Sunday 4 July 2021

ከመንፈስ ቅዱስ “የተሻሉ አማኞች”!

 Please read in PDF

“ተግሣጽን የሚወድ ዕውቀትን ይወዳል፤ መታረምን የሚጠላ ግን ደነዝ ነው” (ዐመት)(ምሳ. 12፥1)

አይመጣም እንጂ ቢመጣ፣ ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ዘመን ካሉ አያሌ አማኞች የሚገጥመው ተቃውሞ እንዲህ የሚል ነው፤ “ምን ነክቶህ ነው ግን፣ ያን ኹሌ የቆሮንቶስን ነውር ፊት ለፊት የተናገርከው? በፍቅር ቀስ ብለህ በግል አትነግራቸውም ነበር? አጉል መተቸት ለምን ትወዳለህ? የሐዋርያት “አለቃ” የነበረውን ቅዱስ ጴጥሮስን ፊት ለፊት ስትቃወምስ ትንሽ ለምን አላፈርክም? ደግሞ የገላትያ አማኞችን አዚም[ጥንቆላ] ማን አደረገባችሁ ትላለህ እንዴ? …

አይመጣም እንጂ ቢመጣ፣ ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስ ቢመጣ ስፍራ ከማያገኙ አገልጋዮች አንዱ ነው፤ እንዴት ጽዮንን አመንዝራ ትላለህ? እንዴት የእግዚአብሔርን ምሕረት ማውራት ትተህ ውብ መቅደሱ ይፈርሳል፣ እግዚአብሔር ሕዝቡን ይሰብራል፣ ይጥላል ትላለህ? እንዴት ቅዱሱን የኪዳን ሕዝብ “”(ኤር. 5፥23) ብለህ ትናገራለህ? እንዴት ኹሌ ክፉ፤ ክፉ ብቻ ታወራለህ? አንተማ ለእስራኤል ባንዳና መዓት ተናጋሪ ብቻ ነህ! …

በነቢያትና በሐዋርያት ትምህርት ውስጥ፣ ኀጢአትን መጠየፍ ዋና ትምህርት ነው፤ በሐዋርያትና በነቢያት መሠረት ላይ ታነጽኹ የምትልም ቤተ ክርስቲያን፣ ኀጢአትን መጠየፏን በግልጥ ማሳየት ካልቻለችና በሥነ ልቡና፣ በድኅረ ዘመናዊነት ቀንበርና በእምነት እንቅስቃሴና በእውነት ቃል አገልጋዮች ትምህርት ሥር ራስዋን ካስጎበደደች የኀጢአት ነገር ይጎፈንናታል፤ ይመራታል። የደስታ ቃል ብቻ ይናፍቃታል፤ ተባርካችኋል፣ ሰላም ነው፣ ፍቅር ነን መባል ብቻ ያምራታል፤ ወቀሳን፣ ተግሳጽን፣ የተገለጠ ነውርና ኀጢአትን “ትክክል አይደለም!” አይወዱም፤ ኀጢአት እየተርመሰመሰ ቀና፤ ቀና ስለ ተወራ ብቻ ጽድቅና ቅድስና የሚበዛ የሚመስላቸው አማኞች ከየቦታው እየፈሉ ነው!

የመንፈስ ቅዱስ ጥማት፣ ቤተ ክርስቲያን “እድፈት ወይም የፊት መጨማደድ ወይም እንዲህ ያለ ነገር ሳይኾንባት ቅድስትና ያለ ነውር ትኾን ዘንድ” ነው፤ (ኤፌ. 5፥27)፤ ይህንም ሲያደርግ ደግሞ፣ “ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤” (ዮሐ. 16፥8)፤ ምክንያቱም የምንኖረውና የምንመላለሰው ሙሉ ለሙሉ ባልተዋጀው ዓለም ነውና፤ ጌታችን ኢየሱስ፣ “ከክፉ እንድትጠብቃቸው እንጂ” ብሎ እንደ ጸለየው፤ (ዮሐ. 17፥15)። መንፈስ ቅዱስ አባት አጽናኝ ነውና የሚጠብቀን እያባበለ ብቻ አይደለም፤ “ለመቀጣት ታገሡ፤ እግዚአብሔር እንደ ልጆች ያደርግላችኋልና፤ አባቱ የማይቀጣው ልጅ ማን ነው? ነገር ግን ሁሉ የቅጣት ተካፋይ ሆኖአልና ያለ ቅጣት ብትኖሩ ዲቃላዎች እንጂ ልጆች አይደላችሁም።” (ዕብ. 12፥7-8) እንዲል፣ ቀጥቶ ሊያስተምረንም ይወዳል!

ይህን የምንጠየፍ ከኾነ ግን፣ አንዳች ኃጢአት እንደ ሌለበት ወይም “በኀጢአት ጸንተው ሳለ”፣ ራሳቸውን እንደሚያታልሉ ዘመነኛ ኑፋቄያት “ኃጢአት የለብንም ብለን ራሳችንን እናስታለን” (1ዮሐ. 1፥8)። እናም እውነተኛ ተግሳጽን አንጥላ፤ በቅዱስ ቃሉ አማካይነት፣ መንፈስ ቅዱስ ወደ እኛ የሚያመጣውን ወቀሳ አንግፋ፤ እንደ ዕብራውያን አማኞች፣ በዳተኝነት አንመላለስ፤ ከመንፈስ ቅዱስ እንደ ተሻልንም ራሳችንን አንቊጠር!

 “ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ባለመጥፋት ከሚወዱ ሁሉ ጋር ጸጋ ይሁን፤ አሜን።” (ኤፌ. 6፥24)።

5 comments:

  1. I love you Guys in Christ.

    ReplyDelete
  2. May the Almighty God continue to bless you!

    ReplyDelete
  3. ተባረክ፤ ወንድሜ

    ReplyDelete
  4. እግዚአብሔር አብዝቶ ይባርክህ!

    ReplyDelete
  5. Touching message - empowered by Holy Spirit.

    ReplyDelete