Tuesday 5 October 2021

“ኑ! አለቃ ሹመን እንመለስ” ለምትሉ!

 Please read in PDF

ከሰሞኑ ጯኺ መፈክሮች ውስጥ፣ “ወደ ተቋማዊው ኦርቶዶክስ (institutional Orthodox) እንመለስ” የሚለው አንዱ ነው። የሚመለሱበት የአብዛኛዎቹ ምክንያታቸው ደግሞ፣ “‘ተሐድሶ’ ወደ ወንጌላውያን አፍላሽ ኾኖአል እንጂ፣ በራሱ መቆም ያልቻለ ነው፤ ስለዚህም ወደ ተቋማዊው ኦርቶዶክስ ተመልሰን አስቀድመን ከጴንጤነት እንዳን፤ ቀጥለን ደግሞ በኦርቶክሳዊ መንገድ ‘ክርስትናን’ እንስበክ” የሚል ነው። እኒህ ሰዎች፣ አኹን ላይ፣ ወደ ተቋማዊው ኦርቶዶክስ መመለስን ቀለል አድርገው ሲናገሩ፣ በወንጌላውያን “pulpit” ላይ የማርያምን ምልጃ ብንሰብክ፣ ከልካይ የለንም ባይ ፍጹም ተላላዎች ይመስላሉ!

እንመለስ ባዮቹ፣ የሚመለሱት ለአገልግሎት ወይም ለሚሽነሪያዊ ጉዞ አይደለም፤ በሚሽነሪ ልብ ለማገልገል አስበው ከኾነ፣ ይህን ያህል ነጋሪት መጎሰምና እንቢልታ ማስነፋትም አይገባቸውም ነበር። ማንም ወንጌልን ሲሰብክ፣ አንዳች ነገር ሳይሠራ፣ አስቀድሞ ስለ ራሱ እንዲያወራ አልተፈቀደለትምና። ደቀ መዛሙርት እንደ ተላኩት ዝም ብለው ወደ ተላኩበት ሄዱ እንጂ፣ ወደ “እንትን ልንመጣ ነውና ‘አቀባበል አድርጉልን’” አይነት ንግግር አልነበራቸውም። ከተደረገ በርግጥ ጨዋ ቢስነት ነው!

ወደ ኦርቶዶክስ በትክክል ወንጌል ለማገልግል ቢሄዱ አንቃወምም፤ ሌላውን አጥላልቶና ኮንኖ መሄድ ግን ስህተትም፤ ንቀትም ነው። ሲቀጥልም፣ ወደ ኦርቶዶክስ ሲሄዱ የነበሩበትን ምንም እንዳላተረፉበት መናገር አለማወቅ ወይም ውጤቱን አለማስተዋል ነው። ምክንያቱም ጌታ የእነርሱን ድካም አልፎ ብዙዎችን ወደ ወንጌል ብርሃን አምጥቶአልና። ይህን ዓይናቸው አይቶ መመስከር ይችል ነበረ!

ብዙዎች ከኦርቶዶክስ ስንወጣ ራእያችን ኹለት ነበር፤ አንደኛው የትንሣኤውን ወንጌል በትክክልና በድፍረት ለሚሰሙ ኹሉ ለመመስከርና እውነተኛውን አምልኮ በትክክል ለእግዚአብሔር ለማቅረብ፣ እውነተኛ ኅብረት ለማድረግም ጭምር ነበር። ምክንያቱም በዚያ እንሰማ የነበረው ወንጌል፣ ምስክርነትና ኅብረት፤ አምልኮውም ጭምር በኅብረ ፍጡራንና ቊሳት ያሸበረቀ ስለ ነበር፣ እርሱን ንቀንና ትተን ነበርና።

ይህን ስንወስን ከእግዚአብሔር ራእይ እንደ ተቀበልን፣ የቅዱስ ቃሉ መሠረትነት እንዳለን፣ የመንፈስ ቅዱስም ውስጣዊ ምስክርነትን አድምጠን እንጂ፣ በገዛ ስሜታችን ተነድተን አልነበረም፤ ለዚያም ነው ብዙዎች አብረውን ዋጋ በመክፈል ጸንተው የቆሙት። ለዚህም ወንጌል ለመታዘዝ ባላቸው ነገር በኹሉም ሊተባበሩን የወደዱት፣ ከለመዱትና ማኅበራዊ ሕይወትና ኅብረተ ሰብ ኑሮ ጭምር ስለ ቅዱሱ ወንጌል ሲገለሉና ሲለዩ እንደ ኪሳራና ጉዳት ያልቆጠሩት … ነገሩ ከእግዚአብሔር እንደ ኾነ በትክክል አምነው ነው።

ይህ ራእይ፣ ዛሬም ድረስ ለእውነተኛ ሐድሶአዊ ሥራ ለሚሠሩ አገልጋዮች፣ የተገለጠና የተብራራ ራእይ እንጂ ድብስብስና ግብስብስ ራእይ አይደለም፤ አዎን፤ ከእግዚአብሔር ራእይ ስንቀበል እንደ ታላቅ ሸክም(ባላደራ) እንጂ፣ ባሰኘን ሰዓት የምንጥለው ዘባተሎ ወይም አሸንካታብ አይደለም። ለጠራን ጌታ ታማኞች እንጂ ኹኔታን እያየን፣ በራድና ለብ የምንልም አይደለንም።

ድካም የለንም፤ የፍጹማን የመላእክት ማኅበር ነን፤ ኀጢአት አልባ ቅዱሳን … ነን አላልንም፤ አንልምም። የዳንን፤ የምንድን፤ ደግሞ መሲሐችን ሲመጣ ፍጹም ድነን መንፈሳዊ አካልን የምንለብስ መሲሑን ያመንን የመሲሑ ማኅበረ ሰቦች ነን! ዳግመኛ መሲሑን በፍጡራን አምልኮ ልናስቀናው ወደ ኋላ አንመለስም! ዳግም የፍጡራንን መካከለኝነት ልንመሰክር ወደ ኋላ አንመለስም፤ ዳግም ማርያምን እመ ምሕረት፣ ኢየሱስን ደግሞ አበ መዓት ልናደርግና፣ “ያድነነ እመዓቱ ይሰውረነ በምሕረቱ በእንተ ማርያም ወላዲቱ” ልንል አንመለስም! ኢየሱስ ብቻውን በማይከብርበት፤ በደባልነት በሚጠራበት በዚያ እኛም ዳሳችንን መጣል አንፈልግም!

ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ባለመጥፋት ከሚወዱ ሁሉ ጋር ጸጋ ይሁን፤ አሜን።” (ኤፌ. 6፥24)

3 comments:

  1. GOD bless you for sharing Abiny. May the SPIRIT be your guide and strength for days to come & till your last breath.

    ReplyDelete
  2. አይ ድንቁርና እግዚአብሔር በአንድም በሌላም መንገድ እንደሚናገር ረስተወሀል

    ReplyDelete
  3. ኦርቶዶክስ አንድ እግዚአብሔር ነው የሚመለክባት እኛ ድንግል ማርያም ታማልደናለች እንጂ አምላክ ነች አላልንም ብንል እንኳን
    ዝም አትለንም።ከኔ ሌላ አምላክ አታምልክ ብሏል ላልከው አዎ ብሏል እኛም ከሱ ሌላ አምላክ የለንም።

    ReplyDelete