Thursday 17 May 2018

ጌታችን ኢየሱስ ወደ ሰማያት ለምን ዐረገ? (ክፍል ፩)

Please read in PDf 

  ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ማረጉ ለእኛ ክርስቲያኖች ዋስትናና ወደ ሰማያዊው ዓለም ለመፍለሳችን ታላቅ የማይናወጥ ምስክራችን ነው፤ ዕርገት ከክርስትና ዋና ትምህርቶችም እንደ አንዱ የሚቆጠርበት ምክንያቱና ዕርገቱን አለ መቀበልም ከዋናዎቹ መናፍቃን የማስቆጠሩም የማይካድ እውነታ ይኸው ነው። እናም ጌታችን አምላካችን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ሰማያት በክብር ማረጉ፣ ለእኛ ለክርስቲያን አማኞች ታላቅ ፋይዳ አለው። ከእኒህ ታላላቅ ፋይዳዎች ሦስቱን መጥቀስ እንችላለን፤ እኒህም፦



1. ድል ነሺነቱንና የቤዛነቱን ሥራ መፈጸሙን ያረጋግጥ ዘንድ፤
   ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ ካላረገ በቀር ድል ነሺነቱና አሸናፊነቱ አይረጋገጥም፤ ድል መንሣቱንና ማሸነፉን የተረዳነውና ደፍረንም የምንመሰክረው ስላረገና ወደ ሰማያት ስለ ሄደ በዓይኖቻችን ስላየን ነው። ጌታችን ከሙታን መካከል የተነሣ ብቻ አይደለም፤ ድል ነሥቶ ወደ ሰማያትም በማረግ በግርማው ቀኝ የተቀመጠና በአባቱ ክብር ፈጽሞ የከበረም ነው። “አሁንም፥ አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር በአንተ ዘንድ በነበረኝ ክብር አንተ በራስህ ዘንድ አክብረኝ።” (ዮሐ.17፥5) የሚለው ጸሎት የተፈጸመው፣ ሲያርግና በግርማኝ ቀኝ የተቀመጠ ጊዜ ነው፤ “ … ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ፤” እንዲል፤ (ዕብ.1፥3)።
  በነቢይ መጽሐፍ ለመሲሑ፣ “እግዚአብሔር ጌታዬን፦ ጠላቶችህን ለእግርህ መቀመጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ አለው።” (መዝ.110፥1) ተብሎ የተነገረው ትንቢት የተፈጸመው፣ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድል ነሥቶ ወደ ሰማያት ባረገ ጊዜ ነው። እርሱ ጠላቶቹን ኹሉ ድል ነሥቷል፤ በድል መንሣቱም “ሞት ሆይ፥ መውጊያህ የት አለ? ሲኦል ሆይ፥ ድል መንሣትህ የት አለ?” (1ቆሮ.15፥55) የሚል ዝማሬ ተስተጋብቶ ከእውነተኛ አማኞች ተሰምቷል። በደሙ ለተመሠረተችውም ቤተ ክርስቲያን፣ “የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም” (ማቴ.16፥18) የሚል ብርቱ ኪዳን ተገብቷል።
  ይህንም ያደረገው ስለ እኛ የሠራው የማዳን ወይም የቤዛነት ሥራ ስለ ተጠናቀቀ ነው፤ ክርስቶስ ወደ ሰማያት ያረገው የመዳንን ሥራ ሙሉ ለሙሉ ፈጽሞ ነው። በሠራው የቤዛነት ሥራም እርሱም፣ አባቱም፣ መንፈስ ቅዱስም ረክተዋል፤ ደስም ተሰኝተዋል፤ በማረጉ ደግሞ የመዳናችን ነገር መጠናቀቁንና ጠላት ፈጽሞ ድል መነሣቱን ማሳያ ታላቅ ማስረጃ ነው። እጅግ አስደናቂው ነገር ማረጉ መዳናችንን በማጠናቀቁ ድል ነሺነቱን ሲያበስር፣ ድል ነሺነቱና አሸናፊነቱም በፍጥረት ኹሉ ላይ ሥልጣንን፣ ኃይልን መቀበሉንም ያሳየናል። “ክርስቶስንም ከሙታን ሲያስነሣው ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይና በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ሊመጣ ባለው ዓለም ደግሞ ከሚጠራው ስም ሁሉ በላይ በሰማያዊ ስፍራ በቀኙ ሲያስቀምጠው በክርስቶስ ባደረገው ሥራ የብርታቱ ጉልበት ይታያል፤” (ኤፌ.1፥20-21)። ደግሞም በሌላ ሥፍራ፣ “እርሱም መላእክትና ሥልጣናት ኃይላትም ከተገዙለት በኋላ ወደ ሰማይ ሄዶ በእግዚአብሔር ቀኝ አለ” (1ጴጥ.3፥22) ተብሎለታል።
