Wednesday 18 September 2013

የተሰሎንቄ እብዶች - 2 (ፈጣኖቹ የጠላት እግሮች!!!)


የመንግስቱን ወንጌል ላለመስማት የራስን በር ጠርቅሞ መዝጋት፣የወንጌሉን ዜና የሚናኙትንም እየገፈተሩ ከሐገርና ከከተማ ማሳደድና ማባረር ይቻላል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን በዘመን ፍጻሜ የተሰጣት ትልቅ ኃላፊነትና አደራ ተኩላዎች በሚበዙባት ምድርና ሐገር ላይ በወንጌሉ ህይወቷን ማነጽና ሳትሰለች ለፍጥረት ሁሉ መናገር ነው፡፡ወንጌሉን ደግሞ አፋችን ተላቆ ገና መናገር ስንጀምረው ተግዳሮቱና ነቀፌታው ሳይውል ሳያድር ያገኘናል፡፡ 
       በተሰሎንቄ ከተማ ያሉ የወንጌል ጠላቶች ወንጌሉንና ወንጌላውያኑን መስማትና ማየት እንኳ ተጠይፈው በጩኸት ድምጽ አሳደዋቸዋል፡፡በጌታ ቃል እንደተነገራቸው ወንጌላውያኑ የእግራቸውን ትቢያ አራግፈው ከከተማይቱ ወጡ፡፡ (ማቴ.10÷14)፡፡ ወንጌል ከእግዚአብሔር ወደእኛ የተዘረጋች የህይወት እጅ ናት፡፡ ለተዘረጋችው እጅ ምላሽ ካልሰጠን እንደጽዋ ለባለተረኛ ትተላለፋለች፡፡ ትላንት እንደዋዛ የሚበዙ እውነተኛ የወንጌል አገልጋዮችን አሳደን ዛሬ ብዙዎቹ አውደምህረትና መድረኮች በፌዘኛና አስቂ ሰባክያን ተይዘዋል፡፡ እውነተኞችን ከመካከላችን ባራቅን ቁጥር ለሐሰተኞችና ለፌዘኞች መገዛታችን ግድ ነው፡፡ ለትልቁ እውነት ካልተገዛን ለትንሹና ለወራዳው ሐሰት መገዛታችን እሙን ነው፡፡ 


       ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የእብዶቹን ከተማ ጥሎ የጌታን ቃል በየቀኑ በማጥናትና በመመርመር ወደሚኖሩባት የቤርያ ወገኖች በሌሊት አመራ፡፡ ወደቤርያ የተጓዙት በሌሊት በሚታረፍበት ሰዓት ነው፡፡ ህዝብ በድንቁርና፣መሪ በሥጋዊ ቅንጦት ፣ሐሰተኛ ወንድሞች እንደአሸን በፈሉባት ፣ኃጢአት እንደክብርና ዝና በሚወራበት ምድር ላይ የሚያርፍ መንፈስ የለምና ከቀኑ አልፎ በሌሊቱም ጊዜ ለሌሎች መዳንና መፈወስ ይተጉ ነበር፡፡ አዎ! ከበዛው የዕረፍት ሌሊታችን ላይ ለጌታ ክብር ማዋልም መታደልና መባረክ ነው፡፡
     ልክ እንደደረሱም ወደምኩራብ ገቡ፡፡ እግዚአብሔር ቃሉን በሐዋርያው አንደበት ስላልኖረና ስላከናወነለት "ስለዚህም ከእነርሱ ብዙ፥ ከግሪኮችም የከበሩት ሴቶችና ወንዶች ጥቂት ያይደሉ፥ አመኑ። (ሐዋ.17÷12)፡፡በተሰሎንቄ ያሉ እብዶች በሩን ቢዘጉትም ጌታ በቤርያ ሌላ ሰፊ በር ከፈተ፡፡ጠላት እንደሚዘጋው በር ቢሆን ወንጌሉ ከኢየሩሳሌም ባልወጣ ነበር፡፡ነገር ግን ጌታ በተዘጋው በኩል እልፍ በር እየከፈተ ወንጌሉ ከእኛም ዘንድ ደርሷል፡፡በእርግጥ ጠላት የሚነካካ እሳት ይበልጥ እንደሚፋፋም አለማወቁ ነው፡፡ወንጌሉ ሲነካካ ፣ሲገፋፋ፣ለእስር ሲታሰብ … ይበልጥ አብዝቶ እንደጸዳል ይፈካል፡፡
      በቤርያ ብዙዎች ቢያምኑም፣የእግዚአብሔር ቃል ቢሰበክም፣ሰዎች ከኃጢአት እስራት ተፈተው አርነት ቢወጡም በዚህ የማይረካ የማይደሰት ጠላት ግን አለ፡፡የበራውን ለማጥፋት ፣የቆመውን ለመጣል ፣የከበረውን ለማዋረድ፣የነጣውን ለማጥቆር … የሚቸኩል የማይታክት ባላጋራ አለ፡፡ቃሉ እንዲህ ይላል፦
"በተሰሎንቄ ያሉት አይሁድ ግን ጳውሎስ በቤርያ ደግሞ የእግዚአብሔርን ቃል እንደ ሰበከ ባወቁ ጊዜ፥ ወደዚያው ደግሞ መጡና ሕዝቡን አወኩ።"(ሐዋ.17÷13)፡፡
ያደቆነ ክፋት ሳያረክስ አይመለስም፡፡የእነርሱ አለመዳን ብቻ ሳይሆን የሌላውም መዳን አበሳጫቸው፡፡ ጠላት በቤርያ ሰው ባይኖረውም ከተሰሎንቄ ግን እስከቤርያ ድረስ ሰው ያስመጣል፡፡ ያውም እያቻኮለና በፍጥነት!!!
      የወንጌል አገልግሎት ለማደናቀፍ እየተደራጁ በየቦታው ከገዳም እስከአጥቢያ ፣ከገጠር እስከከተማ፣ ከደብር እስከመስበኪያ አውደምህረት በመሄድ የሚበጠብጡና በሰዎች መዳን ቀንተው ጉባኤ የሚያውኩ ሰዎችን አውቃለሁ፡፡በሚገርማችሁ ሁኔታ አፋቸውን ሞልተው "ከወንጌል ጠቅሰው" ጌታ ይፈቅዳል ሊሏችሁ ሁሉ ይችላሉ፡፡እነዚህ ሰዎች ከተሰሎንቄ እብዶች ጋር በምንም አይለያዩም፡፡እነዚህ ሰዎች ሐዋርያት በቤርያ እያስተማሩ እንደሆነ እጅግ በፈጠነ መንገድ ነው የሰሙት፡፡ከመዳን ወንጌል ይልቅ ብዙ ጊዜ የክፋት ወሬዎች ፈጥኖ የመሰማትና የመደመጥ እድል አላቸው፡፡የዚያኑ ያህል የመዳኑን ወንጌል ለመስማት የሚጠየፍ ጆሮ የክፋትንና የኃጢአትን ወሬ ግን ለመስማት የሚቸኩል መሆኑ ነው፡፡ ነገር እንዴት ተለዋውጦብናል!!!???
       አዎ! የጠላት ዲያብሎስ እግሮችና የከሳሽ አንደበቶች ሁሌም ፈጣን ብዙ ደጋፊም አላቸው፡፡ ሰይጣን ስራዎቹን በአስቸኳይ የሚሰሩለት ንቁ መልዕክተኞች ፈጣን አገልጋዮች አሉት፡፡ ሰይጣን ሁልጊዜ ሲችል እየቀደመ ካልቻለ እየተከተለ ሰኮና በመንከስ የወንጌል በር ለመዝጋት ይቃትታል፡፡ዳሩ ግን በሩ መከፈቱ፣ ወንጌሉ መሰበኩ መቼም አልተቋረጠም፡፡ፈጣን አገልጋዮች ቢኖሩትም ለብዙዎች ፈውስ ሆነው ለራሳቸው ግን በበሽታ የሚንገላቱ የጌታ ደካማ አገልጋዮች ግን (2ቆሮ.12÷8፤ፊሊ.2÷27፤1ጢሞ.5÷23) በተግዳሮቱና በመከራው ሳይሰቀቁ ወንጌሉን ከምድር ዳርቻ እስከምድር ዳርቻ ይናኙታል፡፡አዎ! የሚያገኘን ህማምን መከራ ለሞት የሚያበቃና የሚያደርስ ቢሆን እንኳ ጌታ በእኛና በደካማ ባርያዎቹ፣ምንም አይነት ሞገስና ብቃት በሌለን ልጆቹ ሲሰራ ከዘመናት እጅ በአፍ እያስጫነ ነው፡፡
         ውዱ ጌታን የምታገለግለው ፣ወንጌሉን ጨክነህ የምትጮኸው ፣ቤተ ክርስቲያንን የምታጸናው ሆይ! ከሳሾችህ ካንተ በላይ ቢሆኑም ፣እግሮቻቸው ካንተ በላይ ቢፈጥኑም፣በሄድክበት ሁሉ ሰላይና ወሬ ጠላፊ ቢያሰማሩም አይዞህ በርታ!!! ይህ ሁሉ እያለ አምላክህ ምርኮን ያበዛልሃልና ጽና!!! በተሰሎንቄ በር የዘጉብህ ቤርያ ድረስ ተከትለው ቢያስጨንቁህም ጌታ ግን ባንተ እጅ ወደመንግስቱ የሚያፈልሳቸው ልጆች ይሰጥሃልና ተጋደል!!!
       ጌታ ለበጎነት የጨከነ ልብ ይስጠን፡፡አሜን፡፡
                

2 comments:

  1. I don't remember who was said this,
    but it was truth (If you don't want
    knowledge try illiteracy.as long as
    we don't have wellness we gonna stuck one place the same way like from the beginning.we need stop & look our surrounding.at that time we gonna get the answer.great job
    PS keep doing what you doing,one day God he goon clean his house.PS
    Work restlessly until you reach your destination.God bless you.

    goal.

    ReplyDelete
  2. The truth has set you free.
    Outstanding work God bless you bra

    ReplyDelete