የመጡና በጌታ ጉልበት የመለሱኝን ውድ የኃይማኖት ወላጆችና ቤተሰቦቼን  መቼም መች አልዘነጋቸውም!!! የሁል ጊዜ ጸሎቴ እናንተን ያብዛ ነው፡፡) አሉ ግን "አንድ ሳር ቢመዘዝ ጎጆ ቤት አያፈስም" የሚሉ መንጋ መሪ መሳይ ዋዘኞች፡፡ የአሮጊት ተረትና ቧልት እየቀላቀሉ ቃሉን የሚሸቃቅጡ!!!
       እውነት ቤተ ክርስቲያን ደጅ ላይ ተቀምጦ የሚለምነው የእኔ ቢጤ በአማኝነቱ ከአንድ ጳጳስና ፓትርያርክ በምኑ ነው የሚያንሰው? በእውኑ ለሌላው የፈሰሰው የክርስቶስ ደም ለዚያ የእኔ ቢጤ አልፈሰሰምን? በእውኑ መንፈስ ቅዱስ በሚመራት ህያው ቤተ ክርስቲያን የሁላችን ክብር አንድ የእግዚአብሔር ልጅነት አይደለምን? በመንግስተ ሰማያትስ ማን ነው ከማን የሚበልጥ? በእውኑ ከሁሉ የሚያንስ ስለመተላለፋችን እንደባርያ የተቆጠረና በፍጹም ትህትና የታዘዘ ክርስቶስ ሁላችንን የሚበልጥ አይደለምን?
      አንድ "ታላቅ" ክህነት ያለው ሰው ቢያጠፋ፣ ቢበድል፣ ተሳሳተ ቢባል ስንት ዕድል ይሰጠው ይሆን? ክህነት የሌለው አንድ የቤተ ክርስቲያን አማኝስ ሲበድል ለምን ከአጠራሩ እንኳ "ተራ ምዕመን" መባል ይዘወተራል? በሐዲስ ኪዳን "ቤተ ክርስቲያን" የሚለው ቃል በሚበዛ ትርጉም ልክ ቤተ አይሁድ የአይሁድ ወገን፣ቤተ እስራኤል የእስራኤል ወገን … እንደሚባለው ቤተ ክርስቲያንም የሚለው ቃል የክርስቲያን (የክርስቶስ) ወገን በሚለው ቃል ነው የተተረጎመው፡፡ ሁላችንም በግል በሰውነታችን (1ቆሮ.3÷16፤ 2ቆሮ.6÷16፤  ሮሜ.8÷9) በማህበር ደግሞ በአንድነታችን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ፣ቤተ ክርስቲያን ነን፡፡ (ሐዋ.12÷1፤ ሮሜ.16÷5፤1ቆሮ.16÷19)፡፡ የክርስቶስ ወገን የሆንነው በእንዲሁ ፍቅር አብ አለምን አፍቅሮ ፣ለእኛ ያለው ፍቅሩንም በልጁ ገልጦ ልጁም ደሙን አፍስሶ ፣የህይወት መንፈስ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ይህን እውነት በልባችን ናኝቶ ነው፡፡ይህ የሆነው ለሁላችን ያለአድልዎ ነው፡፡
     ታዲያ ማን ነው ማንን "ተራ" ማለት የሚችለው? ማን ነው ላንዱ ሺህ ዕድል እየሰጠ ሌላውንም በወግ ማድመጥ እንኳ ነስቶ ሦስት ዕድል የተባለውን የጌታን ትምህርት የሚሽረው? ቤተ ክርስቲያን ይህን በሚገባ ያስተዋለች አይመስልም፡፡ "ተራ" የሚባሉት አማኞቿን በአግባቡ መሰብሰብና መያዝ ስላልቻለች በጥቂት አመታት ውስጥ በሚሊየን የሚቆጠሩ ውድ ልጆቿን አጥታለች፡፡ዛሬ ካራ ስሎ ለማረድና ለመግደል የሚያጉረመርመው የአማሌቅ ድምጽ የሚበዛው ቁጥር ከዚህች እናት ቤተ ክርስቲያን የወጣና የሄደ ነው፡፡እነዚያ አንዳንድ ሳሮች ዛሬ ሚሊየን ሆነዋል፡፡ምነው ይህ ሁሉ ህዝብ በምን ምክንያት የት ሄደ ብሎ መጠየቁ ምነው ተሰወረን???
     ቤተ ክርስቲያን ይህንን በሚገባ ማስተዋል አለባት፡፡አንዱም አማኝ አዎ የቱም ቢሆን "ተራ" "አንድ ሳር" አይደለም፡፡ከጳጳስ እስከ አንዱ አማኝ ሁላችን የክርስቶስ ብልቶች፣ የቤተ ክርስቲያን አካላት ነን፡፡የአገልግሎታችን ድርሻ ይለያይ እንጂ ለክርስቶስ የማያስፈልግ አንድስ እንኳ የለም፡፡በእውኑ ከእኛ ብልቶች የትኞቹ ይሆኑ የማያስፈልጉና ታናሽ ሊባሉ የሚችሉት? ይልቁን ታናናሾቹ ብዙ የሚሰሩና የሚደክሙ አይደሉምን? ጌታ ኢየሱስ የሞተለት እርሱ ፣ያ በግ፣ያ የእኔ ቢጤ፣ያ ድኻ፣ያ አማኝ፣… "ተራ" አይደለም፡፡በደመና የሚነጠቅ ፣አባቱ በቅዱሳኑ መላዕክት ፊት የሚመሰክርለት የእሳት ትንታግ እንጂ!!!
ጌታ ሆይ ወንድሜን እወደው ፣ እንደእግዚአብሔር መልዐክም አከብረው ዘንድ እርዳኝ፡፡ አሜን፡፡

7 comments:

  1. Thank you my brother. I love you.

    ReplyDelete
  2. You known I understand one thing.we don't deserve this name (Christian)we read bible,but the bible can't read us,that is why we can't make any difference.what is the different between US &the world
    You know what he said Mahteme Gandi(former president of Indian 'I hate Christians but I love Jesus.guess what he said that the way we live and the way we token is totally different.PS let us get up &start to live as our father.

    ReplyDelete
  3. Amen yelben new yesafklege

    ReplyDelete
  4. እውነት ነው ወንድሜ ቤ/ክ በዚህ አይነት አመለካከት ባላቸው ተሞልታለች!!! በሰበካ ጉባኤው፣በሰ/ት/ቤት፣በስብከተ ወንጌል……ግን ሁሉ በክርስቶስ ነው ክርስቲያን የተሰኘው ……ለሁላችን ማስተዋል ይስጠን፡፡

    ReplyDelete
  5. ወንድሜ ማስተዋሉን የሰጠህ ልዑል እግዚአብሔር አሁንም ፀጋዉን ያብዛልህ

    ReplyDelete
  6. እግዚአብሔር ይርዳን ወንድምአለም፡፡

    ReplyDelete
  7. እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ማስተዋልን ይስጠን፡፡ እርሱ ይርዳን...

    ReplyDelete