Monday 2 October 2017

በጋሻው ደሳለኝ ና አዲሱ “የቃል እምነት እንቅስቃሴ” ትምህርቱ (ክፍል 1)

ግቢያ
     በዚህ ዘመን በእግዚአብሔር ዘንድ ያልታወቁትን(ማቴ.7፥23) በሕዝብ ዘንድ የገነኑትንና የታወቁትን አገልጋዮች “ተሳስታችኋል ተመለሱ” ማለት፣ ራስን በስለት ላይ የማቆም ያህል ሕመሙ ጽኑና እጅግ አደገኛ ነው፡፡ አደገኛነቱም ከሁለት ነገር አንጻር ነው፤
1.     ደጋፊዎቻቸው ብዙ ከመሆናቸው የተነሣ ተቃውሟቸው ተራ ተቃውሞ ሳይሆን፣ ልክ እንደቅዱሳን ሰማዕታት ስለመምህሮቻቸው በነፍስ ተወራርደው እስከመግደልና ስም ለማጥፋት የሐሠት ታሪክን ፈብርከው ከማኅበረሰቡ እስከማግለል ሊያደርስ በሚችል ጽኑ ቁጣ ውስጥ ስለሚገቡና፤
2.    ሕዝብ[አማንያንም ጭምር] ደግሞ እንዲህ ያለውን ነገር በቅንነትና በልበ ሰፊነት ከእግዚአብሔር ቃልና ከስህተት መምህራን ጠባይ አንጻር ከመመዘን ይልቅ፣ እንዲህ ያሉ መምህራንን የሚቃወሙትን አካላት ቀንተው ወይም ከጥላቻ አንጻር ... አንዳንዴም ሲከፋ የራስን ቅቡልነት በሕዝቡ ለማስረጽ የሚደረግ ደባ ነው በማለት፣ ተግሳጽና ተቃውሞውን በትክክል ለሕዝቡና ለእግዚአብሔር ከመቅናት አንጻር እንደተደረገ አድርጎ መውሰድ ፈጽሞ አልተለመደም፡፡

