Wednesday 3 January 2018

የብልጽግና ወንጌል፣ ከጌታችን ኢየሱስ ያልኾነ ልዩና እንግዳ ወንጌል - ክፍል ፯

Please read in PDF
ሬም በቀጣይነት የሰውን ሰው-ነት በመካድ ለሚያስተምሩት የስህተት አስተምሮአቸው የሚያነሷቸውን ጥቅሶች በማንሣት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምላሾችን እንሰጣለን፡፡
·        2ቆሮ.5፥1 ፦ ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ሥፍራ ሰው-ነታችንን “ምድራዊ ድንኳን” በማለት ይጠራዋል፡፡ ድንኳን ጊዜያዊ መኖርያ እንደኾነ እንዲሁ፣ ይህ የለበስነው ሥጋችንም በምንኖርበት ጊዜያዊ ዓለም ኗሪ፣ ለድካም ተጋላጭ፣ ሙስና መቃብር የሚያገኘው ነው፤ ስለዚህም ሥጋ መንፈሳዊ አካልን ሊለብስ ዳግም እስኪነሣ ድረስ በሞት ዓረፍተ ዘመኑ ይገታል፡፡ “የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰው-ነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” (2ቆሮ.4፥16) እንዲል፣ ይህ እንደድንኳን ያለው ጊዜያዊ ማደርያችን የኾነው ሰው-ነታችን፣ ይለወጣል፣ ይጠፋል፣ ይታደሳል፣ በክርስቶስ ኢየሱስ ከማይጠፋውና ሊሻር ከማይችለው ከሚኾነው ዳግም ትንሣኤ የተነሣ መንፈሳዊ አካልን ይለብሳል፡፡

