Wednesday 3 November 2021

መድሎተ ስሑት ወይስ “መድሎተ ጽድቅ”?! (ክፍል ፲፭)

Please read in PDF

ካለፈው የቀጠለ …

ከዚህ በታች ያሉት ዐሳቦች፣ ስለ መንፈስ ቅዱስ ጥምቀት መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምራቸው ታላላቅ እውነቶች ናቸው። የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት፦

1.  የመንፈስ ቅዱስን ጥምቀት ከመዳናችን ፈጽሞ ነጥለን ልናየው አንችልም። በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት እንዳስተዋልነው፣ ከክርስቶስ ጋር የአካል አንድነት የሚኖረን በመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት አማካይነት ብቻ ነው። በመንፈስ ቅዱስ የሚጠመቀው አማኝ፣ ሕያውና ቅድስት የኾነችውን የቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚካፈልና አማኞችን ወደዚህ ፍጹም አንድነት ለመጨመር የሚከናወን ታላቅ መንፈሳዊ ሥራ ነው።



በአካል ውስጥ ያሉ ብልቶች አንድ እንደ ኾኑ እንዲሁ፣ የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀትም የትኛውንም ልዩነት ሳይመለከት፣ የአካሉን ብልቶች ፍጹም አንድነት ያረጋግጣል፤ አካሉ እጅግ በሚያስደንቅ መልኩ “አካል ሁሉ እያንዳንዱ ክፍል በልክ እንደሚሠራ፥ በተሰጠለት በጅማት ሁሉ እየተጋጠመና እየተያያዘ፥” (ኤፌ. 4፥16) እግዚአብሔር በሉዓላዊነቱ ድንቅና ውብ፤ እጅግ ግሩም አድርጎ ይሠራዋል።

በዚህም እያንዳንዱ አማኝ በሌላው አማኝና አገልጋይ ሳይዋጥ፣ በክርስቶስ አካል ውስጥ የራሱ የኾነ ልዩ ስፍራ አለው።[1] ስለዚህም ለአካሉ ፍጹም የማያስፈልግ አማኝ ከቶውንም የለም! ይህም በመንፈስ ቅዱስ ክንውን ከመዳናችን ጋር በቀጥታ የሚያያዝ ነው።

2.  ልክ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ፣ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በምድር በነበረው አገልግሎቱ ተከታዮቹን ስለ መንፈስ ቅዱስ ጥምቀት አስተምሮአል፤ አጥምቆአልም፤ (ማቴ. 3፥11፤ ማር. 1፥8፤ ሉቃ. 3፥16፤ ዮሐ. 1፥33፤ 3፥5)።

3.  የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት፣ አማኙን ወደ ክርስቶስ አካል ብቻ የሚጨምር ሳይኾን፣ ደግሞም በክርስቶስ ውስጥ ልዩና አዲስ ስፍራን ይሰጠዋል። በርግጥም፣ “እናንተም በእኔ እንዳላችሁ እኔም በእናንተ እንዳለሁ” ብሎ ጌታችን ራሱ እንደ ተናገረ (ዮሐ. 14፥20)፣ በእርሱ እንኾን ዘንድ ሥራውን ኹሉ የሚፈጽመው መንፈስ ቅዱስ ነው።

በሰማያዊ ስፍራ በመንፈሳዊ በረከት መባረክን የምንባረከው፣ ከመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት የተነሣ በክርስቶስ አካል ውስጥ በመጨመራችን ነው።

4.  የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት፣ መዳንን ወይም የነገረ ድኅነት መፈጸምን ያመለክታል። መንፈስ ቅዱስ የሚያድረው ክርስቶስን ባመኑ አማኞች ውስጥ ብቻ ነው (ሮሜ 8፥9፤ 1ቆሮ. 6፥10)፤ መንፈስ ቅዱስ እኛ ውስጥ በመኖሩ መንፈሳውያን ነን፤ ከዚህም የተነሣ ሰውነታችንን ከኃጢአት ኃይልና ከኃጢአት ኵነኔና ከሞትም ፍጹም ያድናል።

5.  የአዲሱ ልደት ዋናው ማረጋገጫችን ወይም ዋናው መያዣና የመዳናችን ዋስትና በመንፈስ ቅዱስ መጠመቃችን እንጂ የውኃው ጥምቀት አይደለም፤ የውኃውን ጥምቀት የወሰደ ኹሉ የመንፈስ ቅዱስን ጥምቀት ተጠምቆአል ማለት አይደለም። “ … በጌታ በኢየሱስ ስም ብቻ ተጠምቀው ነበር እንጂ ከእነርሱ በአንዱ ላይ ስንኳ ገና አልወረደም ነበርና።” (ሐ.ሥ. 8፥16) እንዲል።

