Sunday, 30 September 2018

ነገረ ኢሬቻና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አበው!

Please read in PDF

   ማሳሰቢያ፦ ማንኛውም ሰው የፈለገውን እምነት የመከተል መብት ከያህዌ ኤሎሂም ተችሮታል፤ የወደደውንም “አምላክ”[እግዚአብሔርንም ኾነ ሰይጣንን] መከተል ይችላል፤  ታድያ ካመለክነው ዋጋችንን መቀበል ሳንዘነጋ!!!! ይህ ጽሁፍ የኢሬቻን አምልኮአዊ ሥነ ሥርዐት ለሚከተሉና ዋቄፈታን ሃይማኖታቸው ላደረጉ አልተጻፈም፤ ነገር ግን በክርስትና ውስጥ መስገው፣ ኢሬቻንና ዋቄፈታን ወደ ክርስትና አሹልከው ለማስገባት የሚጥሩትን ሥራቸውን ዕቡይ፤ መንገዳቸውን እኩይ ለማለት የተጻፈ ክርስቲያናዊ የተግሳጽ ጽሁፍ ነው!
ምክንያተ ጽሑፌ
   ሰሞኑን ሚድያውን ከሸፈኑት ነገሮች መካከል አንዱ፣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አበውና አንዳንድ “ክርስቲያኖች” [በክርስትና ስም ያሉትን ኹሉ ይመለከታል]፣ “ዕጣን ዕጣንነታቸውን፤ ክርስቶሳዊ ክርስቶሳዊነታቸውን” ትተው፣ “እሬቻ እሬቻ፤ ዋቄፈታ ዋቄፈታ” መሽተታቸው ነው። እናም ይህ ተግባራቸው እጅግ ቈጥቁጦኛል፣ ለምንስ እንዲህ መኾን አስፈለገው? ብዬ እንድሞግት አስገድዶኛል። በምን መሥፈርት አንዳንድ አባቶች “የኢሬቻ የክብር ተሸላሚ እንደ ኾኑና፣ ለምን ዓላማስ እንዲህ ሊሸለሙ እንደ ተፈለገ፣ ኢሬቻ “ባሕላዊ ወሃይማኖታዊ መልክ” ሊይዝ እንዳለው [እንደ ያዘና ዋቄፈታ በሚለው ዐውድ፣ እንደ ክርስትናና እስልምና ሃይማኖቶች “አምላኩን ጠርቶ” ሲባርክ እያየን ነውና] እየታወቀና እየተሄደበት፣ በግልጽ ሃይማኖታዊ ቀኖናና ዶክትሪን እየተዘጋጀለት ባለበት በአኹኑ ሰዓት፣ ክርስትናን በተለይም ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መታከክ ለምን አስፈለገ?፣ ከክርስትናና የክርስቶስ ጌትነትና አዳኝነት፣ ቤዛነትና ብቸኛ ዋጂነት በማይሰበክበት መድረክ ላይ፣ እኒህ አባቶች የስማቸው መጠራት፣ በተጨማሪም ጥቂት የማይባሉ ክርስቲያኖች በማምለኪያው ሥፍራ[1] መገኘታቸው አልኮሰኮሳቸው፣ አልከነከናቸው፣ አልቆጠቆጣቸው ይኾንን?” … የሚልና ብዙ የጥያቄ ማዕበሎች ይህን ጽሁፍ ለመጻፍ ምክንያት ኾኖኛል።

Thursday, 27 September 2018

በጌታ ቸርነት መጽሐፉ ታተመ!


Please read in PDF
በጌታዬ ኢየሱስ፣ በአባቱ፣ በማኅየዊ መንፈስ ቅዱስ ጉልበትና አቅም፤ ደግሞም እንደ ፈቃዱ እነሆ ታተመ!
መጽሐፉን በግልም ኾነ ማከፋፈል ለምትፈልጉ +251911044555 ወይም +251920893099 መደወል ወይም abentek2@gmail.com በሚል ሜይል አድራሻ ማናቸውንም መጽሐፉን የተመለከተ አስተያየት መስጠት ይቻላል። ክብር ለታረደው፣ ደግሞም ሕያው ኾኖ ለቆመው በግ ለመሲሑ ኢየሱስ ይኹን፤ አሜን።

Tuesday, 25 September 2018

የእግዚአብሔር ኃይል

Please read in PDF

“የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት፥ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና።”
(1ቆሮ. 1፥18)
    ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ በኢትዮጵያውያን ዘንድ የታወቀ አንድ ጠንካራ አባባል አለው፤ “እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል” የሚል፤ ይህ ትምህርቱ እጅግ ጥልቅ ታላቅ መንፈስ ቅዱሳዊ ማስተዋልን የሚሻ አስደናቂ ትምህርት ነው። የትምህርቱ አስደናቂነት እግዚአብሔር ፍጥረትን እምሃበ አልቦ ሃበ ቦ (ካለ መኖር ወደ መኖር) እንዳመጣው፣ እንደ ቀድሞ ፍጥረትን ፈጥሮ በማስገኘት እንዳመጣበት አመጣጥ ያለ አይደለም። ይልቁን “ሕያው የኾነውን” የሰውን[አሮጌውን አዳም] በመስቀልና በመግደል አዲስና ልዩ ሕይወትን፣ ማለትም ለእርሱ ብቻ ሊኖር ያለውን ጠባይና ባሕርይ ገንዘብ ያደረገን አዲሱን ሰው በማስገኘት እጅግ አስደናቂ የማዳን ሥራን በመሥራት የኾነ እንጂ።

Sunday, 23 September 2018

ይድረስ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር ዓቢይና ለክቡር የኦሮሚያ ክልል ፕረዘዳንት ለማ መገርሳ!

Please read in PDF

   አስቀድሜ ትልቁን የሰማይ አምላክ አንተ ብዬ በምጠራበት ዓውድ፣ ከኹለት አንዳችሁን ሳነሣ “አንተ” ብዬ ብጣራ “ባህል ጣሽ፣ አክብሮት ገሳሽ” [በምን አቅሜ - አንድዬ እያለ] አንባቢዎቼም እናንተም እንደማትሉኝ በመተማመን ነው። ስለዚህም አንተ ብዬ በምናገርበት ቦታ ላይ የንቀት ወይም ሌላ ምንም ነገር በውስጤ እንደ ሌለ አስቀድሜ መናገር እፈልጋለሁ።
    መቼም፣ “ይህ ጽሑፍ በየት በኩል ለእነርሱ ይደርሳል?” እንዳልባል፣ ኹለቱም መገናኛ ብዙሃንንና ማኅበራዊ መገናኛዎችንም በቅርብ ተከታታይ መኾናቸውን በተለያየ መንገድ አጣርቻለሁ፤ ከዚህ ባሻገር ኹለቱም በጽሕፈት ቤታቸው ብዙዎች የሚከታተሉት ማኅበራዊ መገናኛዎች አሏቸው፤ እናም ሊደርሳቸው እንደሚችል በማሰብ በእርግጠኝነት መጻፍን መርጫለኹ። ልጽፍ ያነሳሳኝ ዓቢይ ነገር ልቤ ላይ ደጋግሞ ስለመጣና ውጤቱንም በተደጋጋሚ በማየቴ፣ በሌሎች አገራትም ላይ ተመሳሳይ የታሪክ ስህተት መፈጸሙን በማስተዋሌም ጭምር ነው። የዚህ ጽሁፍ ዋነኛ ዓላማ፣ ኀጢአትን ለመኰነን ብቻ እንጂ የማንንም ባህልና ወግ የሚነካ ተግባርን የሚያካትት አይደለም።

Wednesday, 19 September 2018

“ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች” (መዝ. 42)

  የዳዊት መዝሙሮች፣ የብዙ ቅዱሳን ሰዎች ስብስብ መዝሙር ነው። ከእነዚህ አንዱ ደግሞ መዝ. 42ን በምሳሌነት መጥቀስ እንችላለን። መዝ. 42 ጠቅላላው በስደት ላይ ያለ አንድ ሌዋዊ የሚያለቅሰውን ልቅሶ የሚመለከት ነው። ከልቅሶው ውስጥ “ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፥ አቤቱ፥ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች። ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፤ መቼ እደርሳለሁ? የአምላክንስ ፊት መቼ አያለሁ? ዘወትር፦ አምላክህ ወዴት ነው? ሲሉኝ እንባዬ በቀንና በሌሊት ምግብ ኾነኝ።” (ቁ. 1-3) የሚለው ክፍል እጅጉን ልብ የሚሰብር ክፍል ነው።

   መዝሙሩን የዘመረው ሌዋዊ ከቆሬ ወገን የኾነ፣ የቤተ መቅደስ አገልጋይና በቤተ መቅደሱ በታማኝነት እግዚአብሔርን የሚቀድስ፣ የሚወድስ፣ የሚባርክ የነበረ ነው። ሌዋዊው የመሰደዱና ከአገሩ የመነቀሉ ምክንያት የእርሱ ኀጢአት ይኹን የሕዝቡ ኀጢአት በግልጥ አልተገለጠም፤ ከምንም በላይ ግን ጠንካራ የኾነ የእንባ ዘለላና ስብራት ከብቦታል። ሌዋዊው በልቅሶው ውስጥ በጠንካራ ሃዘን ተከብቧል፤ ከፍ ባለው ሃዘኑ ውስጥ ደግሞ በቤተ መቅደሱ ውስጥ በእግዚአብሔር ፊት ለመኾን ያለውንም ጉጉት ያመለክታል። ይህን ታላቅ መሻትና ጉጉቱን ግን ኀጢአት ወይም የአስጨናቂዎቹ እገታ ገድቦታል።

Sunday, 16 September 2018

ማኅበራዊ ድረ ገጾችን ለወንጌል አገልግሎት የመጠቀም አዎንታዊና አሉታዊ ተጽዕኖዎች

  “ዘመናችን ከሸማኔ መወርወርያ ይልቅ በሚቸኩልበት” (ኢዮብ 7፥6) በዚህ ወራት ነገሮች፣ ክስተቶች፣ ሁኔታዎች … ካሰብነው በተቃራኒው ወይም ካሰብነው በላይ ወደሆነ ጫፍ መፍሰሳቸው አይቀሬ ጉዳይ ነው። ለዚህ ደግሞ “አለምን ወደ አንድ መንደርነት እያመጧት” ያሉት የማኅበራዊ ድረ ገጻት ማለትም የኢንተርኔት፣ የሞባይል፣ የሳተላይት ቴሌቪዥን ግንኙነቶችና ሌሎችም ማኅበራዊ ድረ ገጻት በጎም ይሁን አሉታዊ ተጽዕኖዎች መኖሩ ክርክር የሚነሳበት ጉዳይ አይደለም።
    ቤተ ክርስቲያን “ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” (ማቴ. 28፥19) የሚለውን ሐዋርያዊ ታላቁ ተልእኮዋን መጠበቅና መፈጸም የሚቻላት፣ የሚድኑ ነፍሳትን የምታገኝባቸውን እድሎች አሟጣ ስትጠቀም ነው። ለምሳሌ፦ ፌስ ቡክ ወደ አንድ ነጥብ ሦስት ቢሊየን ገደማ አባላት ያሉት ሲሆን፣ ይህንን እውነታ ወደ እውነተኛው ዓለም ብናመጣው በ2016 ቆጠራ የተደረገለትን 1.2 ቢሊየን ገደማ የሚጠጋውን የአፍሪካን ሕዝብ ሽፋን ያካልላል ማለት ነው። ይህም የአድማሱን ሽፋን ብቻ ሳይሆን፣ በውስጡ የሚያስተላልፈው መልዕክት በቀጥታ ይሁን በተዘዋዋሪ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት “መደገፉ” አልያ ፍጹም መቃረኑ አይቀሬ ነው።

Sunday, 9 September 2018

ዘመን - የእግዚአብሔር የቸርነት ስጦታ


 ስለበላን ወይም ስለጠጣን፣ ለብሰን ስላማረብን ወይም እናት አባት፣ ጉልበት ስላለን ወይም መውጣት መግባት ስለቻልን፣ የአገራችን መሪዎች ደግ ወይም ክፉ ስለ ኾኑ፣ ደመወዛችን ስለ ተደላደለ ወይም የንግድ ወረታችን ስላማረበት ወይም ስለ ተትረፈረፈ ከዚህ አልደረስንም፤ ደግሞም ይህ የኾነልን በአጋጣሚ ወይም ከሌሎች የተሻለ ጽድቅና መልካምነት ስላለን፣ እንዲሁ ደግሞ ሌሎች ክፉዎችና እጅግ አላስፈላጊዎች ስለ ነበሩ ተወግደው ለእኛ ዘመን የተጨመረልን፣ ዕድሜ የተሰጠን አይደለም። አዎን! በሕይወታችን ዕድል፣ ዕጣ ፈንታ፣ አጋጣሚ፣ ድንገት፣ የአርባና የሰማንያ ቀን ጽዋ የሚባል ነገር ተሳክቶልን ከዚህ አልደረስንም።

Tuesday, 4 September 2018

የአዲስ ዓመት ስጦታ!

በቅርቡ በክርስትና "ዕቅበተ እምነት" ላይ የሠራኹትና የማስነብበው የመጀመሪያ መጽሐፌ፤ ምናልባትም ለብዙዎች የአዲስ ዓመት ክቡር ስጦታዬ! ጌታዬ ኢየሱስ ይህን ሥራ ስሠራ በብዙ ረድቶኛል! ክብር ለእርሱ ይኹን፤ አሜን።

                                           

የእኛው ቤት ጸበልና የአ.ተ.ት ወረርሽኝ


Please read in PDF

ከጵንኤል ያዕቆብ(Peniel Jacob) የፊት ገጽ (facebook) የተወሰደ



"ጸበል" ለአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አ.ተ.ት) ወረሽኝ መዛመት፥ ምክንያት ከሆኑት መካከል ዋነኛው መኾኑን የተለያዩ የጤናና የመንግስት ተቋማት በማሳሰብ ላይ ናቸው፡፡ የአ.ተ.ት ወረሽኝ ከሰውነታችን ውስጥ ያሉ ጠቃሚ ፈሳሻችን በተቅማጥ እና በትውከት መልኩ በመውጣት የሰው ልጅን ለህልፈት የሚዳርግ በሽታ ነው፡፡ (የጤና ባለሙያዋ ውዷ ባለቤቴም፥ እንደነገረችኝም ከኾነ አ.ተ.ት ይባል እንጂ የኮሌራ ወረሽኝ መኾኑን ነው)፡፡ ይሄም እንግዲህ፤ ሌላኛው የእኛው ቤት ዕዳ ነው፡፡ ለማስረጃነት ይረዳን ዘንድ፥ ከዚህ በታች የሰበሰብኳቸውን የተለያዩ ተቋማት ሪፖርት እንመልከት፥

Thursday, 30 August 2018

ቤተ ክርስቲያንም ከደቦ ገዳዮች እንደ አንዱ ስትኾን!

   Please read in PDF

ቤተ ክርስቲያን እንኳን የተፈጸመን ያልተፈጸመን ኀጢአት ማየት የምትችልበትን ነቢያዊ ችሎታ በመንፈስ ቅዱስ ተችሯታል። ኀጢአትን ለመቃወምና ለመጠየፍ፤ አለማዊነትንም ለመካድ ጭምር በክርስቶስ ኢየሱስ የተገለጠ የእግዚአብሔር ጸጋ ለቤተ ክርስቲያን ተገልጧል፤ (ቲቶ 2፥11-13)። ቤተ ክርስቲያን ይህን የተገለጠ ጸጋ በእውነት በመቀበልና በማመንም ጭምር፣ የሰማይ መንግሥት እንደ ራሴነቷን ማስቀጠል ይኖርባታል። ቤተ ክርስቲያን ይህን ዘላለማዊ አደራ ይዛ ለመሄድ ግን የሞተላትንና አንድ ቤዛዋን ክርስቶስ ኢየሱስን ትኵር ብላ መመልከት የዘወትር ተግባርዋ ሊኾን ይገባል።
  ክርስቶስ ኢየሱስ ጌታችንን እንደ ተሰቀለ ኾኖ ትኵር ብሎ አለማየት ለድንዛዜና ለክፋት፤ ለእውነት ለማያሳዝዝ አዚም ሳያጋልጥ አይቀርም፤ (ገላ. 3፥1)፤ አዚም የአእምሮ ችግር አይደለም፤ ራስንም የመሳት ጉዳይ አይደለም፤ ፍጹም አለማወቅና አለመረዳትም አይደለም፤ ነገር ግን መረዳት እየቻሉ አለመረዳት፣ ማስተዋል እየቻሉ ተላላ በመኾን አለማስተዋል፣ ማየት እየቻሉ መታወር፣ መጠንቀቅ እየቻሉ ፍጹም ቸለተኛ የመኾን ጉዳይ ነው። የገላትያ ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊቷ ያለውን እውነት በዝንጉነትና በቸለተኝነት ባለማስተዋል በአዚም ተያዘች። እናም የተሰቀለውን ክርስቶስን ባለማየት ስንፍና ተያዘች።

Thursday, 23 August 2018

የሊቀ ጳጳሳት ፍራንሲስ ማሳሰቢያ ኹላችንን አይመለከትምን?

    የካቶሊኩ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፍራንሲስ፣ “ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን በቀሳውስቷ በልጆች ላይ የሚፈጸሙ ወሲባዊ ጥቃት የመከላከል እንዲህ ያለ አድራጐት ተፈጽሞ ቢገኝ እንኳ አንዳትሸፋፍን የሚያደርግ ባህል ለማረጋገጥ አስፈላጊው ጥረት ሁሉ መደረግ እንዳለበት” ዛሬ ከጽሕፈት ቤታቸው አስታውቀዋል። ይህ እጅግ አስደናቂም አሰቃቂም ውሳኔ ነው፤ ይህን ስሰማ ቤተ ክርስቲያን እንዴት ባለ ነውር ተጠልፋ መውደቋን ደጋግሜ አሰብሁ፤ ውስጤም በጽዩፍ መንፈስ ኾኖ ተቈጣ።


Wednesday, 22 August 2018

ከሆነኝ ኢየሱስ!

Please read in PDF

ጠዋት በማለዳ ሲመሽም በሠርኩ
በኃጢአት ወድቄ ድኼ እያለቀስኩ
መሐሪ ፍለጋ ለበደሌ ይቅርታ

Wednesday, 15 August 2018

በሥጋ የተገለጠ አምላክ


    የክርስትና ትምህርት የመገለጥ ትምህርት ነው። የመገለጡ ምንጭ መለኮት ከኾነው ከራሱ ከእግዚአብሔር እንጂ፣ በሰው ወይም ከሰው አይደለም። ይህ መገለጥም “ከጥንት ጀምሮ በብሉይ ኪዳን ታሪክ እግዚብሔር በልዩ በልዩ መንገድ ለአበውና ለነቢያት በቃልም ሆነ በድርጊት፣ በራእይም ሆነ በሕልም በተአምራዊ ሁኔታ የገለጠላቸውን ሁሉ ያካትታል፤ በተለይም በኋለኛው ዘመን በሥጋ የተገለጠውን ክርስቶስንና የማዳን ሥራውን ሁሉ ይመለከታል።”[i]

ከዋናው መገለጥ በፊት የነበረው “መገለጥ”
     ብሉይ ኪዳን ታላቁን መገለጥ ፍለጋ ብዙ የመቃተት ድምጾች፣ ሕልሞች፣ ራእዮች፣ ትንቢቶች … የተሰማበት የምጥ መጽሐፍ ነው። እኒህ ብዙ መቃተቶችና ፍለጋዎች ለረጅም ዓመታት የተደረጉ ናቸው። በእኒህ ረጅም ዘመናት መላእክት ሊያዩት የሚመኙትንና ሰዎች ሊያገኙት ያላቸውን መዳን፣ ቅዱሳን ነቢያት “…ተግተው እየፈለጉ መረመሩት፤” (1ጴጥ. 1፥10-11)፣ ታላቁ ነቢይ ሙሴ፦ “የእግዚአብሔር ሕዝብ ሁሉ ነቢያት ቢሆኑ፥ እግዚአብሔርም በእነርሱ ላይ መንፈሱን ቢያወርድ አንተ ስለእኔ ትቀናለህን?” (ዘኊል. 11፥29) በማለት፣ ታላቁ መገለጥ ለሕዝቡ ኹሉ እንዲገለጥና እንዲያገኛቸውም አብዝቶ ተመኘ። እጅግ የሚደንቀው ነገር የዘኊልቅ መጽሐፍን ሲጽፍ እንኳ፣ እጅግ የበዛውን ትውልዶች በመቁጠር ሲደክም ትልቁ ዓላማው ሊያርፍበት ያለውን ዋናውን መሲህ ፍለጋ ነበር። እርሱን ስላላገኘም በብዙ ፍለጋ ውስጥ ማለፉን እናስተውላለን።
    አንድ አባት ይህን እውነት በመጽሐፋቸው እንዲህ ብለው ገልጠዋል፦

Saturday, 4 August 2018

ለ'ኔ ስትል "አርደህ"



"እኔ ቀናተኛ" ስትለኝ አምላኬ፤
እንዴት ትቀናለህ? ብያለሁ ሞግቼ፤
ግና ...

Wednesday, 1 August 2018

“ … ይጸለይባችኋል” ፤ እንዲህም ደግሞ መች ነው የተጀመረው?

Please read in PDF
(ምነው ነውራችን አላልቅ አለ?)
   ከአንድ ወዳጄ ጋር በሥራ ምክንያት ተገናኝተን የቤተሰቡን የውርስ ጉዳይ ያማክረኛል። ሁሉም የተትረፈረፈ ሃብት አላቸው። የአባታቸው ውርስ ደግሞ የእነርሱን ይበልጣል። ሕጋዊውን መንገድ ከተጨዋወትን በኋላ መላ ቤተሰቡ ተማምነው ለታላቅ ወንድማቸው ውክልና ይሰጡትና ንብረቱ በየድርሻቸው በታላቅ ወንድማቸው እጅ እንዲተዳደር ይደረጋል። በሰላም ነገሩ ተቋጨ። ነገሩ ከተጠናቀቀ ከሦስት ወር በኋላ ግን የቤቱ አራተኛው ልጅ (ከሌሎቹ ይልቅ እጅግ ብዙ ሃብትና ተሰሚነት አለው) እኔው ያለሁበት ድረስ ይመጣል። ለካ፥ ከመካከላቸው አምስተኛው ልጅ ከአራተኛው ታላቅ ወንድሙ ጋር ተጋጭቶ በጠብ ይፈልገዋል።