   በቅዱስ ጳውሎስ ንግግር አሁን ከሚጠፋውና ከሚያልፈው መከራ አንጻር፣ ሊመጣ ያለው ክብር ሲነጻጸር እጅግ ታላቅና በምንም ሊመሰልና ሊተካከል የሚቻል አይደለም፡፡ መከራው እንዲያውም ሥፍራ ሊሰጠው የሚገባ አይደለም፡፡ በእጅ ያልተሠራ፤ የዘላለም ቤት የሚኾን፤ ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ አለንና፡፡ ይህም የሚኾነው ምድራዊው ድንኳን ሰው-ነታችን ሲፈርስ ወይም ምድራዊው ሰው-ነታችን ሲሞት ነፍሳችን ወይም መንፈሳችን “ሰው-ነታችንን” ይለያል፡፡ ድንኳኑ ሰው-ነታችንም ፈራሽ[ሟች] ይኾናል ማለት ነው፡፡ ይህ ማለት ግን የሥጋ ድንኳንነት እርባና ቢስ ወይም የቱታ ያህል ጥቅመ ቢስ ነው ማለት አይደለም፡፡
    በብዙ መከራና ሐዘን ውስጥ እንኳ እናልፋለን፤ “ለብሰን ራቁታችንን እንዳንገኝ”፣ ወደሰማይ እስክንሄድ ድረስ በብዙ እንቃትታለን፡፡ ስለዚህም ፍጹም ድኅነታችንን በመቀበል፤ የተዋጀውንና የትንሣኤውን አካል የለበሰውን አዲሱን ሰውነት ለመያዝ፤ ይህ ታላቅ ምስጢር የሚከናወንባትን ቀን ከምንም በላይ አብዝተን እጅግ እንናፍቃለን፡፡ የቃሉ ዓውድ ይህን ታላቅ መንፈሳዊ ነገርን ያመለክታል እንጂ፣ የሥጋን አላስፈላጊነትና ቱታ መኾን ብቻ ፈጽሞ አያመለክትም፡፡
·        ዮ.4፥19፦ “ይልቁንስ በጭቃ ቤት የሚኖሩ፥ መሠረታቸው በትቢያ ውስጥ የሆነ፥ ከብል በፊት የሚጨፈለቁ እንዴት ይሆኑ?” ቃሉን፣ በብሉይ ኪዳን በጠንካራ የግጥም ድርድር የተናገረው ቴልማናዊው ኤልፋዝ ነው፡፡ ቃሉ በቀጥታ ከዐፈር የተሠራውን የሰውን ሰው-ነት የሚያመለክት ሲኾን (ኢዮ.10፥9፤ 33፥6)፣ “ከብል በፊት የሚጨፈለቁ”  ሲልም፣ ሰው በቀላሉ እንደሸክላ ተሰባሪ ወይም ሟች መኾኑን አመልካች ነው፤ በሌሎች ስፍራዎችም ይህ ሃሳብ ተገልጦ አለ፤ (ኢዮ.7፥17፤ 22፥16፤ መዝ.22፥6፤ ኢሳ.64፥8፤ ሮሜ.9፥21፤ 2ቆሮ.4፥7)፡፡
   ቃሉ በንጽጽር የቀረበው፣ ኢዮብ፣ “ጻድቁ ፈጽሞ አይጠፋም” የሚለውን ሃሳብ ባለመደገፍ ነው፤ (ቁ.17)፡፡ ለዚህም የሰውን ኀጢአተኝነት አስረግጦ ይሞግታል፤ በኢዮ.4፥7፤ 9፤ 17 ሰው ኹሉ ኃጢአተኛ ነው፤ ንጽሕናም የለውም ይላል፡፡ በሌላ መንገድ በንጽጽሩም ውስጥ ሰውና መላእክት ተያይዘው ቀርበዋል፤ከዚህ በሚበልጥ ንግግር፣ “እነሆ፥ በባሪያዎቹ አይታመንም፤ መላእክቱንም ስንፍና ይከስሳቸዋል፤” በማለትም፣ የመላእክትን ታናሽነትና አዳፋነት በግልጥ ይናገራል፡፡ እጅግ ታላቅ በኾነ ንጽጽር ደግሞ፣ መላእክትን ስንፍና የሚከሳቸው፤ እግዚአብሔርም የማይታመንባቸው ከኾነ፣ ሰው-ነቱ እንደጭቃ ቤት የኾነና ለአደጋ ተጋላጩ ምስኪን ሰውማ እንዴት እጅግ ያንስ ይኾን?
    እኒህ መዋቲ የኾኑ ሰዎች ሲጠፉ፣ እንደማይታወቁ ነፍሳት በእግዚአብሔር ፊት ምንም እንዳልኾኑ መገንዘቡ ግልጥ ነው፡፡ የሰው ልጅ አሟሟት እንደሚፈርስ ድንኳን “ጥበብ አልባ ወይም ዐላማ ቢስ” ነው፡፡ መላእክቱን ያልታመነው ጌታ ይልቁን ደካማው የኾነው የኀጢአተኛው ሞት አንዳች አይነካውም፡፡ ይህ ደካማ ሰውም ከምንም በላይ የእግዚአብሔርን ልቀትና ታላቅነት አምልቶና አስፍቶ መናገር ፈጽሞ አይቻለውም፡፡
   የኤልፋዝ ንግግር የሥጋን ዕርባና ቢስነት ፈጽሞ የሚናገር አይደለም፡፡ ኀጢአት ስለሚያስከትለው አስከፊ ገጽታና መዘዝ እንጂ፡፡ ይህም እንኳ ኹሉን ኀጢአተኛ የሚመለከት አይደለም፡፡ ስለዚህም በማናቸውም የሕይወት መንገድ እንዲህ ያለ ጊዜያዊ መከራ ሲደርስበት [እጅግ አጭር ከመኾኑ የተነሣ “በጥዋትና በማታ መካከል” ተብሎ ለተጠቀሰው ጊዜ ያህል] እጅግ ታጋሽ መኾን እንዳለበት ቁስለኛውን ኢዮብ ያሳስባል፡፡
    ቁ.21 ላይ ያለውን አዲሱ መደበኛ ትርጉም፣ “ያለጥበብ ይሞቱ ዘንድ፣ የድንኳናቸው ገመድ አልተነቀለምን?” በማለት፣ የሰውን አካል ልክ እንደድንኳን ጊዜያዊ መኾኑን ያስቀምጣል፡፡[1] ይህም የቁ.19ን ሃሳብ የሚያጸና ነው፡፡ ስለዚህም ቃሉ የቀረበው መላእክት እንኳ ንጹሐን ባልኾኑበት መንገድ፣ ይልቁን ሥጋ ለባሹ ከጭቃ ወይም ከአፈር የተሠራው ሰው እንዴት በእግዚአብሔር ፊት በደል አልባ ኾኖ ሊቀርብ ይቻለዋል? የሚል ሞጋች ሃሳብን የሚያቀርብ ነው፡፡
  የእምነት እንቅስቃሴ መምህራን ይህን ቃል ለራሳቸው እንደሚጠቅሱት፣ የሥጋን “የነፍስ ተራ ማደርያነትን´ አመልካች አይደለም፡፡ የሥጋን ሥጋነት ወይንም ከምድር አፈር ወይም ጭቃ መዘጋጀቱን አምኖ ደካማነቱንና ከመላእክት አንጻር እንኳ የእነርሱን ያህል ንጹሕ አለመኾኑን ለማመልከት የተነገረ እንጂ ምንም እርባና እንደሌለው ታስቦ የተነገረ ቃል አይደለም፡፡ ቃሉን በተነገረበት እንዲህ ያለ ክብር ለመረዳት “አለመድከም” ግን እግዚአብሔር እኛን ካየበት ታላቅ ክብር በገዛ ፈቃድ ራስን ማውረድና ማዋረድ ነው፡፡
    ካነሣን አይቀር፣ ስለሰው ሰውነት የቡዛዊውም የባርክኤል ልጅ ኤሊሁ እንዲህ ሲል ይናገራል፤ “ነገር ግን በሰው ውስጥ መንፈስ አለ፥ ሁሉንም የሚችል የአምላክ እስትንፋስ ማስተዋልን ይሰጣል፡፡” (ኢዮ.32፥8) ይላል፡፡ በአጭር ቃል ኤሊሁ ሰው መንፈስ ነው አይለንም፤ በሰው ውስጥ መንፈስ መኖሩን ይነግረናል እንጂ፤ ይህ ደግሞ በበዛው የቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርት ውስጥ ያለ ነው፤ (ሉቃ.1፥46፤ ዮሐ.12፥27፤ 13፥32፤ ራእ.6፥9)፡፡
·        1ቆሮ.1553፦ “ ... ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፥ መንፈሳዊ አካል ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊ አካል ካለ መንፈሳዊ አካል ደግሞ አለ፡፡ ... ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሊለብስ ይገባዋልና፡፡ ...” የሚለውን የሥጋን ከንቱነት ሊሞግቱበት ከሚያቀርቧቸው ትቀሶች አንዱ ነው፡፡ ነገር ግን እያነሣን ካለነው ሃሳብ ጋር ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ምንም የሚያገናኘው ነገር ባይኖርም እናብራራው ዘንድ ይገባናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ስለትንሣኤ ሙታን አስፍቶ በተናገረበት ክፍሉ የተናገረው ነው፡፡ በትንሣኤ ሙታን አዲስና መንፈሳዊ፤ የማይበሰብስን አካል እንለብሣለን፡፡ ይህ ሥጋን ስለመካድ ወይም ግዙፍነት ስላለመኖሩ የተነገረ ቃል አይደለም፡፡
    “መንፈሳዊ”(pneumatikos) የሚለውን ቃል ሐዋርያው የተጠቀመው፣ አካላዊነትን በመቃወም ወይም ባለመቀበል አይደለም፡፡ በአጭሩ ፍጥረታዊ ሲል፣ በፍጥረታዊ ማንነት ወይም በራስ ጥረት የሚደረግን ሥጋዊ ሥራን፣ ትምክህትን የሚያመለክት ሲኾን፣ መንፈሳዊ ሲል ደግሞ፣ ኹለንተናን በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር ሥር ስለማድረግ ወይም መኾንን የሚያመለክት ነው፡፡ ስለዚህም ቃሉ የመንፈስ ቅዱስ ምሪትን የሚቀበል ማንነትን የሚያሳይ ነው፡፡ ይህም ከመንፈሳዊ ባሕርይ ጋር ፍጹም መስማማትን የሚያመለክት ነው፤ (ሮሜ.7፥14፤ 1ቆሮ.2፥13፤ ገላ.6፥1)፡፡
     በሙታን ትንሣኤ ከሚኾኑት ነገሮች አንዱ ሰውነታችንን መጣል ሳይኾን፣ በኹለንተናችን መንፈሳዊውን አካል ወይም የማይበሰብሰውን አካል ለብሰን በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር ሥር እንኾናለን ለማለት የተነገረ ቅዱስና ክቡር ቃል ነው፡፡ አካሉ ተፈጥሮአዊ ወይም ሰው-ነታዊ ነው፤ ነገር ግን ወደፍጹም ሙላትና እግዚአብሔር ወዳሰበልን ክብርና ሙላት የደረሰ ወይም የሚደርስ ስለኾነ መንፈሳዊ ተብሎ ተገልጧል፡፡
    ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን መካከል ሲነሣ ሰው-ነትን ጥሎ[ክዶ] አልተነሣም፡፡ ባዩት ጊዜም፣ መንፈስ እንጂ ሥጋና ደም ጭምር ስላልመሰላቸው ደቀ መዛሙርቱ፣ “እኔ ራሴ እንደ ሆንሁ እጆቼንና እግሮቼን እዩ፤ በእኔ እንደምታዩት፥ መንፈስ ሥጋና አጥንት የለውምና እኔን ዳስሳችሁ እዩ” (ሉቃ.24፥39) አላቸው፡፡ ለመግደሎሟ ሴትና ለሌሎችም ታያቸው (ዮሐ.20፥18፤ ማቴ.28፥17)፣ ሰገዱለት(ማቴ.28፥17፤ ሉቃ.24፥52)፣ ደግሞም አብሯቸው በላ (ዮሐ.21፥15)፣ ቀርቧቸው አብሯቸው ሄደ(ሉቃ.24፥15)፣ ወደሰማያትም ሲያርግ ደመና ከዓይናቸው እስክትሠውር በመራቅ እንጂ በመርቀቅ አላረገም፤ (ሐዋ.1፥11)…፡፡
   እንኪያስ ትንሣኤውን የምንተባበር እንደዋናችንና እንደገዢያችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምንነሣው እንዲኹ ነው፤ ይህም የሚኾነው፣ “ብልቶቻችንን የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርገን ለኃጢአት ባለማቅረብ፥ ነገር ግን ከሙታን ተለይተን በሕይወት እንደምንኖር ራሳችንን ለእግዚአብሔር በማቅረብ፥ ብልቶቻችንንም የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርገን ለእግዚአብሔር በማቅረብ፤” (ሮሜ.6፥13) ነው፡፡ ራሳችንን የዓመፃ የጦር ዕቃ አድርገን ለኃጢአት ማቅረብ ፍጥረታዊ ማንነትን መያዝ ነው፤ ራሳችንን፤ ብልቶቻችንንም የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርገን ለእግዚአብሔር ማቅረብ ይህ ታላቅ መንፈሳዊነትና ለመንፈስ ቅዱስ ኹለንተናን ማስገዛት ነውና፤ ይዘን ለምንነሣው መንፈሳዊ አካል “መሠረትም” ነው፡፡
    የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላትም ስለሰውና ሰው-ነት የተናገረውን ብናነሣ ለዚህ ርእስ ዋቢ ይኾንልናል፤ “ሰው፤ እግዚአብሔር ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ የሕይወትንም እስትንፋስ እፍ አለበት፤ (ዘፍ.2፥7) ስለዚህ ሰው ሥጋና ነፍስ (መንፈስ) ነው፡፡ ሴትንም ከወንድ ፈጠረ፤ (ዘፍጥ.2፥21፤ 22)፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር ሰውን እንዴት እንደፈጠረው ከዚህ የበለጠ መግለጫ አይሰጥም፡፡ ሰው አስቀድሞ ሕይወት ካለው እንሰሳ ሳይሆን ግዑዝ ከሆነ ከዐፈር መፈጠሩን መጽሐፍ ቅዱስ በግልጥ ያስተምራል፡፡ ሰው ከእንሰሳት ፈጽሞ የተለየ መሆኑ በእግዚአብሔር መልክና ምሳሌ በመፈጠሩ ይታያል፤ (ዘፍ.1፥26፤ 2፥7፤ 3፥19)፡፡”[2]
   በዚኹ ገጽ ላይ ስለሰውነት ሲያብራራ፣ “ጠቅላላ የሰው ሁኔታ ሥጋና ነፍስ፣ ሰው መሆን ማለት ነው፤ ማቴ.5፥29፤ 6፥22፡፡ የውስጥ ሰውነት የሰውን መንፈስ (ሮሜ.7፥22፤ ኤፌ.3፥16፤ 17)፤ የውጭ ሰውነት ሥጋን ያመለክታል፤ 2ቆሮ.4፥16፡፡” በማለት ይተረጕማል፡፡ እኛም ከዚኹ ጋር በመስማማት ሰው ኹለንተናው ነፍስና ሥጋ ወይም መንፈስና ሥጋ ነው ብለን እናምናለን፤ እንታመናለን፡፡ ሰውን ግን መንፈስ ብቻ ነው የሚሉትን እንቃወማለን፤ ከሃሳባቸውና ከትምህርታቸውም አንተባበርም፡፡ ነቢያት አበው፣ ጌታችን ኢየሱስና ሐዋርያት በቅዱሳት መጻሕፍት ያስተማሩንን ብቻም እንከተላለን፡፡ ጌታ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሆይ! ስለረዳኸን ከብር፣ ምስጋና፣ ውዳሴ ላንተ ይኹን፤ አሜን፡፡
ይቀጥላል …





