Saturday 16 September 2023

ጥንቆላና ሃይማኖተኝነት!

 Please read in PDF

ከሰሞኑ የስልጤ አከባቢ ጉዳይ አስደምሞኛል። አንድ ቤተ እምነት “በጥንቍልናና መተት፤ በድግምት አማኞቼን ወይም ተከታዮቼን አጥቅተውብኛል” በሚል አስባብ፣ በኦርቶዶክሳውያንና በወንጌላውያን አማኞች ላይ ጥቃት ማድረሳቸውን በምስልም፣ በድምጽም፣ በምስለ ወድምጽም ተመልክቻለሁ።

እግዚአብሔር የፍጥረተ ዓለሙ አምላክና ገዢ ነው፤ እግዚአብሔር ኀጢአትን ጭምር ከወሰኑ ሳይወጣ ይቈጣጠረዋል፤ ሰይጣንም እንኳ በእግዚአብሔር ቍጥጥር ሥር ይገዛል፤ ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ በአማኝ ልጆቹ ላይ ሲራገም፣ ሲጣላ ቢውል፣ አንዳችም ስንዝር መጠጋት አይችልም፤ “በአጠገብህ ሺህ በቀኝህም አሥር ሺህ ይወድቃሉ፤ ወደ አንተ ግን አይቀርብም።” (መዝ. 91፥7) እንዲል።

እግዚአብሔር ለሕዝቡ ጽኑ ጥበቃና መግቦታዊ እንክብካቤ ስላለው፣ “በምድረ በዳ በጥማት፥ የነፋስ ጩኸትም በሞላበት ውድማ አገኘው፤ ከበበው ተጠነቀቀለትም፤ እንደ ዓይን ብሌን ጠበቀው።” (ዘዳግ. 32፥10) እንደ ተባለው፣ “ከበበው ተጠነቀቀለት” ሲል፣ የእግዚአብሔርን ጫጩቶቿን ለመመገብና ለመንከባከብ እንዲሁም ከአደጋ ለመንከባከብ እንደ ምታንዣብብ ወፍ ያለ ጽኑ ጥበቃና ትድግናን የሚያመለክት ነው።

ይህ እግዚአብሔር ዛሬም ያህዌ ኤሎሂም ነው፤ ፈጥሮ የሚንከባከብና ጠብቆ ወደ ፈቃዱ በሰላም የሚያደርስ አምላክ ነው። በአዲስ ኪዳንም፣ “ብዙ ሕዝብም ባየ ጊዜ፥ እረኛ እንደ ሌላቸው በጎች ተጨንቀው ተጥለውም ነበርና አዘነላቸው።” (ማቴ. 9፥36) ተብሎ ለጌታችን ኢየሱስ እንደ ተነገረው እንዲኹ፣ ለሚያምኑት እጅግ የሚራራ፣ በጭንቀታችንና በንቀት በመተዋቸው የሚያዝንልን ጌታ አለን! ኢየሱስ ሕዝቡን ከአጋንንት እስራት ይፈታና ነጻ ያወጣ፣ ከለምጻቸው ያነጻ የነበረው፣ ሳይታክት ይፈውሳቸው፣ ያስተምራቸው የነበረው … ሕዝቡና የሚድኑ ወገኖቹ ስለ ኾኑ ነው። ይህንም የሚያደርገው ለሕዝቡ ካለው ርኅራኄ የተነሣ ነው። ለኢየሱስ ሕዝቡ ዘወትር እንደ ጠፉ በጐቹ ሲኾኑ፣ እርሱ ደግሞ የማይታክት የዘላለም እረኛው ነው።

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ካለባት ጽኑ ሐሜቶች አንዱ፣ ጠንቋይና አስጠንቋይ አማኝና አገልጋዮችን “በጉያዋ ይዛለች” የሚል ነው። ከዚህ ሐሜት መች ይኾን የምትገላገለው? መችስ ነው በይፋ ተቃውማ ልክ ሐዳስያንን በአደባባይ እንደምታወግዘው፣ አስተማተኞችንና መተተኞችን፣ ጠንቋዮችንም የምታወግዘው? ሌላው ቤተ እምነት ደግሞ፣ “በኦርቶዶክሳውያንና በወንጌላውያን ጥንቁልና ተጐዳን” ሲል እየሰማን ነው፤ አለመታደል!

እውነተኛው ክርስትና ለጠንቋይም ለአስጠንቋይም ስፍራ የለውም፤ ጥንቍልና የአጋንንት ሥራ ነው ብሎ በይፋ ይቃወማል፤ ሃይማኖተኞች ግን በክርስትና ስም ሊጠነቁሉም ሊያስጠነቁሉም ይችላሉ። እናም ለኹሉም አንድ ጽኑና የታመነ ስብከት አለን!

ኢየሱስ ክርስቶስ ከየትኛው የአጋንንት እስራት ይፈታል፤ ይቤዣል፤ ይታደጋል፤ ነጻ ያወጣል፤ እናም ተደገመብን፣ ይደግሙብናል፤ ያስመትቱብናል ለሚሉትም ለሚደግሙትና ለሚያስመትቱትም እነሆ! ወደ ጌታ ኢየሱስ ኑና ከሃይማኖት እስራት ተፈቱ ልንል እንወዳለን!

1 comment:

  1. Ewinet, If you knew the bible and the church well, you would not say that. Do you know "ANDIMINTA Tirgum" in our church? What that means is detailed one-by-one interpretation of each and every verse in the bible. Andem this; andem that; lelam this... Thus, one verse can have three, four or more meanings depending on the case. I suggest that you talk to people who studied the Bible (old & new testaments) in our church. I can give hundreds of examples to highlight my point - I mean verses having multiple interpretaions. thanks.

    ReplyDelete