በሰማርያ የነበሩ አማኞች በፊልጶስ ቢጠመቁም፣ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት አልጠመቁም ነበር፤ ስለዚህም ከውኃው ጥምቀት ባሻገር በመንፈስ ቅዱስ መጠመቅም ሊያስፈልጋቸው ግድ ኾነ፤ ስለዚህም “በዚያን ጊዜ እጃቸውን ጫኑባቸው መንፈስ ቅዱስንም ተቀበሉ።” ይላል።

6.  የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት አንዴ ይፈጸማል። የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት የማይደጋገምና አንድ ጊዜ ብቻ የሚፈጸም ነው። እግዚአብሔር በልጁ የሚያምኑትን፣ በመንፈስ ቅዱስ ልጆቼ ብሎ የሚጠራቸው በመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት የተጠመቁትን ብቻ ነው፤ ይህም፣ “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና። አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና።” (ገላ. 3፥28) እንዲል፣ ከክርስቶስ ጋር አንድ ለመኾን፣ አንድ ጊዜ ብቻ በመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት ተጠምቀን፣ ከኹሉ ማለትም ከአካሉ ብልቶች ጋር አንድ ሰው እንኾናለን።

የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት፣ እንደ መንፈስ ቅዱስ ሙላት ወይም መሞላት አይደጋገምም፤ የሚፈጸመውም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ነው።[2]

7.  የመንፈስ ቅዱስ ጥምቀት አማኞች ሲጠመቁት፣ በአማኞች ላይ የሚያደርገው የባለቤትነት ማረጋገጫ ነው።[3] በሌላ ንግግር አማኙ በመንፈስ ቅዱስ ሲጠመቅ፣ የዘላለም ሕይወትና ከእግዚአብሔር ጋር ለዘላለም ለመኖሩ እንደ ቅድሚያ ክፍያ ወይም መያዣ የተሰጠው ነው።

የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊ፣ ስለ ውኃ ጥምቀት ስህተት

የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊ ብቻ ሳይኾን፣ ሌሎችም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሊቃውንት ስለ መንፈስ ቅዱስ ጥምቀት ግንዛቤ የላቸውም።

“… በዕለተ ዓርብ በደሙ ካሣ ሲከፍል ያንጊዜ የአዳምና የዓለም ኀጢአት ሁሉ የተደመሰሰ ስለኾነ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ጥንተ አብሶ በሰዎች ላይ አይገኝ የተባለው አምነው ለተጠመቁት ክርስቲያኖች እንጂ ከቤተ ክርስቲያን ውጭ ለኾኑት ሁሉ አይደለም። … ተጠማቂው በዕለተ ዓርብ ከጌታ ጐን በፈሰሰው ማየ ሕይወት በመጠመቁ ከጌታ ጋር አንድ በመኾኑ ጸጋውንም በማግኘቱ ኃጢአቱ ትደመሰሳለች፤ ኹለተኛውም ሞት አያገኘውም ማለት ነው።”[4]

“… የአዳምና ሔዋን ልጆች እንደ የጾታቸው በአርባ በሰማንያ ቀናቸው ሲጠመቁ በዘር ከወረደው መርገም ይገላገላሉ። የቀደሙ ወላጆቻችን ያስወሰዱት የጸጋ ልጅነት በጥምቀት ይመለስላቸዋል።”[5]

የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊም በግልጥ ቃል እንዲህ ይላል፤ “በጥምቀት የክርስቶስ አካል ሆኖ መሠራት የጀመረ እያንዳንዱ ክርስቲያንም ወደ እግዚአብሔር በማደግ ላይ ነው።”[6] ጸሐፊው፣ አማኙ የክርስቶስ አካል ውስጥ መሠራት የሚጀምረው በውኃ ጥምቀት መኾኑን በግልጥ ይናገራል። ዳግመኛ የመወለዱም ስፍራ ወይም ማኀፀን፣ የተባረከው ውኃ እንደ ኾነም ጭምር።[7] በተጨማሪም የውኃ ጥምቀት፣ የኀጢአት ሥርየትና ቅድስና እንደሚያሰጥ አጽንዖት በመስጠት ይናገራል።[8] ከዚህም የተነሣ የምንጠመቅበት ውኃ፣ “የድኅነታችን ውኃና(water of salvation) ወላጅ እናት” እንደ ኾነም ጭምር በድፍረት ይናገራል።[9]

