Friday 10 November 2023

ትምህርቱን ያር'ቅ ዘንድ!

Please read in PDF

ትምህርተ ሥላሴ የክርስትና ዋነኛ ትምህርት ነው። ጠንቅቀን ካልተረዳን ደግሞ ስተን የምናስትበት ትምህርት ነው። ቅድስት ሥላሴ የእምነት መሠረት እንደ መኾኑ፣ ይህን ትምህርት አለማመን ወይም ከትምህርቱ አንዱን አለመቀበል፣ ከኑፋቄ ያስመድባል። ለዚህ ምሳሌ፦ አርዮስንና መቅዶንዮስን በትምህርተ ሥላሴ ላይ ባመጡት ኑፋቄ መወገዛቸውን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስታውሷል።

ሥላሴ እርስ በርስ ባላቸው ግንኙነታቸውና ማለትም፣  “ሁሉ ከአባቴ ዘንድ ተሰጥቶኛል፤ ከአብ በቀር ወልድን የሚያውቅ የለም፥ ከወልድም በቀር ወልድም ሊገለጥለት ከሚፈቅድ በቀር አብን የሚያውቅ የለም።”(ማቴ.11፥27) በሚለውና፣ ሥላሴ ከፍጥረት ጋር ባላቸው ግንኙነታቸው "አንድ ናቸው" ብሎ ማሰብ አደጋው የትየለሌ ነው። በሌላ ንግግር አብ ከወልድ ወይም ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ያለውን ዐይነት ግንኙነት፣ ከፍጥረት ጋርም አለው ብሎ ማሰብና ማስተማር ጥፋቱና ስህተቱ ከባድ ነው።

የዳዊት ፋሲል "የሥላሴ አስተንትኖ" ስህተት ከዚህ ይመነጫል። "ኹሉም የኾነው ከአብ ነው፤ ... አንድም በአብ የኾነ የለም ... "ከ" ኹሌ ለአብ ነው፤ "በ" ደግሞ ኹሌ ለወልድ ብቻ ነው የተነገረው" ይላል።

ነገር ግን ሥላሴ እኛን ለማዳን በሠራው ሥራ፣ የማንነት ቀውስ ውስጥ አልገባም፤ ወይም ወልድ በመዋረዱ አምላክነትን እንደ መቀማት አልቆጠረም ወይም መንፈስ ቅዱስ ለቤተክርስቲያን በመሰጠቱ አላደፈም። ደግሞ፣ “ብዙ ልጆችን ወደ ክብር ሲያመጣ የመዳናቸውን ራስ በመከራ ይፈጽም ዘንድ፥ ከእርሱ የተነሣ ሁሉ በእርሱም ሁሉ ለሆነ፥ ለእርሱ ተገብቶታልና።”(ዕብ. 2፥10) ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ መለኮታዊ ክብሩን በመተው እንደ እኛ ሰው ኾኖ፣ መከራን በመቀበል አዳነን፤ ከእግዚአብሔርም ጋር ቤተሠብ አደረገን።

በሌላ ስፍራም በግልጥ እንዲህ ተብሎአል፣ "ሁሉም ከእርሱ[ከክርስቶስ]፣ በእርሱ[በክርስቶስ]፣ ለእርሱ[ክርስቶስ] ነውና፤ ለእርሱ[ለክርስቶስ] ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።" (ሮሜ 11:36)፣

እንደገናም፣

“እርሱም የማይታይ አምላክ ምሳሌ ነው፤ የሚታዩትና የማይታዩትም፥ ዙፋናት ቢሆኑ ወይም ጌትነት ወይም አለቅነት ወይም ሥልጣናት፥ በሰማይና በምድር ያሉት ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋልና ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኵር ነው፤ ሁሉ በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሮአል፤”(ቆላ. 1፥15-16) ይላል።

ስለዚህ ወልድ ፍጥረትን ፈጠረ ስንል፣ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ተለይቶ አይደለም፤ ስለዚህ ፍጥረት ኹሉ ለሥላሴ ይገዛል። በማዳን ደግሞ ወልድ በተለየ አካሉ መጥቶ ሥጋ ለበሰ እንላለን እንጂ አብም መንፈስ ቅዱስም ለበሱ አንልም። የክርስቶስ ማዳን ፍጻሜውም የሥላሴን መንግሥት መመሥረትና ማጽናት ነው።

እና ዳዊት ፋሲል ሆይ፤ እኒህን ኹለት ነገሮች እባክህን ለይና ከስህተትህ ታረም።

እኛ ግን እንላለን፣

“ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና፤ ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።”(ሮሜ 11፥36)

3 comments:

  1. Great post! I liked your thoughtful analysis. Keep writing—you have a talent for it!

    ReplyDelete
  2. Your blog consistently delivers excellence. Thank you for the valuable information!

    ReplyDelete
  3. Your post is a radiant example of brilliance! Insightful, well-articulated, and truly valuable. Thanks for sharing your perspective.

    ReplyDelete