    ቢኾንም ለእግዚአብሔር ክብር በማድላት መናገር ግዴታችን ነው፡፡ “በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት፡፡ ማንም ወደ እናንተ ቢመጣ ይህንም ትምህርት ባያመጣ በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት፤ ሰላም የሚለው ሰው በክፉ ሥራው ይካፈላልና፤” (2ዮሐ.9-11)፤ “ፍሬም ከሌለው ከጨለማ ሥራ ጋር አትተባበሩ፥ ይልቁን ግለጡት እንጂ፥” (ኤፌ.5፥11) እንዲል፣ ከበጋሻውና ከመሰል የቃል እምነት አገልጋዮች ጋር ቅንጣት ታህል የሚያገናኘን ነገር እንደሌለን ማሳወቅ እወዳለሁ፡፡
    እውነተኛ ክርስቲያኖች እንደክርስቶስ፣ “በሚራራና በማይነቅፍ ልብ ከኀጢአተኞች ጋር ‘ለጊዜው’ ቢኖሩም” (ሉቃ.5፥30 ፤ 15፥1) በቋሚውና ዘወትር ሊታመኑለት ለሚገባቸው ጌታ ራሳቸውን ሲቀድሱ ግን፣ በማናቸውም ዓይነት ኹኔታ ኀጢአት ከሞላበትና ገዝፎ ከሚፋንነው፤ ከማያምነውም ማኅበረሰብ መራቅ ይገባቸዋል፡፡ ኀጢአት የኑሮ ዘይቤ በኾነበት ዓለም ክርስቲያኖች እንዲኖሩ አልተባለላቸውም፡፡ ይልቁን አለመተባበር፤ ከፍ ሲልም ክፋቱን መግለጥና ሌሎችም እንዲርቁ ማስጠንቀቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ምክንያቱም ብርሃን በምንም ዓይነት መንገድ በጨለማ ውስጥ ያለውን ክፋት ከመግለጥና አራቁቶ ከማሳየት አይቆጠብምና፡፡
    በየትኛውም ዘመን ሰይጣንና የሐሰት አገልጋዮቹ ሲነሡ፣ “አሳባችንን አበላሽተው ለክርስቶስ ከሚሆን ቅንነትና ንጽሕና ሊለውጡን የሚያልሙት” ከመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅስን በመጥቀስና ኢየሱስ የሚለውን ስም በመጥራት ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ ባሕርያቸውን፣ “እንደ እነዚህ ያሉ ሰዎች የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ፥ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች ናቸው” በማለት በግልጥ የተናገረው፤ (2ቆሮ.11፥3 ፤ 13)፡፡ የሐሰት መምህራን  የክፋት ጥጋቸውን ወዲያው አይገልጡልንም፤ ትምህርታቸውን ወዲያው ከመግለጥ የሚታቀቡት ውሸተኞችና ተንኮለኞች ሠራተኞች ስለኾኑ ነው፡፡
    እኒህ የሐሰት መምህራን የክርስቶስን የመዳን ወንጌል እያጣመሙና ከጥንት በነቢያትና በቅዱሳን ሐዋርያት የተሰበከውን በመቃረን፣ ለሐሰተኛው ክርስቶስ መንገድ ደልዳይ፤ ጎዳና አቅኚ፤ ጥርጊያ ጠራጊ ኾነው እያየናቸው ነው፡፡ ትምህርቶቻቸው የሐሰትና እጅግ አጸያፊ መኾኑን ስለሚያውቁ የሰው ልብ ነሁልሎ ፍጹም እስኪከተላቸው ይጠብቃሉ፤ ከዚያም በሙሉ ልብ እንደተከተላቸው ሲያስቡ አሳቻ ጊዜ ጠብቀው መርዛቸውን መትፋት ይጀምራሉ፡፡  
ሐሰት መምህራንን የመቃወማችን መጽሐፍ ቅዱሳዊ  እውነታ
1.     ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የሐሰት መምህራንን ትምህርቶቻቸውን በመቃወምና ስማቸውን ጠቅሶ በማጋለጥ ዋና ምሳሌያችን ነው፡፡ ለምሳሌም፦ ሄሜኔዎስና እስክንድሮስ[እስክንድሮስ የተባለው ምናልባት የናስ አንጥረኛው እስክንድሮስ ሊኾን ይችላል (2ጢሞ.4፥14)] (1ጢሞ.1፥20)፣ ሄሜኔዎስና ፊሊጦስ (2ጢሞ.2፥17)፣ ዴማስ(2ጢሞ.4፥10) እና ሌሎችንም መጥቀስ ይቻላል፡፡ ሐዋርያው የብሉይ ኪዳን ነቢያትን መጻሕፍት በትክክል ያውቅም ስለነበር፣ እንዲህ ያለውን መንፈሳዊ ድፍረት ከመንፈስ ቅዱስና ከቅዱሳን ነቢያት መውረሱን የማንክደው ሐቅ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳንም እንደቅዱስ ኤርምያስና ሕዝቅኤል ያሉ ታላላቅ ነቢያት የሐሰት ነቢያትን በማጋለጥ ለእግዚአብሔር ክብርና ቅድስና በመቆም ይታወቃሉ፡፡
     እግዚአብሔር አምላክ እረኝነትን በተመለከተ አንዲትም በግ ብትሆን የሚገደው አምላክ ነው፡፡ አንዲቱም በግ እንድትጠፋበት አይፈልግም፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ በሐሰተኛ እረኞች እጅ አንዲቱም በግ እንድትወድቅ ፈቃዱ አይደለም፡፡ የአገልጋይ ትልቁ ሥራም፣ “የሰው ልጅ ሆይ፥ ለእስራኤል ቤት ጠባቂ አድርጌሃለሁ፤ ስለዚህ የአፌን ቃል ስማ ከእኔም ዘንድ አስጠንቅቃቸው፡፡ እኔ ኃጢአተኛውን፦ በእርግጥ ትሞታለህ ባልሁት ጊዜ፥ አንተም ባታስጠነቅቀው ነፍሱም እንድትድን ከክፉ መንገዱ ይመለስ ዘንድ ለኃጢአተኛው አስጠንቅቀህ ባትነግረው፥ ያ ኃጢአተኛ በኃጢአት ይሞታል፤ ደሙን ግን ከእጅህ እፈልጋለሁ፤” (ሕዝ.3፥17-18) እንዲል፣ እንደከተማ ቅጥር ጠባቂ፣ በጦርነትም ጊዜ የከተማው ጠባቂ የጦርነቱን ኹኔታ ለከተማይቱ ነዋሪዎች እንዲናገር፣ ታማኝ የእግዚአብሔር አገልጋይም ከእግዚአብሔር የሕዝቡ ጠባቂዎች ኾነው፣ የእግዚአብሔርን ቃል በትክክል የሚያስተላልፉ ናቸው፡፡ ይህን ማድረግም መንፈሳዊ ግዴታቸው ነው፡፡
    አንድ አገልጋይ፣ “ኃጢአትን የምትሠራ ነፍስ እርስዋ ትሞታለች፤” (ሕዝ.18፥20) የሚለውን ቅዱስ ቃል ደፍሮ ለመናገር አንደበቱ ከተንተባተበ ወይም በሚያመቻምች ቃል ሊናገር “ቃላት ቅመማ ከጀመረ” እጅግ አደገኛ መንፈሳዊ ድንዛዜ ውስጥ ነው ያለው፡፡ እግዚአብሔር ኃጢአትን እንደሚጠየፍ በግልጥ መናገር ታላቅ መንፈሳዊ ምስክርነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ባሕርይ ውጭ የኾነውን ነውርና ርኩሰት ከመቅጣት ቸል አይልም፤ ይህን እውነት ቸል ብሎ ማለፍና ተቃራኒውን ማስተማር “ሐሰተኛ” ከመባል ውጪ ምንም ዓይነት ሌላ ስያሜ አያሰጥም፡፡
      ነቢዩ ኤርምያስ በትንቢቱ ያስተላለፈው ዋና መልእክቱም እግዚአብሔር ቅዱስና ጻድቅ ስለሆነ፣ እስራኤል ሁሉ ከክፋታቸው ተመልሰው በእውነትና በመታዘዝ እንዲያመልኩት እንጂ በሐሰት እንዳይሆን አበክሮ መናገር ነበር፡፡ ለዚህም ነው በግልጥ፣ “አታላይቱ ይሁዳ በሐሰት እንጂ በፍጹም ልብዋ ወደ እኔ አልተመለሰችም” (ኤር.3፥10) በማለት በግልጥ የተናገረው፡፡
     ስለሐሰተኛ ነቢያትም፣ “እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፦ ነቢያቱ ውሸት በስሜ ትንቢት ይናገራሉ፤ አላክኋቸውም፥ አላዘዝኋቸውም፥ አልተናገርኋቸውም፤ የውሸቱን ራእይ ምዋርትንም ከንቱንም ነገር የልባቸውንም ሽንገላ ይሰብኩላችኋል፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር በስሜ ትንቢት ስለሚናገሩ ነቢያት፦ በዚህች አገር ሰይፍና ራብ አይሆንም ስለሚሉ ስላላክኋቸው ነቢያት እንዲህ ይላል፦ እነዚያ በሰይፍና በራብ ይጠፋሉ፤” (ኤር.14፥14)፣ “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ትንቢት የሚናገሩላችሁን የነቢያትን ቃል አትሰሙ፤ ከንቱነትን ያስተምሩአችኋል፤ ከእግዚአብሔር አፍ ሳይሆን ከገዛ ልባቸው የወጣውን ራእይ ይናገራሉ፡፡ ለሚንቁኝ ሁልጊዜ፦ እግዚአብሔር፦ ሰላም ይሆንላችኋል ብሎአል ይላሉ፤ በልቡም እልከኝነት ለሚሄድ ሁሉ፦ ክፉ ነገር አያገኛችሁም ይላሉ፡፡ ቃሉን ያይና ይሰማ ዘንድ በእግዚአብሔር ምክር የቆመ ማን ነውና? ቃሉንስ ያደመጠ የሰማስ ማን ነው? እነሆ፥ የእግዚአብሔር ዐውሎ ነፋስ፥ እርሱም ቍጣው፥ የሚያገለባብጥ ዐውሎ ነፍስ ወጥቶአል፤ የዓመፀኞችን ራስ ይገለባብጣል፤” (ኤር.23፥16-19)፣ “እኔ አልላክኋቸውምና፤ ነገር ግን እኔ እንዳሳድዳችሁ፥ እናንተና ትንቢት የሚናገሩላችሁ ነቢያትም እንድትጠፉ በስሜ ሐሰተኛ ትንቢትን ይናገራሉ፥ ይላል እግዚአብሔር፡፡ ለካህናትም ለዚህም ሕዝብ እንዲህ ብዬ ተናገርሁ፦ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ሐሰተኛውን ትንቢት ይናገሩላችኋልና፦ የእግዚአብሔር ቤት ዕቃ በቅርብ ጊዜ ከባቢሎን ይመለሳል የሚሉአችሁን የነቢያቶቻችሁን ቃል አትስሙ” (ኤር.27፥15-16)፣ “ነቢያቶችዋም ከእግዚአብሔር ዘንድ ራእይ አላገኙም፤” (ራእ.2፥9)፣ “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ምንምን ሳያዩ የገዛ መንፈሳቸውን ለሚከተሉ ለሰነፎች ነቢያት ወዮላቸው! እስራኤል ሆይ፥ ነቢያትህ በምድረ በዳ እንደሚኖሩ ቀበሮች ናቸው፤” (ሕዝ.13፥3-4) በማለት በግልጥ ተናግረዋል፡፡[1]
    ቅዱስ ጳውሎስም ኃጢአተኝነትን እንድንክድና ከጽድቅ ጋር ብቻ እንድንተባበር በሁሉም መልእከቶቹ እጅግ አበክሮ ተናግሯል፤ (ሮሜ.8፥6 ፤ ቲቶ.2፥12)፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ ቅዱሱን የመዳንና የጸጋ ወንጌል ከሐሰት ትምህርት በመከላከልና ለዚያም ሥራ ታላቅ ዘብነቱን የሐሰት ትምህርትንና ሐሰተኛ አስተማሪዎችን ያለፍርሃት በማጋለጥ ይታወቃል፡፡ “በክርስቶስ ጸጋ እናንተን ከጠራችሁ ከእርሱ ወደ ልዩ ወንጌል እንዲህ ፈጥናችሁ እንዴት እንዳለፋችሁ እደነቃለሁ፤ እርሱ ግን ሌላ ወንጌል አይደለም፤ የሚያናውጡአችሁ የክርስቶስንም ወንጌል ሊያጣምሙ የሚወዱ አንዳንዶች አሉ እንጂ፤” (ገላ.1፥6-7)፤ በማለት የሐሰት መምህራን ወንጌልን ጨብጠው አናዋጭ እንደሆኑ በትክክል ገልጦታል፡፡
2.    እኛም ኃጢአተኝነትንና ኑፋቄን አሾልከው የሚያስገቡትን ፈጽሞ አንታገሳቸውም፡፡ ይህን የምናደርገው ለእነርሱ “ማስታወቂያን ስለመሥራት” አይደለም፡፡ በወንጌሉ ስም ተተግነው የሚዘሩትን የኑፋቄ ዘር ፍሬ እንዳያፈራ ስለማድረግ ነው፡፡ “የሚመጣውም ያልሰበክነውን ሌላ ኢየሱስ ቢሰብክ፥ ወይም ያላገኛችሁትን ልዩ መንፈስ ወይም ያልተቀበላችሁትን ልዩ ወንጌል ብታገኙ፥ በመልካም ትታገሡታላችሁ፤” (2ቆሮ.11፥4) እንዲል፣ የሐሰት መምህራንን ዝም ብሎ የሚያልፍና የሚታገስ ቆሮንቶሳዊ ጠባይን ልንይዝ አይገባንም፡፡
     አዎን! በጋሻውና ባልንጀሮቹ እንደሚሉት “ለወንጌል አገልግሎት” ሰዎችን ቢጠሩ፣ የሚሊኒየም አዳራሽ እንደማይበቃቸው ሲሸልሉ ሰምተናል፡፡ ይህ ተአምር ከመሰላቸው ተአምርነቱ ለእነርሱ እንጂ ለእኛ አይደለም፡፡ ምክንያቱም አሁንም በየቲቪ ቻናሎች የምናያቸው ብዙ የሐሰት ነቢያትና ሐዋርያት አዳራሾቻቸው ሞልተው እያየን ነውና፡፡ ይህ ማለት ግን በደጋፊና በሰሚ ብዛት ከክርስቶስ ያልኾነውን ልዩ ወንጌል መጋረድ፣ መሸፈን፣ ድል መንሣት ይቻላል ማለት አይደለም፡፡ እንዲያውም ከጥንት እንደምናየው የደጋፊ ብዛት ልብን ሲያሳብጥ፤ የማስተዋል ዓይንን ሲያሳውር ነው ያየነው፡፡
     በቀደሙት ዘመናትም የታመኑት ነቢያት ጥቂት ነበሩ፤ እንዲሁም እጅግ በጣም ጥቂት ደቀ መዛሙርት እንደነበራቸው መጽሐፍ ቅዱስና ታሪክ ምስክራችን ነው፡፡ በተለይም ደግሞ በዚህ ዘመን ራሳቸውን ለእውነተኛው ጻድቅና ቅዱስ አምላክ የለዩ አማኞችና አገልጋዮችን ማግኘት፣ ልክ በዔሊ ዘመን እንደነበረ እንደእግዚአብሔር ራእይ ብርቅና ልዩ ነው፡፡ የበጋሻው መውደቅ አያስደንቀንም ወይም ደስ አያሰኘንም፡፡ ከእግዚአብሔር መንግሥት ግን በአፍአ መሆኑ የክርስቶስ ልብ ላለን ሁላችን ያሳዝነናል፤ በመራራትም እንጸልይለታለን፡፡ ይህ መራራታችንና ማዘናችን ለኑፋቄ ትምህርቱ እንድናዝንና እንድንራራ ግን ፈጽሞ አይገፋፋንም፤ እኛም ለድርድር አናቀርበውም፡፡ ጌታ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነገር ሁሉ ማስተዋልን ያድለን፤ ለበጋሻውም ምልስና ሰሚ ልብ እንዲሰጠው እንማልዳለን፤ አሜን፡፡
ይቀጥላል …



      [1] ነቢዩ ሕዝቅኤልና ነቢዩ ኤርምያስ በተመሳሳይ ጊዜያት በተለያየ ሥፍራ ያገለገሉ ነቢያት ናቸው፡፡ ሁለቱም የምርኮ ዘመን ነቢያት ሲኾኑ፣ ነቢዩ ኤርምያስ ጌታ እግዚአብሔር ይሁዳን ከኃጢአቷና ከበደሏ ልትመለስ ስላልወደደች በአምላካዊ ፍርዱ ጠራርጎ ሁሉንም እንደሚያጠፋ በመናገሩ፣ በተደጋጋሚነትም ፍርድንና ጥፋትን ያዘለ ትንቢት በመናገሩ ሕይወቱ ለመተቸትና ለመነቀፍ እጅግ ተጋልጧል፤ (10፥24)፣ ከጥቂት ወዳጆቹ በቀር ብዙዎች ፈጽመው እስኪጠየፉትና እስኪርቁት ሐሰተኝነትን ፊት ለፊት ተጋፍጧል፤ ነቢዩ ሕዝቅኤልም በኮቦር ወንዝ ዙርያ ያሉትን ምርኰኞችን ሲያገለግል የኢየሩሳሌምን ውድቀት፣ የአወዳደቋን መጠንና ስፋት የኢየሩሳሌምን ካርታ አንስቶ በዙርያዋ ትእይንትን በማሳየት፣ ልክ እንደ የዓይኑ ዐምሮት የኾነች ሚስቱ፣ ቤተ መቅደሱም ከሕዝቡ መካከል እንዴት ከእነርሱ እንደሚወሰድ በማሳየት፣ ሕዝቡም በፍጹም ባርነት እንደሚጋዝ በግልጥ ተናግሯል፡፡
    እኒህ እውነተኛ ነቢያት ትንቢት በሚናገሩበት ወራት የሐሰት ነቢያቱ ሁለት ዋና ነገሮችን አድርገዋል፤ ሕዝቡ ከእግዚአብሔር የኾኑትን ነቢያት ከምርኮው በፊት እንዳልሰማቸው እንዲሁ፣ ከምርኮውም በኋላ እንዳይሰማቸው በብረቱ ጥረው አድርገው ሕዝቡን በማታለላቸው ለጊዜው “ተከናውኖላቸዋል”፡፡ የሐሰት ነቢያቱ ከምርኮው ዘመን በፊት “ሁሉም ነገር ሰላም ነው” በማለት ሕዝቡን ሲያታልሉ፣ ከምርኮው በኋላ ደግሞ እግዚአብሔር በዚያው እንዲቆዩ ሲያዝዝ የሐሰት ነቢያቱ ግን፣ “አይደለም” በማለት ሲሞግቱ፤ ሕዝቡንም ሲያታልሉ እንመለከታለን፡፡