ይህ በግልጥ የሚያሳየን፣ የ“መድሎተ ጽድቅ” ጸሐፊ፣ ስለ መንፈስ ቅዱስ ጥምቀት አንዳችም ዕውቀትና ማስተዋል እንደሌለው ነው። አንድ አማኝ የሚወለደውና ዳግመኛ ልጅነትን የሚያገኘው “ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ” ወይም በራሱ በመንፈስ ቅዱስ ብቻ እንደ ኾነ አለማስተዋሉ እጅግ የሚያሳዝን ነው።

ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ ዛሬም ባለመለወጥ ከቤተ ክርስቲያን ጋር አለ፤ ቤተ ክርስቲያንን በመንፈሱ የሚቀድስ፣ አማኞችን ኹሉ የሚያነጻና የሚቀድስ፣ መሲሑ ወዳለበት ወደ ጽዮን ተራራ ለማድረስና ሩጫቸውን እንዲፈጽሙ፣ በጥምቀቱ ዳግም ልደትን በመስጠት የሚጀምርና እንዲጨርሱም አብሮአቸው የሚቃትት ታማኝና አዛኝ ጰራቅሊጦስ፤ አካል ያለው አምላክ ነው፤ አሜን።

ይቀጥላል …



[1] ጆን ኤፍ. ዋልቮርድ፤ መንፈስ ቅዱስ - ማንነቱና አገልግሎቱ፤ 1989 ዓ.ም፤ USA; Dallas፤ አሳታሚ  LAPSLEY/BROOKS FOUNDATION ገጽ 185

[2] ጆን ኤፍ. ዋልቮርድ፤ መንፈስ ቅዱስ - ማንነቱና አገልግሎቱ፤ 1989 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ ገጽ 189

[3] መልሳቸው መስፍን (ዶ/ር)፤ ቤተ ክርስቲያን፤ 1997 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ ገጽ 187

[4] አበራ በቀለ (ሊቀ ጉባኤ)፤ ትምህርተ ሃይማኖትና ክርስቲያናዊ ሕይወት፤ ገጽ 204

[5] አቡነ ጎርጎርዮስ፤ ትምህርተ ሃይማኖት ርትዕት፤ 1993 ዓ.ም፤ አሳታሚ ማኅበረ ቅዱሳን ገጽ 43

[6] መድሎተ ጽድቅ፤ ያረጋል አበጋዝ(ዲያቆን)፤ ገጽ 113

[7] መድሎተ ጽድቅ፤ ያረጋል አበጋዝ(ዲያቆን)፤ ገጽ 128

[8] መድሎተ ጽድቅ፤ ያረጋል አበጋዝ(ዲያቆን)፤ ገጽ 129፤ 186

[9] መድሎተ ጽድቅ፤ ያረጋል አበጋዝ(ዲያቆን)፤ ገጽ 137

9 comments:

  1. ይገርማል በጣም ሕዝቤ እውቀት ከማጣት ጠፋ ይላል የእግዚአብሔር ቃል ጌታ ይባርክህ ወንድሜ እውቀቱ አሁንም በእጥፍ ይጨምርልክህ👀👀👀🙏

    ReplyDelete
  2. EGZEABHER tegawen yabzalehe bewenat enamesagenalen

    ReplyDelete
  3. GOD bless you for sharing Abiny.May the SPIRIT be your guide and strength for days to come,till your last breath.

    ReplyDelete
  4. God bless you bro for preaching this beautiful word of God that can save multitude of people who can obey the truth!!!

    ReplyDelete
  5. God bless for the precious and expensive teaching confidentially when many are hiding this truth!🙏

    ReplyDelete
  6. እኔ ኦርቶዶክስ ተከታይ ነኝ ግን ሁሌም ተከታትዬ አነባለሁ ምርጥ ነገር ነው

    ReplyDelete
  7. አሜን እውነት ነው መምህር ብዙ ተማርኩ እግዚአብሔር ይመስገን 🙏🙏🙏
    ተባረክ

    ReplyDelete
  8. What can i say? No words 😶

    ReplyDelete
  9. ምሳሌ 14-12 ለሰው ሁሉ ቅን የምመስል መንገድ አለ ፍፃሜ የሞት መንገድ ነው
    ስጋችን በጥርስ ይዘን ሕይወታችን እንታደግ

    ReplyDelete