[1] በእርግጥ አንዳንድ ትርጉሞች እስከቁ.17 ድረስ ብቻ ያለውን ይይዛሉ፡፡
[2] መጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃል ገጽ.75

5 comments:

  1. geta tsegawn yabzalh

    ReplyDelete
  2. Mn aynet chikane new bel? Sew lind yemaychilewn gizuf aletama yenufake terara bekalu ewnetnet nadkew deledelkew aferarreskew:: ebakh abenezer wendme mulu adrashahin magignet binchil melkam neb2r

    ReplyDelete
  3. Mn aynet chikane new bel? Sew lind yemaychilewn gizuf aletama yenufake terara bekalu ewnetnet nadkew deledelkew aferarreskew:: ebakh abenezer wendme mulu adrashahin magignet binchil melkam neb2r

    ReplyDelete
  4. ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን መካከል ሲነሣ ሰው-ነትን ጥሎ[ክዶ] አልተነሣም፡፡ ባዩት ጊዜም፣ መንፈስ እንጂ ሥጋና ደም ጭምር ስላልመሰላቸው ደቀ መዛሙርቱ፣ “እኔ ራሴ እንደ ሆንሁ እጆቼንና እግሮቼን እዩ፤ በእኔ እንደምታዩት፥ መንፈስ ሥጋና አጥንት የለውምና እኔን ዳስሳችሁ እዩ” (ሉቃ.24፥39) አላቸው፡፡ ለመግደሎሟ ሴትና ለሌሎችም ታያቸው (ዮሐ.20፥18፤ ማቴ.28፥17)፣ ሰገዱለት(ማቴ.28፥17፤ ሉቃ.24፥52)፣ ደግሞም አብሯቸው በላ (ዮሐ.21፥15)፣ ቀርቧቸው አብሯቸው ሄደ(ሉቃ.24፥15)፣ ወደሰማያትም ሲያርግ ደመና ከዓይናቸው እስክትሠውር በመራቅ እንጂ በመርቀቅ አላረገም፤ (ሐዋ.1፥11)…፡፡amen amen amen

    ReplyDelete
  5. (ወደ ቆላስይስ ሰዎች 2 )
    =====================
    6፤ እንግዲህ ጌታን ክርስቶስ ኢየሱስን እንደ ተቀበላችሁት በእርሱ ተመላለሱ።
    7፤ ሥር ሰዳችሁ በእርሱ ታነጹ፥ እንደ ተማራችሁም በሃይማኖት ጽኑ፥ ምስጋናም ይብዛላችሁ።
    8፤ እንደ ክርስቶስ ትምህርት ሳይሆን፥ እንደ ሰው ወግና እንደ ዓለማዊ እንደ መጀመሪያ ትምህርት ባለ በፍልስፍና በከንቱም መታለል ማንም እንዳይማርካችሁ ተጠበቁ።

    ReplyDelete