15 comments:

  1. በዚህ ዘመን በእግዚአብሔር ዘንድ ያልታወቁትን(ማቴ.7፥23) በሕዝብ ዘንድ የገነኑትንና የታወቁትን አገልጋዮች “ተሳስታችኋል ተመለሱ” ማለት፣ ራስን በስለት ላይ የማቆም ያህል ሕመሙ ጽኑና እጅግ አደገኛ ነው፡፡ betam gobez lij ... berta

    ReplyDelete
  2. በውነት ያነበብኩት ፅሁፍ ለዘመናት የቆየውን በልቤ ያስቀመጥሁትን አንድ የሚቆጨኝን ነገር በተውሰነ መልኩ ስላቀለለልኝ እግዚአብሄርን ከልቤ አመሰግነዋለሁ። ቃለ_ህይወት ያሰማልኝ ለበለጠ ፀጋ ያድርስልን።

    ReplyDelete
  3. ትክክል ነው በርታ

    ReplyDelete
  4. ጌታ ጸጋና ምህረቱን ያበዛልህ ተወዳጅ ወንድም! የእውነት ጌታ እግዚአብሄር በነገር ሁሉ ጸጋን ይጨምርልህ! በእውነት ብዙዎች ለክርስቶስ ወንጌል ሳይሆን እርስ በእርስ ላላቸው መተዋወቅ ስህተቱን ለመግለጥ ዝም ባሉበት ወቅት በድፍረት እና መልካም በሆነ መንፈስ ለመናገር ስለ ቆረጥክ እና ስለጀመርክ ጌታ ኢየሱስ ዘመንህን ይባርክ! እንዳንተ አይነት ለክርስቶስ እንጂ ለሰዎች ባርያ ያልሆኑ ወንድሞችን እና አገልጋዮችን ያብዛልን! ቀጣዩን ክፍል ከጌታ ጋር እጠብቃለሁ! STAY BLESSED BROTHER!

    ReplyDelete
  5. አንተ ሌባ በዚህ ሁሉ ዝባዝንኬ ጽሁፍህ አንድ ግዜ በጋሻውን አንስተህ " ስለነቀፍክ " ኦርቶዶክሳዊ መምሰልህ ነው?አንተስ ከእነሱ በግብር አንድ አይደለህ?ወይስ ኦርቶዶክሳውያን ያነቡልኛል ብለህ ነው?....

    ReplyDelete
  6. Wendeme!!! Geta Bedemu Yegardeh Dengele Bemlgawa Tetebekeh Kirstos bemlkot Altegelesem kemalet yetebekeh .Libachen Bebzu Azenech Bedemu yetewajut hulu sayawekut kirstosen Eyekadu nachew.Geta hoy kante bich mhiret Ale yewetutenm Ante Geta Amlak Ereften Setachew.Amen!!!

    ReplyDelete
  7. ምነው አንተስ አጋሩ አልነበርክም እንዴ?

    ReplyDelete
  8. ወንድሜ በርታ ጸጋ ይብዛልህ

    ReplyDelete
  9. በጋሻው፡ ያሬድ፡ በሪሁን፡ መኳነንት፡ ያለው የሚባሉ ቡድኖች በአንድነት ነው እየሰሩ ያሉት፡፡ብዙ ህዝብን አታለዋል፡፡እባክህ ጻፍ የስህተት ትምህርት መሆኑን አጋልጠው፡፡ ደግሞ ለጥንቃቄ ይሁን የፍረቻ ሰው እየመረጡ ይሰበሰባሉ

    ReplyDelete
  10. በጋሻውን የተቃወምክበት ነገር አልገባኝም:: እንደቃሉ ያልሆነ ትምህርት አስተምሮ ከሆነ ለምን እንዲህ ያልከው ስህተት ነው እንዲህ ነው ቃሉ የሚለው ብለህ የማትገልፀውና ለኛስ የማታስረዳን:: ማስረጃ የሌለው ክስ ቅናት ይባላል ::

    ReplyDelete
    Replies
    1. በቀጣይ የወጡ ጽሑፎችን ተመልከት ወዳጄ!

      Delete
  11. በጋሻው ያሬድና በሪሁን መንፈስ ነኝ ይላሉ??

    ReplyDelete
  12. Amen! May God bless you with more!

    ReplyDelete
  13. ተባረክ ወንድማችን ጌታ በነገር ሁሉ ካንተ ጋር ይሁን በርታ

    ReplyDelete