  ዕርገቱ የድል ነሺነቱ ዋና ምስክር ነው፤ “ሞቼም ነበርሁ እነሆም፥ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ፥ የሞትና የሲኦልም መክፈቻ አለኝ” (ራእ.1፥18) ብሎ የተናገረው ጌታና መሲሐዊው ንጉሥ፣ ይህን ታላቅ ሥልጣን የገለጠውና ሞትን ድል ነሥቶ የዋጠው፣ በከበረ ዕርገቱ ራሱን በማረግ ሲገልጥ ነው። ሞትም፣ ሲዖልም፣ ገሃነምም፣ የምድር ኃይላትም፣ አጋንንትም፣ መቃብርም፣ መበስበስም፣ የሞት ጣዕርም … ያልያዙትና ያሸንፉት ዘንድ ፈጽሞ ያልተቻላቸውና ከዘላለም እስከ ዘላለም ሕያው መኾኑን ያስረገጠው በማረጉ ነው።
  አሸናፊው ድል ነሥቶ በአባቱ ቀኝ፣ ግርማንና ክብርንም ለብሶ አለ፤ በክርስቶስ የተፈጸመውን መዳን ከማመን፤ እጅ ዘርግቶ ከመቀበል፤ ልብን እንደ ውኃ አፍስሶ ከመገዛት በቀር፣ እኛ ሌላ አንዳች ምርጫ የለንም። ክርስቶስ ከሠራው የመዳን መንገድ ውጭም ሌላ መንገድ ለራስ ማበጀትና መፈለግ፣ ሥላሴ የረኩበትን ፍጹም መንገድ፣ “እኔ አልረካሁበትም” የማለት ያህል ታላቅ ንቀት ነው። ክርስቶስ የሠራውን የቤዛነት ሥራ ሥላሴ ወደውታል፤ ረክተውበታል፤ የሰው ዘር ኹሉ ይህን የማይቀበል ከኾነ በብርቱ የእግዚአብሔር ቁጣ ሥር አለ ማለት ነው፤ (ዮሐ.3፥36)። ይህ ደግሞ የዘለዓለም ኵነኔና የገሃነመ እሳት አስፈሪ ፍርድ ነው።
   አባታችን እግዚአብሔር ባለበት በዚያ ለመኖር ስናስብ መንገዱ፣ ጌታችን ኢየሱስ መርቆ የከፈተልን መንገድ ነው። በማረግ ወደ አባቱ ሲሄድ፣ እኛም በእርሱ በኩል ወደ እርሱ እንደ ምንሄድ እየነገረንና እያሳየን ነው። “ … ሄጄም ስፍራ ባዘጋጅላችሁ፥ እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ።” (ዮሐ.14፥6) ብሎ ሲናገር፣ በማረግ መሄዱ ለእኛ ጥቅምና ክብር እንደ ኾነ ሲነግረን ነው። ስለዚህም የክርስቶስ ማረግ የመንፈሳዊ ሥፍራችን ዳርቻው የት ድረስ እንደ ኾነ ሊያሳየኝም ጭምር ነው። ቤዛችንን ጨርሶ የገባበት የሕያውነት እልፍኝ እኛም ከእርሱ በተሰጠን ሕይወት የምንገባበት እልፍኝ ኾነልን፤ አሜን ክብር ይኹንለት።
   ድል ነሺውና አሸናፊው ኢየሱስ ዛሬም በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ሥራን የሚሠራም ነው፤ እስከ አሁንም የሠራውን ሥራ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይገልጠዋል፤ “በእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ ብሎና የመንፈስ ቅዱስን የተስፋ ቃል ከአብ ተቀብሎ ይህን እናንተ አሁን የምታዩትንና የምትሰሙትን አፈሰሰው።” (ሐዋ.2፥33)፣ የማዳን ሥራውን ለዓለም እንዲናኝ፣ መንፈስ ቅዱስን በሐዋርያት ላይ ያፈሰሰው እርሱ ድል ነሺው የይሁዳው አንበሳ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ደግሞም እስጢፋኖስ በተወገረ ጊዜም ሊቀበለው በክብር የተነሣው፣ በክብር ያረገው የቤተ ክርስቲያን ራስ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው።
ድል ነሺው የቤዝወት ሥራውን አጠናቆ የሄደ ቢኾንም፣ ዝም ያለ ግን አይደለም፤ “የታመነውም ምስክር ከሙታንም በኵር የምድርም ነገሥታት ገዥ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ … በመቅረዞቹም መካከል የሚመላለስና” (ራእ.1፥4-5፤ 13)፣ መቅረዝ በኾነችው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚሠራውን ማናቸውንም ሥራ የሚመለከትና የሚያይ ከፊቱም ያልተሠወረ ገዥና ንጉሥ ነው። እምነታችን፣ አገልግሎታችን፣ ማንነታችን፣ የምናገረውና በልባችን የምናሰላስለውና የምናጉተመትመው ነገር ኹሉ በፊቱ የተራቆተና የተገለጠ ነው፤ ድል ነሺው በክበበ ትስብእት ብቻ ያለ አይደለም፣ ግርማ መለኮትንም ለብሶ በሰማያት በክብር በዙፋኑ አለ፤ እንኪያስ ላመናችኹ ኹሉ ማረጉ፣ መሄዱ ደስታችሁና እርካታችኹ ነው፤ ላላመናችሁት፣ በስሙ ለምትዘብቱ ግን ጽኑ ፍርድ ተጠብቆላችኋል፤ ጌታ መንፈስ ቅዱስ የተሰቀለውን፣ በሥጋ የሞተውን፣ የተነሣውንና ያረገውን ጌታ በእምነት ዓይኖች አስተውለን ማየት እንድንችል ዓይኖቻችንን ያብራልን፤ አሜን።

ይቀጥላል …

2 comments: